Tuesday, 29 April 2014 12:27

የዞን 9 ፀሐፊዎችና የጋዜጠኞች እስራት አነጋጋሪሆኗል•

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(10 votes)

 ኢትዮጵያ የዓለም     የፕሬስ ነጻነት ቀንን ቅዳሜ ታከብራለች
 
         በተመሳሳይ ሰዓት ከተለያዩ ቦታዎች በፖሊስ ተይዘው ባለፈው አርብ አመሻሽ ላይ የታሰሩት 6 ፀሐፊዎችና 3     ጋዜጠኞች ጉዳይ በአወዛጋቢነቱ በአገር ውስጥና በውጭ የብዙዎችን ትኩረት  የሳበ ሲሆን ፖሊስ የምርመራ ጊዜ  እንደሚፈልግ ለፍ/  ቤት በመግለጹ ለሁለት ሳምንት በእስር  እንዲቆዩ ተወስኗል፡፡ ፖሊስ በምን ጉዳይ ዘጠኙን  ፀሃፊዎችና ጋዜጠኞች እንዳሰራቸው ለፍ/ ቤቱ ሲገልፅ፣   በመብት ተሟጋችነት ከሚታወቅ የውጭ ድርጅት ጋር በሃሳብና  በገንዘብ ተባብረው፣  በኢንተርኔትና ማህበራዊ ድረገፆች አገሪቱን ለማሸበር በመንቀሳቀስ ተጠርጥረዋል ብሏል፡፡

    በመብት ተሟጋችነት የሚጠቀሰው የውጭ ድርጅት ማን እንደሆነ ፖሊስ ባቀረበው መዝገብ  በስም አልሰፈረም፡፡ አገር ለማሸበር ተንቀሳቅሰዋል በሚል እንዲጠረጠሩ ያደረጋቸው   ድርጊት ምን እንደሆነ የሚጠቁም ነገርም  
አልተጠቀሰም ተብሏል፡፡  በተመሳሳይ ጉዳይ ተጠርጥረዋል ተብለው የታሰሩት፣   ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ  ፣  ጋዜጠኛ አስማማው ኃ/ጊዮርጊስ  ፣   ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ፣  እንዲሁም  ዞን ዘጠኝ  በሚል ስያሜ የሚታወቁት  ፀሃፊዎች-  አቤል ዋበላ፣  ዘላለም ክብረት፣  በፍቃዱ ኃይሉ፣  ማህሌት ፋንታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ እና አጥናፉ  ብርሃነ ናቸው፡፡   
     ጋዜጠኞችን በማሰር በተለያዩ ጊዜያት በዓለም አቀፍ የመብት ተከራካሪ ተቋማት   በምትወቀሰው  ኢትዮጵያ ውስጥ ከ 1994 ዓ. ም በኋላ የተወሰነ ያህል መሻሻል ታይቶ የነበረ ቢሆንም የ 1997  የምርጫ  ቀውስን ተከትሎ በርካታ ጋዜጠኞች ታስረው፣  በርካታ ጋዜጦች   መዘጋታቸው ይታወሳል፡፡ ሰሞኑን ጋዜጠኞችና  ፀሃፊዎች አንድ ላይ በብዛት መታሰራቸው    ግን ካለፉት ዓመታት የተለየ ያደርገዋል፡፡   ይህ በእንዲህ እንዳለ  የዓለም የፕሬስ ቀን በአገራችን በኢትዮጵያ የፊታችን ቅዳሜ ይከበራል፡፡

Read 4268 times