Saturday, 07 June 2014 13:09

ማህበራቱ ለፓትርያርኩ ቅሬታችንን እንዳናቀርብ ተከለከልን አሉ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የሰንበቴ ማህበራቱ በደብረ ምጥማቅ ሰአሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም እና ክርስቶስ ሰምራ ካቴድራል አስተዳደር ላይ ያለንን የመልካም አስተዳደር ቅሬታ ለቅዱስ ፓትርያርኩ እንዳናቀርብ ተከለከልን፤ ለእንግልትም ተዳርገናል አሉ፡፡
በቤተክርስቲያኑ የሚገኙ የሰባት ሰንበቴ ማህበራት ጥምረት ተወካዮች ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ከሌላ ደብር ተቀይረው በመጡ የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደሮች እየተፈፀመብን ነው የሚሉትን በደልና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለቅዱስ ሲኖዶስና ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ከ12 ጊዜ በላይ ቢመላለሱም ጉዳያቸው እልባት አላገኘም፡፡
የማህበሩ አባላትና የደብሩ አጥቢያ ምዕመናን የሚያቀርቡት ጥያቄ በአግባቡ ለፓትርያርኩ አልደረሰም የሚሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ የሰንበቴ ማህበራቱ የመሬት ወረራ እያካሄዱ ነው የሚል የተሳሳተ መረጃ ለፓትርያርኩ መድረሱን ተከትሎ “አስቁሟቸው” የሚል ትእዛዝ መተላለፉን፤ ይህን ትዕዛዝ ተገን በማድረግም ያልተስማሙበትንና የቤተክርስቲያኒቱን ቃለ አዋዲ ያልጠበቀ መመርያ አምጥተው በ3 ቀን ውስጥ ፈርሙ በማለት  የደብሩ ኃላፊዎች እንዳስጨነቋቸው ገልፀዋል፡፡
መመሪያውን በ3 ቀን ውስጥ ፈርሙ የሚለውን ትዕዛዝ በመቃወምም ረቡዕ ግንቦት 27 ቀን 2006 ዓ.ም ለቅዱስ ሲኖዶስ ቅሬታ ለማቅረብ ከ400 በላይ ምዕመናን ወደ ፅ/ቤት ቢያመሩም በደህንነትና በፖሊስ አባላት እንዳይገቡ መከልከላቸውንና የፓትርያርኩ ዋና ፀሐፊ “ከእናንተ መሃል 10 ሰው ብቻ በነገው እለት (ሃሙስ) ጥያቄያችሁን ይዞ ይቅረብ” በሚል እንዳሰናበቷቸው የቅሬታ አቅራቢዎቹ ተወካዮች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
በቀጠሮው መሰረት ከትናንት በስቲያ ሃሙስ፣ ለፓትርያርኩ የሚቀርብ የአቤቱታ ደብዳቤ ይዘው ቢሄዱም  የሚያስተናግዳቸው አካል ማጣታቸውን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ጠቁመው፣ በተደጋጋሚ የፓትርያርኩ በር ቢዘጋብንም ቤተክርስቲያኒቱን ከጥፋት ለመታደግ አሁንም በድጋሚ ጥያቄያችንን ይዘን እንቀርባለን ብለዋል፡፡

Read 1954 times