Print this page
Monday, 14 April 2014 10:32

በዓለም አትሌቲክስ ኢትዮጵያዊ ሪከርዶች እንደተያዙ ይቆያሉ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

      በዓለም  የአትሌቲክስ  ስፖርት  በረጅም ርቀት፤ በጎዳና ላይ ሩጫ እና በቤት ውስጥ ውድድሮች በኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተያዙ የዓለም ሪከርዶች የሚሰበሩበት እድል እየተመናመነ መምጣቱን የተለያዩ ጥናቶች አመለከቱ።  በተለይ በረጅም ርቀት በወንዶች   10ሺ ሜትር እና በሁለቱም ፆታዎች በ5ሺ ሜትር በኢትዮጵያውያን የተመዘገቡት 3 ሪከርዶች በመላው ዓለም ውድድሮቹ ካለመካሄዳቸው በተያያዘ የሪከርድ ሰዓቶቹ በቅርብ ዓመታት መሻሻላቸው ያጠያይቃል ተብሏል፡፡ ቀነኒሳ በቀለ  በ5ሺ እና 10ሺ ሜትር ውድድሮች ያስመዘገባቸው ሁለት የዓለም ሪከርዶች ሳይሰበሩ 10 ዓመታት ያለፏቸው ሲሆን ፤ አትሌቱ በተመሳሳይ ርቀቶች በዓለም ሻምፒዮና የኦሎምፒክ  መድረኮች ያስመዘገባቸውን ሪከርዶች  እንደተቆጣጠረ ነው፡፡  በሌላ በኩል በሴቶች 5ሺ ሜትር ውድድር ጥሩነሽ ዲባባ የያዘችው ክብረወሰን ከተመዘገበ 6 ዓመታት ያለፉት ሲሆን አትሌቷ በረጅም ርቀት በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና ያስመዘገበቻቸው ሪከርድ ሰዓቶች የከፍተኛ ብቃት መለኪያ እንደሆኑ ቀጥለዋል፡፡  በአትሌቲክስ ውድድሮች ሪከርዶችን ካስመዘገቡ የኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል ለ20 አመታት ባሳለፈው የሩጫ ዘመኑ ከ27 በላይ ሪከርዶችን ከ2 ማይል እስከ ማራቶን ባሉ ርቀቶች በማስመዝገብ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ከሳምንት በኋላ 41ኛ ዓመቱን የሚይዝ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ከትራክ ውጭ በተደረጉ ውድድሮች የተመዘገቡ  ከ3 በላይ የአለም ሪከርዶችን እንደያዘ ነው። በሴቶች 5ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በኦሎምፒክ እና በዓለም ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት ያላት መሰረት ደፋር በ5 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ያስመዘገበችው ሪከርድ ያልተሰበረ ሲሆን በዓለም የቤት ውስጥ ውድድሮች በ1500 እና በ3ሺ ሜትር የነበሩ ሪከርዶችን ባለፉት 3 እና 4 አመታት እንደተቆጣረች ቆይታ ዘንድሮ የተሰበረባት በኢትዮጵያዊቷ ገንዘቤ ዲባባ ነው፡፡ ገንዘቤ ዲባባ ዘንድሮ በ1500ሜና በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች እንዲሁም በ2 ማይል ሩጫ ሶስት የዓለም ሪከርዶችን የጨበጠች ሲሆን  በተለይ ሰሞኑን በአይኤኤኤፍ ማረጋገጫ ያገኘችበት የ3ሺ ሜትር ው ሪከርድ በድጋሚ ለመሰበር ቢያንስ 5 አመታትን እንደሚፈጅ ይገለፃል፡፡
በተለያዩ ጊዜያት የተሰሩ ጥናቶችን በመዳሰስ ለመረዳት እንደተቻለው በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚካሄዱ የአትሌቲክስ ውድድሮች ከ100 ሜትር እስከ ማራቶን ርቀቶች በየጊዜው ሪከርዶችን በማሳካት የሚሆንላቸው አትሌቶች ከተወሰኑ አገራት የሚገኙ ናቸው፡፡ በመካከለኛና ረጅም ርቀት ሩጫዎች የኢትዮጵያ እና የኬንያ አትሌቶችን  የውጤት የበላይነትና የሪከርድ ባለቤትነት ላለፉት 20 አመታት የሚቀናቀን ጠፍቷል፡፡ በአጭር ርቀት ውድድሮች ደግሞ የጃማይካ እና የአሜሪካ አትሌቶችን ስኬት የሚስተካከል አልተገኘም።  ከላይ ከተጠቀሱት አራት  አገራት የሚወጡ አትሌቶች በአትሌቲክስ ውድድሮች ያስመዘገቧቸው ሪኮርዶችን የማሻሻሉ እድል በየዓመቱ በ0.5 በመቶ እንደተወሰነ በጉዳዩ ላይ ስፖርትሳይንቲስትስ የተባለ ድረገፅ የሰራው ትንታኔ አመልክቷል፡፡  የላቀ ብቃት፤ የላቀ ፍጥነት እና የላቀ ጥንካሬ በሚለው የኦሎምፒክ መርህ  መሰረት የእነዚህ 4 አገራት ምርጥ አትሌቶች በአትሌቲክስ ስፖርት በሰው ልጅ ተፈጥሯዊ ብቃት ሊሳካ የሚችለውን የሪከርድ አቅም 99 በመቶ አሟጥጠውታል የሚል ድምዳሜን የስፖርትሳይንቲስት ባለሙያዎች በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ በስፖርቱ አለም የ147 ውድድሮች ሪከርድ በሰው ልጅ ብቃት ሊመዘገብ የሚችለው ማጣርያ በ2027 እኤአ  እንደሚያበቃ ያረጋገጡ ጥናቶች አሉ፡፡ አይኤንኤስኢፒ የተባለ እና በፓሪስ ተቀማጭ የሆነ የስፖርት ኢንስቲትዩት በሰራው ጥናት አረጋግጧል።  በአሁኑ ወቅት በስፖርቱ አለም በተለይ በአትሌቲክስ ውድድሮች ሪከርዶችን ለማስመዝገብ እጅግ ወሳኝ ከሆነው ተፈጥሯዊ ክህሎት ባሻገር፤ ለፍጥነት የሚመደቡ አሯሯጮች፤ በቴክኖሎጂ የታገዙ የመሮጫ ጫማዎች፤ ዘመናዊ ህክምናዎች እና መድሃኒቶች፤ እጅግዘመናዊ የስልጠና፤ የአመጋገብ እና የስነልቦና ዝግጅቶች እንዲሁም በስኬት  የሚገኝ ገቢ አስፈላጊ ይሆናሉ፡፡ በዘመናችን በህክምና ረገድ ያሉ አገልግሎቶች እና መድሃኒቶች አትሌቶች ለረጅም ጊዜ እየተወዳደሩ በመቆየት ካላቸው ልምድ ሪከርዶችን የመስበር እድላቸውን ከማስፋቱም በላይ፤ ከጉዳቶች ሙሉ ለሙሉ ለመዳንና ለማገገም በሚኖራቸው እገዛ ስፖርተኞች ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ በሌላ በኩል እንደ ጂን ቴራፒ አይነት ዘመናዊ ህክምናዎች ስፖርተኞች በጡንቻዎቻቸው አላግባብ ጉልበት የሚያፈሱበትን ሁኔታ እና ድክመታቸውን በመፈወስ ብቃታቸውን ያግዛል፡፡ በአጠቃላይ የአትሌቶች ብቃት እያደገ ሲቀጥል፤ የቴክኖሎጂ እና የሳይንስ ድጋፍ እየመጠቀ ሲሄድ በርካታ የአትሌቲክስ ሪከርዶች መሻሻላቸው አይቀርም፡፡ በእርግጥ  በዓለም የአትሌቲክስ ውድድሮች በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ መድረክ  የወርቅ ሜዳልያዎችን ከማግኘት በላቀ ሁኔታ እንደከፍተኛ ስኬት የሚቆጠረው ሪከርዶችን ማስመዝገብ ነው፡፡ ለምን ቢባል  የየትኛውንም የአትሌቲክስ ውድድር ሪከርድ ማስመዝገብ በውድድር አይነቱ ያለተቀናቃኝ የበላይነት መያዝ መቻሉን የሚያረጋግጥ ስኬት በመሆኑ ነው፡፡ ሪከርዶች የሩጫ ውድድሮችን የፉክክር ደረጃ ከማሳደጋቸውም በላይ ለተመልካቾች የማይረሳ ልዩ ስሜት በመፍጠርና የስፖርቱን ተወዳጅነት በመጨመር አስተዋፅኦ አላቸው፡፡  ሪከርድ የሚያስመዘገቡ አትሌቶች በተለያዩ የውድድር የቦነስ ሽልማቶች ይጠቀማሉ፡፡ የትጥቅ እና የመሮጫ ጫማዎችን በሚያቀርቡላቸው ስፖንሰሮች ተጨማሪ ክፍያ እና የገቢ እድል ይፈጠርላቸዋል፡፡ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በሚካሄዱ ውድድሮች በቀጥታ ተጋባዥ የሚሆኑበትንም እድል ያገኛሉ፡፡
ባለፉት 15 አመታት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከ1500 ሜትር እስከ ማራቶን፤ ከ2 እስከ 10 ማይል ፤ በተለያዩ የጎዳና ላይ ሩጫዎች እንዲሁም ከ2ሺ  እስከ 5ሺ ሜትር በሚደረጉ የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ውድድሮች በአሸናፊነት ፍፁም የበላይነት በማሳየት እና ሪከርዶችን በማስመዝገብ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር (አይኤኤኤፍ) በአሁኑ ወቅት በአትሌቲክስ ስፖርቶች 53 ሪከርዶች ተመዝግበዋል፡፡ አይኤኤኤፍ በትራክ ላይ የሚደረጉ የሩጫ ውድድሮችን ሪከርዶች በኦፊሴላዊ ደረጃ መመዝገብ የጀመረው በ1912 እኤአ ሲሆን ቤት ውስጥ የአትሌቲከስ ውድድሮች ደግሞ ከ1987 እኤአ ወዲህ እውቅና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡  በትራክ ላይ የሩጫ ውድድሮች  አይኤኤኤፍ  በወንዶች ከመዘገባቸው ሪከርዶች መካከል አራቱ በሁለቱ የኢትዮጵያ አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ኃይሌ ገብረስላሴ ሲያዙ፤ በሴቶች ደግሞ ሶስት ሪከርዶች ሁለቱ በጥሩነሽ ዲባባ እንዲሁም አንደኛው በድሬ ቱኔ እንደተያዙ ናቸው።  በዓለም የቤት  ውስጥ የአትሌቲክስ ውድድሮች ደግሞ በወንዶች ቀነኒሳ በቀለ በ5ሺ ሜትር ሪከርድ ሲኖረው፤ በሴቶች ምድብ የተመዘገቡት ሶስት ኢትዮጵያዊ ሪከርዶች ደግሞ ዘንድሮ  በገንዘቤ ዲባባ አማካኝነት በ1500 ሜትር እና በ3ሺ ሜትር የተያዙትና  በመሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር ያስመዘገበችው ናቸው፡፡  ከዚህ በታች በዓለም የአትሌቲክስ ስፖርት የኢትዮጵያ አትሌቶች ያስመዘገቧቸው የዓለም፤ የዓለም ሻምፒዮና እና የኦሎምፒክ እና የልዩ ልዩ ውድድሮች ሪከርዶች ተቀነጫጭበው ቀርበዋል፡፡
ኢትዮጵያዊ የዓለም ሪከርዶች
በ5ሺ ሜትር የትራክ ውድድሮች  በሁለቱም ፆታዎች  የዓለም ሪከርዶች በኢትዮጵያውያን የተያዙ ናቸው፡፡ በወንዶች 5ሺ ሜትር  ከ1884 እኤአ ጀምሮ 37 ሪከርዶች ተመዝግበዋል፡፡ በዚህ የሪከርድ መሻሻል ሂደት 5 ጊዜ ኢትዮጵያን ስድስት ጊዜ ደግሞ ኬንያውያን አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ ከ1994 እስከ 1998 እኤአ ድረስ ለአራት ጊዜያት የ5ሺ ሜትር ሪከርዶችን በማሻሻል ከፍተኛውን ድርሻ የተወጣ አትሌት ነበር፡፡  በ2004 እኤአ በሆላንድ ሄንግሎ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በ12 ደቂቃ ከ37.35 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ሪከርድ ግን ላለፉት 10 ዓመታት ሳይሰበር የቆየ ነው፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ5ሺ ሜትር ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ ከ14 ዓመታት በኋላ 12 ደቂቃ ከ09.39 እንዲሁም ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 11 ደቂቃ ከ56.19  ሰኮንዶች ሊሆን እንደሚችል ሲገመት 11 ደቂቃ ከ11.61 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡ በሌላ በኩል በሴቶች 5ሺ ሜትር ከ1922 እኤእ ጀምሮ 27 ጊዜ ሪከርዶች ሲመዘገቡ ከ2004 እኤአ ጀምሮ የተመዘገቡ አራት ክብረወሰኖች በትውልድ ኢትዮጵያዊ በሆኑ አትሌቶች አሳክተዋቸዋል፡፡ በ2004 እኤአ የርቀቱን ክብረወሰን 14 ደቂቃ ከ24.68 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ አስመዝግባ የነበረችው በትውልድ ኢትዮጵያዊ ብትሆንም በዜግነት ለቱርክ የምትሮጠው ኢልቫን አብይ ለገሰ ነበረች፡፡ የኢልቫን አብይ ለገሰን ሪከርድ በ2006 እና በ2007 እኤአ አከታትላ ለመስበር የበቃችው ደግሞ መሰረት ደፋር ናት፡፡ ከእሷ በኋላ ላለፉት 6 ዓመታት ሳይሰበር የቆየውን ሪከርድ በ2007 እኤአ በኖርዌይ ኦስሎ በተካሄደ ውድድር 14 ደቂቃ ከ11.15 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በጥሩነሽ ዲባባ  የተመዘገበው ነው፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ5ሺ ሜትር በሴቶች ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ  ከ14 ዓመታት በኋላ 13 ደቂቃ ከ41.56 ሰከንዶች ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 13 ደቂቃ ከ37.25 ሰኮንዶች ሲሆን 12 ደቂቃ ከ33.36 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡
በ10ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በወንዶች  ከ1847 እኤአ ጀምሮ 47 ሪከርዶች ሲመዘገቡ የኢትዮጵያ ሁለት አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ኃይሌ ገብረስላሴ ለአምስት ጊዜያት  የሪከርድ ሰዓቶቹን በማሻሻል አስተዋፅኦ ነበራቸው።  በ2005 እኤአ ላይ ቤልጅዬም ብራሰልስ ላይ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ያስመዘገበው 26 ደቂቃ ከ17.53 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በርቀቱ ላለፉት 9 አመታት ተይዞ የቆየውን ሪከርድ  አስመዝግቧል፡፡ በራንኒንግ ዎርልድ ጥናታዊ ዘገባ በሰው ልጅ ብቃት በ10ሺ ሜትር ሊመዘገብ የሚችለው ሪከርድ  ከ14 ዓመታት በኋላ 25 ደቂቃ ከ32.27 ሰኮንዶች ከ26 ዓመታት በኋላ ደግሞ 25 ደቂቃ ከ04.36 ሰከንዶች ሲሆን 23 ደቂቃ ከ36.89 ሰከንዶች የመጨረሻው የሪከርድ ወሰን ነው፡፡
በዓለም የቤት ውስጥ  የአትሌቲክስ ውድድሮች በወንዶች 5ሺ ሜትር ኃይሌ ገብረስላሴ ለሶስት ጊዜ ሪከርዶች ቢያስመዘግብም አሁን ያለውን ሪከርድ በ2004 እኤአ በእንግሊዝ በርሚንግሃም 12 ደቂቃ ከ49.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በተመሳሳይ በሴቶች የ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር ብርሃኔ አደሬ በ2004 እኤአ፤ ጥሩነሽ ዲባባ በ2005 እና በ2007 እኤአ ካስመዘገቧቸው ሶስት ሪከርዶች በኋላ አሁን ተመዝግቦ ያለውን ሪከርድ ከ2009 እኤአ ጀምሮ ተቆጣጥራ የምትገኘው በስቶክሆልም ርቀቱን በ14 ደቂቃ ከ24.37 ሰኮንዶች የጨረሰችው መሰረት ደፋር ናት፡፡ ዘንድሮ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ውድድሮች ሁለት አዳዲስ ሪከርዶች ያስመዘገበችው ደግሞ ገንዘቤ ዲባባ ናት፡፡ ገንዘቤ በስዊድን ስቶክ ሆልም የ3ሺ ሜትር የዓለም ሪከርድን 8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ከማስመዝገቧም በላይ በካርሉስርህ ጀርመን በተካሄደ የ1500 ሜትር ውድድር ደግሞ ርቀቱን በ3 ደቂቃ ከ55.17 ሰከንዶች የሆነ የሪከርድ ጊዜ አስመዝግባ ማሸነፏ ይታወሳል፡፡
በጎዳና ላይ ሩጫዎች እና በልዩ የአትሌቲክስ ውድድሮች በኢትዮጵያውያን የተመዘገቡ ሌሎች ክብረወሰኖችም አሉ፡፡  ኃይሌ ገብረስላሴ በዚህ ምድብ ሶስት ሪከርዶች ተመዝግበውለታል፡፡ የመጀመርያው በ20ሺ ሜትር የትራክ ውድድር በ2007 እእእ በቼክ ኦስትራቫ 56 ደቂቃ ከ25.98 ሰከንዶች በማስመዝገብ የያዘው  ሲሆን ሌላው ደግሞ በ10 ማይል የጎዳና ላይ ሩጫ  በ2005 እኤአ በቲበርግ ሆላንድ ውስጥ 44 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች የጨረሰበት ናቸው፡፡ በ2007 እኤአ ላይ በቼክ ኦስትራቫ በ1 ሰዓት ውስጥ በሚሸፈን ርቀት የተመዘገቡ ሁለት ሪከርዶችንም ኢትዮጵያውያን አስመዝግበዋል፡፡ ይሄውም በ1 ሰዓት ውስጥ በኃይሌ ገብረስላሴ የተሮጠው 21285 ሜትር እና በድሬ ቱኔ የተሸፈነው 18517 ሜትር ርቀት ናቸው፡፡ በተያያዘ በዓለም ትልልቅ ማራቶኖች የቦታዎቹን ሪከርድ በማስመዝገብ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውን ይፎካከራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ወንዶች  ከተያዙ የትልልቅ ማራቶኖች የቦታ ክብረወሰኖች መካከል ባለፈው ሳምንት ቀነኒሳ በመጀመርያው ማራቶኑ ፓሪስ ላይ  ያሸነፈበት 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ 4 ሰከንዶች፤ በዱባይ ማራቶን በ2008 እኤአ ላይ አትሌት ኃይሌ ያስመዘገበው 2 ሰአት ከ04 ደቂቃ ከ53 ሰከንዶች፤ በኒውዮርክ ማራቶን በ2001 እኤአ ላይ ተስፋዬ ጅፋር በ2 ሰዓት ከ07 ደቂቃዎች ከ43 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የበርሊን፤ የቦስተንና  የሮተርዳምን የቦታ ሪከርዶች ኬንያውያን ይዘውታል፡፡
ኢትዮጵያዊ የዓለም ሻምፒዮና የኦሎምፒክ ሪከርዶች
በዓለም አትሌቲክስ  ሻምፒዮና ላይ በወንዶች ምድብ   ኬንያውያን በ800፤ በ3ሺ መሰናክል፤ በ5ሺ ሜትር እና በማራቶን ያሉ ሪከርዶችን በመቆጣጠር ከኢትዮጵያውያን ይልቃሉ፡፡ በወንዶች ምድብ  በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ  ሪከርድ ይዞ የሚገኝ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ሲሆን በ2009 እኤአ በርሊን ላይ ርቀቱን በ26 ደቂቃ ከ46.31 ሰኮንዶች በመሸፈን ባስመዘገበው ጊዜ ነው፡፡ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ   በሴቶች ምድብ ከተመዘገቡ ሪከርዶች የኢትዮጵያ አትሌቶች በሁለት ውድድሮች ሲጠቀሱ አንዲትም ኬንያዊ አትሌት የለችበትም፡፡ ጥሩነሽ ዲባባ በ5ሺ ሜትር ሴቶች 14 ደቂቃ ከ38.59 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜን  ሄልሲንኪ ላይ በ2005 እኤአ  እንዲሁም በ2003 እኤአ ፓሪስ ላይ ብርሃኔ አደሬ በ10ሺ ሜትር 30 ደቂቃ ከ04.18 ሰኮንዶች በሪከርድ እንደተመዘገበላቸው ነው፡፡ በኦሎምፒክ መድረክ በወንዶች  በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ሁለት ክብረወሰኖችን የያዘው  ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ ቀነኒሳ በቀለ ሁለቱንም የኦሎምፒክ ክብረወሰኖች እኤአ በ2008 በቤጂንግ በተካሄደው 29ኛው ኦሎምፒያድ ሲያስመዘገባቸው በ5 ሺ ሜትር 12 ደቂቃ ከ57.82 ሰኮንዶች እንዲሁም በ10ሺ ሜትር 27 ደቂቃ ከ04.7 ሰኮንዶች የሰፈሩ ናቸው፡፡ ኬንያውያን በ800፤ በ1500፤ በ3ሺ መሰናክልና በማራቶን የተያዙ የኦሎምፒክ ሪከርዶችን በመቆናጠጥ የተሻለ ውክልና አላቸው፡፡ በኦሎምፒክ መድረክ በሴቶች ምድብ በተመዘገቡ ሪከርዶች ኢትዮጵያ በሁለት አትሌቶች ስትጠቀስ ኬንያ ግን አንድም አላስመዘገበችም፡፡ በኢትዮጵያውያን የተያዙት ሁለት የረጅም ርቀት የኦሎምፒክ ሪከርዶች በ2008 እእአ ላይ በቤጂንግ ኦሎምፒክ ጥሩነሽ ዲባባ በ10ሺ ሜትር  29 ደቂቃ ከ54.66 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበችውና በ2012 እኤአ ላይ በለንደን በተካሄደው 30ኛው ኦሎምፒያድ ቲኪ ገላና በማራቶን ስታሸንፍ ርቀቱን የሸፈነችበት 2 ሰዓት ከ23 ደቂቃ ከ07 ሰኮንዶች ናቸው፡፡

Read 3211 times
Administrator

Latest from Administrator