Monday, 14 April 2014 10:23

ድራግ - የሰሞኑ ወሬ

Written by  አበበ ተሻገር abepsy@yahoo.com
Rate this item
(1 Vote)

ከወንዱ ዘር ይልቅ የሴቷ ዘር ካናቢስ የበለጠ ተፈላጊ ነው፡፡ የካናቢስ ተክል እንደ ፓፓያ ተክል የወንድና ሴት ዝርያ አለው፡፡ የወንድ ፖፖያ ተክል የሚፈለገውን ፍሬ አይሰጥም ግን እሱ ከሌለ ሴቷ ፍሬ አትሰጥም፡፡ በካናቢስ በኩል ደግሞ ሴቷ በገበያው ላይ የበለጠ ተፈላጊ ነች (ወንድና ሴቱ በምን ይሆን የሚለዩት?)፡፡ ለምን የበለጠ ተፈላጊ ሆነች? ከተባለ ያችን ማነቃቂዋን ንጥረ ነገር (Psychoactive principle – tetrahy drocannabinol – THC)   የበለጠ የምትሸከመው እሷው ስለሆነች ነው፡፡ ቅጠሉም፣ አበባውም፣ ፀጉሯም በተለያየ መጠን ይህን ሥሙ ረዥም የሆነ ንጥረ ነገር ቲኤችሲ THC ትይዛለች፡፡ ዋጋውም ቅጠሉ ሌላ፣ አበባው ሌላ ሁሉም የየራሣቸው ተመን አላቸው፡፡ የት ነው የሚገኘው ብሎ ጠያቂ አለ?
እንዲያው ዋናው ንጥረ ነገር በሴቷ ካናቢስ በከፍተኛ መጠን ይገኛል ይባል እንጂ በጥቅሉ ካናቢስ ከ400 በላይ ንጥረ ነገሮችን የያዘ ጉድ ነገር ነው (የአማርኛው ጉድ) ከእነዚህ ውስጥ 60 ያህሉ ንጥረ ነገሮች ዋና ዋና ሡሥ አምጭዎች፣ አነቃቂዎች፣ አደንዛዦች፣ አእምሮና አካል ገዥዎች፣ በሽታና ሞት ጠሪዎች፣ ጓደኛና ቤተሰብ አባራሪዎች (የሆናችሁትን ሁሉ ማድረግ የሚችሉ) ናቸው፡፡ ዋናው ግን ቀደም ብለን ያነሳነው ንጥረ ነገር ቲኤችሲ ሲሆን ይህ ንጥረ ነገር በማሪዋና ውስጥ በትንሹ ከአንድ በመቶ ጀምሮ እስከ 15 በመቶ ድረስ ይገኛል፡፡
ማሪዋናን መጥቀሴ በአብዛኛው ገበያ ላይ ከሚገኙት ምርቶች ውስጥ ማሪዋናና ሃሽሽ (በተለያየ ቦታ የተለያየ መጠሪያ አላቸው) እነዚህ በቀዳሚነት ስለሚነሱ ነው፡፡ የተፈጥሮአቸውን ጉዳይ ለተመራማሪዎቹ ትተን እነዚህን ዕፆች በሚወስዱ ሰዎች ላይ የሚከተለውን አእምሯዊም በሉት ሥነ ልቦናዊ፣ የባህሪም ይሁን የስነልቦና፣ አካላዊም በሉት ማህበራዊ ጫናዎቹ ምን እንደሚመስሉ ለመመልከት እንሞክር፡፡  
ዘመናዊ የህክምና መሳረያዎች የአንጎልን ሥርዓትና ዕድገት ሁኔታ ለማጥናትና ለመረዳት ትልቅ እገዛ አድርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት እድሜአቸው እስከ 24 የሚደርሱ አፍላ ወጣቶች አንጎላቸው ሙሉ በሙሉ እድገቱን አይጨርስም፡፡ በተለያየ መነሻ በአፍላ እድሜ የማሪዋና፣ የሲጋራ ወይም የአልኮል መጠጥ የሞከረ አንድ ግለሰብ በወጣትነቱና በጎልማሳ የእድሜው ደረጃ ላይ በሱስ የመጠመድ እድሉ ሰፊ ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ የአፍላነት እድሜ ታዳጊ ውጣቶች ማሪዋናን እንደ ቀላል ጉዳይ አንሰተው ሊሞክሩ ይችላሉ፡፡ ምክንያታቸውም ጓደኛን ለመምሰል፣ ለመዝናናት፣ ከድብርት ለመውጣት፣ ከአዋቂዎች ጎራ የተቀላቀሉ ዓይነት ስሜት ለመፍጠር፣ መሳሰሉት ቀላል መነሻዎች ሊሆን ይችላል፡፡ ክፋቱ ግን ማሪዋናን ለመጀመር የሚቀለውን ያህል ለመተው የሚያስችል ሠፊ መንገድ የለም፡፡ ቀደም ሲል እንደጠቀስነው እነዚያ ንጥረ ነገሮች እንደሚወሰደው መጠን በደቂቃዎች፣ በሰዓታት ወዘተ በደም ውስጥ እየሰረጉ ይገባሉ፡፡ ከግለሰቡ ጋር ቁርኝት ይፈጥራሉ፡፡ በነገራችን ላይ ማሪዋናን ለሙከራ በሚል ከሚወስዱ ስድስት ሠዎች ውስጥ አንዱ በዛው ሠምጦ ይቀራል፡፡ በእርግጥ አብዛኞቹ ወጣቶች ወደዚህ ሱስ የሚገቡት በጓደኛ ተፅዕኖ ነው፡፡ በሱስ ውስጥ ያሉ ወጣቶች ለሌላ ሃይል አይኑራቸው እንጂ ጓደኛን ለመጎተት ብርቱ ናቸው፡፡ አፍላ ወጣት ነህ ሁሉን መሞከር አለብህ፣ ሞክረህ በሚሉና በተለያዩ ማሳመኛቸው ግብዣውን ሁሉ በማቅረብ ወይም ላያቸው ላይ በማጨስ ሊስቡ የሚችሉበት እድል ሰፊ ነው፡፡
ማሪዋና ጀማሪዎች ላይ መውሰድ ከጀመሩባቸው ቀናት አንስቶ አንዳንድ ያልተለመዱ ለውጦች ይስተዋላሉ፡፡ ለምሳሌ የአይን መቅላት፣ የጿጉርና የልብሳቸው ጠረን መለወጥ፣ የማስታወስ ሁኔታ መቀነስ፣ ባልተለመደ ሁኔታ ቀላል ሥህተቶችን መፈፀም፣ ዘወትር ከሚገኙባቸው ቦታዎች መራቅ፣ ጓደኛ መለወጥ፣ ከዘመድ አዝማድና ቤተሰብ መራቅ ይጀመራል፡፡ ይቀጥላል የድብርት ሥሜት ይንፀባረቃል፣ በእግር ሲጓዙ መድከም፣ እንቅልፍ ማጣት ወይም አብዝቶ መተኛት፣ ለነገሮች ምላሽ ለመስጠት መዘግየት፣ ከምክንያታዊነት መውጣት ወይም ምክንያታዊ መሆን አለመቻል፣ የንግግር ሁኔታ መፋለስ፣ የአፍ ጠረን መለወጥ፣ የጥርስ መበላሸት፣ ዘወትር የሚያከናውኗቸውን ጉዳዮች ከማድረግ መሥነፍ ወዘተ፡፡
እንዲህ ይላል አንድ ሰው ቀልቡ መለስ ሲልለትና የሆነውን ሁሉ መለስ ብሎ ለማሰብ ሲሞክር “ይነጋል ይመሻል እኔ ግን የጊዜ ልዩነት አይገባኝም... ብቻ የምፈልገው ነገር ወዳለበት እየተንሰፈሰፍኩ እከንፋለሁ፣ አገኛዋለሁ እየተንሰፈሰፍኩ እወስደዋለሁ፣ እወጣለሁ፣ እሞቃለሁ እንደገና እወርዳለሁ፣ እቀዘቅዛለሁ፡፡ ራሴን መጥላት ጀመርኩ፣ ከጓደኞቼ ከቤተሰቤ ተለያየሁ፣ እፈራለሁ፣ ሁሉንም ነገር ሁሉንም ሰው እፈራሁ ብቻዬን ቀረሁ...”
አደንዛዥ ዕፅ በአንጎል ውስጥ በተለይ ለማስታወስ በሚረዳን ክፍል ላይ ተፅዕኖ ያሣድራል፡፡ ራሳችንን፣ ዓለምን፣ አካባቢንና ቤተሰብን ያስረሳል ወይም ለእነዚህ ጉዳዮች ቦታ አይሰጡም፣ ሃላፊነት አይወስዱም፣ መደበኛ ሥራቸውን ማከናወን ወደማችሉበት ደረጃም ይደርሳሉ፡፡ ተማሪዎች ከሆኑ ደግሞ የማሪዋና ክፋቱ ለተማሪ የሚያስፈልገውን ዋና ዋና ጉዳዮች ከጉያቸው ይነጥቃል፡፡ ትምህርት ትልቁ የሚሰጠን ወይም የሚያሰለጥነን ነገር በእያንዳንዱ ጉዳይ ላይ ለምን የሚል ጥያቄ እንድናነሳ ነው፡፡ ምክንያታዊ እንድንሆን ምክንያት (reason) እንድንጠይቅ ምክንያት እንድንፈልግ ነው ፡፡ ሆኖም አደንዛዥ ዕፅ ይህን የሚያከናውነውን የአንጎል ሥርዓት ያውከዋል፣ ያዳክመዋል ግለሰቡ ማብሰልሰል ይሳነዋል፡፡ ማሪዋና ተጠቃሚ የሆኑ ተማሪዎች በሂሳብ ትምህርት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየደከሙ ይሄዳሉ፣ ገለፃ በሚያስፈልጋቸው የትምህርት አይነቶች ራስን ወይም የተረዱትን፣ ያነበቡትን ወይም ያጠኑትን ጉዳይ መግለፅ ያቅታቸዋል ይዘበራርቃሉ፡፡ የተማሩትን ወይም ያጠኑትን መግለፅ አለመቻል ብቻ ሳይሆን ማስታወስ ሁሉ አይችሉም፡፡ የማስታወሰና የትኩረት ጉዳይ ከቀነሰ፣ ለምን ወይም አመክንዮ (reasoning) ከጠፋ፣ ማብላላትና የተወሳሰቡ ቀመሮችን መፍታት ካልተቻለ የመማር ጉዳይ አከተመለት ማለት ነው፡፡ ትምህርት ይቆማል ሥራም ከሆነ እነዚህ መሰረታዊ ጉዳዮች ከሌሉ ጠረጴዛህን እንኳን ለማፅዳት እድል ሳታገኝ እንደወጣህ ትቀራለህ፡፡
አእምሮ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ይቀጥላል ማሪዋና የሚወስዱ ሰዎች የጊዜ ቀመር ግንዛቤ አይኖራቸውም፣ የማገናዘብና የሁኔታዎችን ሚዛን መጠበቅ ያቅታቸዋል ለምሳሌ መኪና በሚያሽከረክሩበት ጊዜ የትራፊኩን እንቅስቃሴ መመዘንና (balance) መቆጣጠር አይችሉም፣ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ሲፈፅሙ (ችለው ካደረጉት) የሚራመዱት ሳያገናዝቡ ይሆናል፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካን ሀገር (ለመጥፎውም ለመልካሙም ምሳሌአችን በሆነችው) በድንገተኛ የህክምና ክፍል ውስጥ በየእለቱ ከሚገኙ ታካሚዎች አብዛኛቹ በአልኮልና አደንዛዥ ዕፅ ምክንያት የደነዘዙ ወይም በዚህ ምክንያት አደጋ የደረሰባቸው ግለሰቦች ሲሆኑ በወንጀል ተጠርጥረው ከሚታሰሩ ወንዶች 40 በመቶ ያህሉ የማሪዋና ሱሰኞች ናቸው፡፡ ማሪዋናን ለመጀመር የሚቀለውን ያህል ለመተው መንገዱ ሰፊ ሥላልሆነ እነዚህ ሰዎች ታስረውም ቢሆን አለት ተደርምሶም ይሁን ማሪዋና ወዳሉበት እሥር ቤት እንዲደርስ ያደርጋሉ፡፡ ይህን ወሬ እንሰብስበውና የበዓል ሰው ይበለን፡፡
እንደዋዛ በትንሹ ይጀመራል ያነቃቃል፣ የመሰልጠን የማወቅ መስመር የገባን ይመስለናል፣ መጠኑ ከፍ ይላል (ሱስ ነውና ማለቱ አይቀርም) መቃዥትም መንቀዥቀዥም ይቀጥላል፣   መጠኑ ይበዛል አእምሮም አካልም ይፈዛል፣ ይደነዝዛል ወደ መመረዝና መመረዝ (አንዱ ላልቶ አንዱ ጠብቆ ይነበብ) ድረስ ይዘለቃል፡፡ ያሉበትን መርሳት፣ የሆኑትን አለማወቅ፣ አካልንና አእምሮን አለማዘዝ፣ ድብርት፣ የእንቅልፍ ችግር፣ የወሲብ ጓደኛን ማብዛት፣ ጥንቃቄ አለማድረግ የመሳሰሉት በአብዛኞቹ ላይ የሚታዩ ናቸው፡፡ የማሪዋና ክፋቱ ወይም ሃይሉ ደግሞ ቀደም ሲል እንዳወጋነው መርዙን በሰውነት ውስጥ ተክሎ መርጨቱና ብዙ መቆየቱ ነው፡፡ ለምሳሌ በአልኮል መጠጥ ውስጥ አንድ ንጥረ ነገር ይኖራል (ethanol) በማሪዋና ውስጥ ግን 400 የሚደርሱ ንጥር ነገሮች ይኖራሉ፡፡ በአልኮል ውስጥ ያለው ንጥረ ነገር በሰውነት ውስጥ ለሰዓታት የመቆየት አቅም ሲኖረው፤ በማሪዋና ውስጥ ያለው ግን ለሳምንታት ከዚያም በላይ ለወራት ይዘልቃል፡፡ እንደተወሰደው መጠን ሁለቱን ወይም ሲጋራን ጨምሮ ሦስቱን ቀይጠው ወይም ቀላቅለው በሚወስዱ ሠዎች ላይ ደግሞ የአእምሮ ድንዛዜ ከፋ አለ ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ብዙ የማሪዋና ሱሰኞች ሲጋራና አልኮል ተጠቀሚዎች ናቸው፡፡
ማሪዋና ተጠቃሚዎች በቀላሉ ለቀላል በሽታዎች ሁሉ ይጋለጣሉ፣ በሽታን የመቋቋሚያ አቅም ያንሳቸዋል፣ በወንዶች ላይ በዘር ፈሣሽ ውስጥ የሚገኙ ህዋሳትን (Cells) ያንኮላሻል ለዚህም ትንሿ መጠን በቂ ልትሆን ትችላለች፡፡ በዚህ ወቅትም ይህ የዘር ፈሣሽ ዘር የመተካት አቅም አይኖረውም፡፡ በሴቶች ላይ የወር አበባ ዑደትን ያውካል፡፡ ማሪዋና ተጠቃሚ ከሆኑ ሰዎች የሚወለዱ ህፃናት ከመደበኛው ጊዜ ቀድመው ሊወለዱ፣ ክብደታቸው በጣም አነስተኛና የሚወለዱት ልጆች ለአካላዊ ችግር የተጋለጡ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሌላ ሌላውን ቁጥር ትተን ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ በአለማችን ማሪዋናን የሚያመርቱ ሠዎች ቁጥር በአስር እጥፍ ጨምሯል ተጠቃሚዎችስ?
የማሪዋና ችግር አካላዊ ከሆነው ባሻገር በሥነ ልቦና በኩልም በድብርት፣ በጭንቀትና በፍርሃት ስሜቶች ብቻ አይቆምም፣ ሱሱ እየበዛና እየቆየ ሲሄድ ግለሰቦቹ ራስን የመጥላትና ራስን የመግደል ሙከራ ውስጥ ይገባሉ (ራሱን ለመግደል ሙከራ የሚያደርግ ማንኛውም ሰው እርዳታ ካላገኘ ራሱን ማጥፋቱ የሚጠበቅ አደጋ ነው) ጥናቶች ተሰብስበው ማጠቃለያ (Review) ተዘጋጅቶላቸው በ2002 ለአሜሪካን ሴኔት የህግ ክፍል የቀረበ መረጃ (Physiological and effect of cannabis ለዚህ ፀሁፍ መነሻ ሆኗል፡፡ እንደውልላችሁ ለምትሉ አንባብያን 0115159126 ተጨማሪ ስልካችን ነው፡፡

Read 3548 times