Saturday, 14 June 2014 12:09

ሲጋራ የውበትና የገፅታ፣ የስያሜና የአርማ እገዳ ተጣለበት

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ጤናንና ህይወትን ለመታደግ ነው ተብሏል
ሲጋራ ማጨስ ለከፍተኛ የጤና አደጋ፣ ባስ ሲልም ለህልፈት እንደሚዳርግ ማንም ሊክድ አይችልም። እንዲያም ሆኖ ከወደ አየርላንድ የተሰማው አዲስ እገዳ ክፉኛ ያስደነገጠው ከአጫሾች ይልቅ የትምባሆ ኩባንያዎችን ነው። ሰሞኑን አየርላንድ ማንኛውም ሲጋራ ስያሜ፣ የንግድ ምልክትና አርማ እንዳይኖረው የሚያግድ ህግ  አውጥታለች፡፡ እገዳው ሲጋራዎች ላይ ብቻ ግን አይደለም፤ የሲጋራ ፓኮዎችም ያለምንም ፅሁፍና ምልክት ለገበያ እንዲቀርቡ ህጉ ያስገድዳል። አዲሱ ህግ የትምባሆ ኩባንያዎችን ቢያስከፋም የአየርላንድ የጤና ሚኒስትር ጄምስ ሬይሊ፤ እገዳው የብዙዎችን ህይወት ለመታደግ ያግዛል ብለዋል፡፡
የምርት ስያሜ፣ የንግድ ምልክትና አርማ ያለው ሲጋራ ለሸማቶች እንዳይቀርብ የሚያግድ ህግ በማጽደቅ አየርላንድ በአውሮፓ የመጀመሪያዋ አገር ናት ተብሏል፡፡
አውስትራሊያ ተመሳሳይ እገዳ በሲጋራ ላይ በመጣል ከዓለም የመጀመሪያዋ አገር ስትሆን ኒውዚላንዶች ደግሞ በረቂቅ ህጉ ላይ እየተከራከሩ እንደሆነ ታውቋል፡፡ እንግሊዝን ጨምሮ ሌሎች የአውሮፓ አገራት እገዳው በህግ የመውጣቱን አስፈላጊነት ገና እያጤኑት ነው ተብሏል፡፡
የአየርላንድ ጤና ሚኒስትር በሰጡት መግለጫ፤ “የህጉ ዓላማ የሲጋራ ፓኮዎች ለሸማቾች ያላቸውን ማራኪነት በመቀነስ፣ በጤና ላይ የሚያደርሱትን አደጋ ማጉላት ነው፡፡ ፓኬቶች ሰዎችን በተለይ ህፃናትን የማሳሳት አቅማቸውን በመቀነስ የማጨስ ጐጂነትን እንዲገነዘቡ እናደርጋለን” ብለዋል፡፡
የትምባሆ ኩባንያዎች ግን እገዳውን አጥብቀው ተቃውመዋል፡፡ የትምባሆ ምርቶችን ስያሜና አርማ አልባ አድርጐ ማቅረብ፣ ሃሰተኛ የሲጃራ ምርቶችን የሚያመርቱ ወንጀለኞችን የሚያግዝና የሚያበረታታ ነው ብለዋል - ኩባንያዎቹ፡፡
ቤንሰን ኤንድ ሄጅስ እና ደንሂል በሚሉ ስያሜዎች የሚታወቁት ሲጋራዎች ባለቤት የሆነው የብሪቲሽ አሜሪካን ቶባኮ (BAT) ቃል አቀባይ እንደተናገሩት፤ የአየርላንድ ካቢኔ ረቂቅ ህጉን ማጽደቁ አሳዝኗቸዋል።
“ምንም ፅሁፍ ያልሰፈረበት ሌጣ ፓኬት፣ ታዳጊዎች ሲጋራ እንዳይጀምሩ ወይም አጫሾች ማጨስ እንዲያቆሙ ስለማድረጉ ተዓማኒ ማስረጃ የለም” ሲል ተሟግቷል  ተቋሙ፡፡
በቅርብ ዓመታት ሲጋራ ማጨስ በህብረተሰቡ ላይ የጋረጠውን አደጋ ለመቅረፍ የሚያስችል ውይይት ያደረገችው አየርላንድ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም በስራ አካባቢ ሲጋራ ማጨስን ሙሉ በሙሉ የሚያግድ ህግ በማውጣት በዓለም የመጀመርያው አገር ሆናለች፡፡ በሥራ አካባቢ ሲጋራ ማጨስ የሚከለክለው ህግ መሸታ ቤቶችንና ክለቦችንም እንዳካተተ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እንዲያም ሆኖ ታዲያ የህጉ ተፈፃሚነት 97 በመቶ እንደተሳካ ተገልጿል፡፡

Read 2237 times