Saturday, 03 May 2014 12:22

እቺ ጎንበስ ጎንበስ ሣር ፍለጋ ሳትሆን ዱባ ለመስረቅ ናት!

Written by 
Rate this item
(3 votes)

ሰውየው ወደ አደን ሊወጣ እየተዘገጃጀ ነው፡፡ መሣሪያ ሲያዘጋጅ፣ ጥይት ሲቆጥር ጥሩሩን (የውጊያ ልብሱን) ሲያጠልቅ፤ ዝናሩን ሲታጠቅ፤ ከአፋፍ ሆኖ የሚያስተውለው ጎረቤቱ፤ “ምን ጉድ መጣ? መጠየቅ አለብኝ ብሎ ወደ ቁልቁል ወረደ፡፡
ታጣቂው ሲወጣ ጎረቤቱ አገኘው፡፡
“እንዴት አደርክ ወዳጄ!” አለ አዳኙ ሞቅ አድርጎ፡፡
“ደህና እግዚሃር ይመስገን! አንተስ እንዴት አድረሃል?”
“ወደ ደጋ ወጥቼ ሠርጉም፣ ልቅሶውም ተደባልቆብኝ፤ እሱን ተወጥቼ መምጣቴ ነው! አሁንኮ ካፋፍ ላይ ሆኜ ቁልቁል ሳስተውል ትጥቅህን ስታዘጋጅ አይቼህ ምን ገጥሞት ይሆን? ብዬ ነው ልጠይቅህ የመጣሁት?” አለው፡፡
“የለም፤ ወደ ጫካ ለአደን እየሄድኩ ነው፡፡”
“ምን ልታድን አስበህ ነው?”
“ነብር”
“ነብር?!” አለ ጎረቤት፤ በድንጋጤ፡፡
“ምነው ደነገጥክ?”
“ነብር አደገኛ ነዋ!”
“ቢሆንም ተዘጋጅቻለሁ፤ አሳድጄ እገድለዋለሁ!”
“ብትስተውኮ አለቀልህ ማለት ነው፡፡ እሺ ብትስተው ምን ይውጥሃል?”
“ከሳትኩማ ወዲያውኑ አቀባብዬ ደግሜ እተኩሳለሁ”
“ሁለተኛ ጊዜ ብትስተውስ?”
“ወዲያው ለሶስተኛ ጊዜ አቀባብዬ ግንባሩን እለዋለሁ!”
“ለሶስተኛ ጊዜ ብትስተውስ?”
“እህ! አንተ ከእኔ ነህ ወይስ ከነብሩ?!”
*      *      *
ነገርን ከአሉታዊ ገፁ አንፃር ብቻ ማየት እጅግ ጎጂ ባህል ነው! ለሀገር ዕድገት ስንል፡፡ ለሀሳብ ነፃነት ስንል፤ በምንደክምበት ረዥም መንገድ ከማን ጋር መጓዝ ተገቢ እንደሆነ ያልለየ ጋዜጠኛ ዓላማና ግቡ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ ነው፡፡ ቢያንስ የቱ ድረስ ተራራውን አብረን እንጓዛለን ማለት ያባት ነው! የሀገር ጉዳይ ከፅሁፍና ከሀሳብ ነፃነት ተለይቶ አይታይም - ዲሞክራሲያዊ አካሄድ አለን የምንል ከሆነ፡፡ የህዝቡን መረጃ የማግኘት ነፃነት ሳናከብር ለሀገርና ለህዝብ ዲሞክራሲያዊ መብቶች እየታገልን ነው ብንል ቢያንስ ወይ ለበጣ ወይ የዋህነት ነው፡፡ ሳይማሩ ማስተማር ለአስተማሪውም ለተማሪውም ኪሳራ አለው፡፡ አመለካከትን ያዛባል፡፡ ጎዶሎ ዕውቀት ሊሆን ይችላል፡፡ የአላዋቂነትን ገደል ያሰፋል፡፡ ውጤቱም-ያልነቃ፣ የማይጠይቅ፣ ለለውጥ ያልተዘጋጀ ህዝብ ይዞ መኖር ይሆናል፡፡ ያ ደግሞ “ባለህበት ሃይ” ወይም “ቀይ ኋላ ዙር” የሚል የሰልፍ ህግ ከማክበር ያለፈ አገራዊ ፋይዳ የለውም፡፡ አርቀን እናስተውል፡፡ የዓለም ኢንፎርሜሽን ቀን፣ የዓለም ላብ አደሮች ቀን፣ የዓለም የሴቶች ቀን፣ የዓለም የጤና ቀን፣ የዓለም የእናቶች ቀን፣ የዓለም የህፃናት ቀን .. ዛሬም የዓለም የፕሬስ ቀን፤ እናከብራለን እንላለን፤ ሁሉም፤ ሀሳብን በነፃ ጋር ቅርብ ቁርኝት ያላቸው የራቁ ፅንሰ-ሀሳቦች ናቸው፡፡
እዚህ ላይ የፈረንሳይ ፈላስፋ ፒየር ጆሴፍ ፕሩዶንን ማስታወስ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም፡- ብዙ ፈላስፎች ህዝብን ለመግዛት በሚፅፉበት ዘመን እሱ ህዝብ ሆነን ስለመገዛት ፅፏል፡- “መገዛት ማለት መታሰብ ማለት ነው፡፡ መታወስ ማለት ነው፡፡ መመዝገብ ማለት ነው፡፡ የመንግስት ቁጥጥር ውስጥ መግባት ማለት ነው፡፡ ተጠያቂ መሆን ማለት ነው፡፡ መለካት ማለት ነው፡፡ ተለይቶ መታየት ማለት ነው፡፡ በኦዲተር መታወቅ ማለት ነው፡፡ የፈጠራ መለያ ማግኘት ማለት ነው፡፡ የንግድ ፈቃድ ማግኘት ነው፡፡ ሥልጣን ማግኘት ነው፡፡ መካተት ነው፡፡ መቀጣት ነው፡፡ መታነፅ ነው፡፡ የእርማት መንገድ ላይ መቀመጥ ነው፡፡ መስተካከል ነው፡፡ ይህ ሁሉ እንግዲህ በየአንዳንዱ ክንዋኔ፣ በየአንዳንዱ ሽያጭና ግዢ እንዲሁም፣ በየአንዳንዱ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚታይ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ መብትን መገፈፍ፣ የመናገር፣ የመፃፍ፣ የመሰብሰብ፣ የመደራጀትን ነፃነት ማጣት፣ አግባብ አይደለም፡፡ ዕውቅና ማጣት መገደብ፣ መገፋት፣ መጣል፣ መረጋገጥ፣ መወገር፣ ወዘተ በኃይል መገዛት ነው፡፡ ያ ደግሞ የዲሞክራሲን ሰፈር አያቅም፡፡
ተገዢዎች ጥበብ እንዳላቸው አንርሳ፡፡ ልምድ እንዳላቸው አንርሳ፡፡ ከትላንት ሊማሩ እንደሚችሉ አንርሳ፡፡ ህዝቦች፤ መማረር፣ መናደድ፣ ማዘን፣ ትተው፤ ዝም ሊሉ እንደሚችሉ አንርሳ፡፡ ዲሞክራሲ ሙልጭ እሚወጣው (Zero Sum) ይሄኔ ነው!
በንፁህ ልቦና የማይሰራ የፕሬስ ሰው ህዝብንም፣ ሙያውንም፣ እራሱንም ይጎዳል፡፡
የፕሬስ ሰው በመደለል አያምንም፡፡ ሥልጣንንም አይቋምጥም፡፡ የኢኮኖሚንም ሆነ የፖለቲካ ሥልጣን ሙሰኞች፤ ስለሐቀኛ ጋዜጠኛ ሲያስቡ የሚጨንቃቸው ለዚህ ነው!
“ተመስጌን ነው!
የእንግሊዝን ጋዜጠኛ
ጉቦ መስጫ፣ ማማለያ
ወይም እጁን መጠምዘዢያ
ቅንጣት ታህል ቦታ የለም!!
ያለጉቦ መስራቱንም
መመልከቻም፣ ጊዜ የለም
መገንዘቢያም፣ ወቅት አደለም!!
ተመስጌን ነው!”
    ይለናል ሐምበር ዎልፍ፤ ጣሊያን የተወለደው እንግሊዛዊ ገጣሚ፡፡
ፕሬስ አጋዤ ነው ብሎ የሚያምን መንግሥት ራሱን ማያ መስተዋት ያገኛል፡፡ ሆደ-ሰፊ አመለካከት፤ አዎንታዊና ገንቢ ምዛኔ ያለው ሥርዓት ጤናማ አገርን ያለመልማል፡፡
“በፕሬስ አትናደድ፡፡ አለበለዚያ አብዛኛው ሥራህ የህዝቡን የፖለቲካ ህይወት ካልገዛሁ ማለት ብቻ ይሆናል፡፡” (ክሪስታቤል ፓንክረስት) ያ ደግሞ የሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ጉዞን ያጨናግፋል፡፡ ጠብታዎችን በሙሉና በጥልቅ ዐይን ማየትና በጊዜ ቦታ ቦታ ማስያዝስ ከብዙ መጪ ጠንቀኛ ዥረቶች ይገላግለናል፡፡
ታሪክ ፀሀፊዎች፤ “በትክክለኛው የታሪክ ወገን መቆም፤ ከዛሬ ጎን ሳይቆሙ ሊደረግ ይችላልን?” በሚለው ጥያቄ ዙሪያ ብርቱ ሙግት ያቀርባሉ፡፡ ነፃ ጋዜጠኛ ግን ይህን ጥያቄ በአዎንታ አይመልሰውም፡፡ ይልቁንም፤ ተጨባጩ ዕውነት ባለበት ቦታ ሁሉ ጋዜጠኛ አለ፤ ይላል፡፡ ምነው ቢሉ፤ የአሜሪካው ፀሐፊና ጋዜጠኛ ሐንተር ቶምፕሰን ነገሩን እንዲህ ይደመድምልናል፡-
“እኔ በአለፉት አሥር ዓመታት የማውቀውን ዕውነት ሁሉ ብፅፍ ኖሮ እኔን ጨምሮ ከሪዮ እስከ ሲያትል ያለው 600 ያህል ህዝብ እስር ቤት ይበሰብስ ነበር፡፡ በጋዜጠኛነት ሙያ ውስጥ፤ ፍፁም ውድና የማይገኝ (rare) እንዲሁም አደገኛ ሸቀጥ (dangerous commodity) ፍፁም እውነት ነው፡፡” ይህ ማለት ግን አንፃራዊ እውነት፣ ተጨባጭ ሁኔታ ላይ የተመረኮዘ መረጃ የለም ማለት አይደለም፡፡ ከላይ ያልነውን ሁሉ ብለን ስናበቃ፤ ስለ ፕሬስና ፕሬስ ሰዎች ለመናገር፣ ከሌላ ዓላማና ግብ አኳያ የተዛባ፣ የተዛነፈ ወይም ፍፁም በሥሃ የተሞላ አመለካከት ይዞ መገኘት፤ “እቺ ጎንበስ ጎንበስ ሣር ፍለጋ ሳትሆን ዱባ ለመስረቅ ናት” ከማለት በቀር ምን ይባላል?!

Read 4733 times