Saturday, 03 May 2014 12:01

“የአውሮፓ ቀን” የህፃናት የሩጫ ውድድር ነገ በጃንሜዳ ይካሄዳል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

*ከ2500 በላይ ህፃናት ይሳተፋሉ
የፊታችን አርብ የሚከበረውን “የአውሮፓ ቀን” ምክንያት በማድረግ የህፃናት የሩጫ ውድድር ነገ በጃንሜዳ ይካሄዳል፡፡ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ባዘጋጀው በዚህ ውድድር፤ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች የተውጣጡ ከ2500 በላይ እድሜአቸው ከ14 አመት በታች የሆኑ ህፃናት ተካፋይ ይሆናሉ፡፡
ለዘጠነኛ ጊዜ በሚካሄደው በዚህ ውድድር ተካፋይ የሚሆኑት ህፃናት፤ በአራት የእድሜ ክልል ተመድበው ከአንድ እስከ ሁለት ኪሎሜትር ርቀት የሚሸፍን የሩጫ ውድድር ያካሂዳሉ፡፡ ከዚህ ውድድር ቀደም ብሎ በአለም አቀፍ ት/ቤት ህፃናት ተማሪዎች መካከል የሁለት ኪሎ ሜትር የዱላ ቅብብል ውድድር ይካሄዳል፡፡
የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት ይህን የህፃናት የሩጫ ውድድር የአውሮፓ ቀንን ምክንያት በማድረግ በየአመቱ የሚያዘጋጀው፤ ስፖርት ለአንድ ሀገር እድገት የሚያበረክተውን ከፍተኛ ጠቀሜታ ከግምት ውስጥ በማስገባትና ኢትዮጵያ በአለም አቀፉ መድረክ ወደር የለሽ ክብርና ዝና በተጐናፀፈችበት የአትሌቲክስ ስፖርት ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የምታደርገውን ጥረት በመደገፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት መሆኑን የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት የፕሬስና ኢንፎርሜሽን ኦፊሰር አቶ ሰሎሞን ከበደ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

Read 1601 times