Saturday, 14 June 2014 12:17

ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ኢስተር ራዳ ከአመቱ 50 የዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ አይሁዳውያን አንዷ ሆነች

Written by 
Rate this item
(2 votes)

      የእስራኤል ፕሬዚዳንት፣ ጠ/ሚንስትር፣ የገንዘብ ሚ/ር እና የኢኮኖሚ ሚ/ር በዝርዝሩ ውስጥ ተካተዋል
ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ ታዋቂ ድምጻዊት ኢስተር ራዳ፣ ‘ዘ ጀሩሳሌም ፖስት’ ጋዜጣ የአመቱ የዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ አይሁዳውያን ብሎ ከመረጣቸው 50 ታዋቂ ግለሰቦች መካከል አንዷ ሆነች፡፡
በሶል፣ በአር ኤንድ ቢ እና በፋንክ ስልቶች የተቃኙና የኢትዮ-ጃዝ ቃና ያላቸው ሙዚቃዎችን የምትጫወተውና “የእስራኤል የሶል ሙዚቃ ንግስት” በመባል የምትጠራዋ ኢስተር ራዳ፣ በእስራኤል ብቻም ሳይሆን በመላ አለም በርካታ አድናቂዎችን ማፍራት የቻለች ድምጻዊት መሆኗን ‘ዘ ጀሩሳሌም ፖስት’ ባለፈው ሰኞ ይፋ ባደረገው መረጃ መስክሮላታል፡፡
ጋዜጣው ተስፋ ከሚጣልባቸውና ከፍተኛ ስኬት ካስመዘገቡ የዘመኑ ተጠቃሽ ቤተ እስራኤላውያን አርቲስቶች ተርታ ትሰለፋለች ያላት ይህቺ ድምጻዊት፣ በተለያዩ ጊዜያት በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ ስኬታማ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን ማቅረቧንና፣ ኢትዮጵያዊ ቅኝት ያላቸውን ሙዚቃዎች እንደምትጫወትም ገልጧል፡፡
በሙዚቃው ዘርፍ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ማፍራትና ለኤምቲቪ አውሮፓ የሙዚቃ ሽልማት እስከመታጨት የደረሰችው ኢስተር ራዳ፣ ‘ኪሮት’ እና ‘ስቲል ዎኪንግ’ን በመሳሰሉ ፊልሞች፣ ሙዚቃዊ ቲያትሮችና ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች ላይ በተዋናይነት በመስራት ድንቅ የትወና ክህሎቷን አስመስክራለች፡፡
በተለያዩ የአለም ክፍሎች የሚኖሩ ፖለቲከኞች፣ ተመራማሪዎች፣ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች፣ ስራ ፈጣሪዎች፣ ቢሊየነሮች፣ አርቲስቶችና በሌሎች ሙያዎች ላይ ተሰማርተው ውጤታማ መሆን የቻሉ ግለሰቦችን በዘንድሮው የአመቱ 50 የአለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ አይሁዳውያን ዝርዝር ውስጥ ያካተተው ዘ ጀሩሳሌም ፖስት፤ ከእነዚህም ውስጥ ኢስተር ራዳን ጨምሮ 15 ያህሉ ሴቶች መሆናቸውን ይፋ አድርጓል፡፡
ካቻምና በእስራኤል ጠ/ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ፣ አምና ደግሞ በገንዘብ ሚንስትሩ የር ላፒድ ተይዞ የነበረውን የዚህ  ዝርዝር መሪነት፣ ዘንድሮ የአሜሪካ ትሬዠሪ ጸሃፊ የሆኑት ጃክ ሊው ተረክበውታል፡፡ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ቁልፍ ሚናን በሚጫወተው በዚህ ዘርፍ ውስጥ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ የሚገኙት እኒህ ሰው፣ በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አስተዳደር ውስጥ ተጽዕኖ መፍጠር የቻሉ ተሰሚ ሰው እንደሆኑ ጋዜጣው ዘግቧል፡፡
በተጽዕኖ ፈጣሪነት ሁለተኛውን ደረጃ የያዙት አሜሪካዊቷ ቤተ እስራኤላዊ ጃኔት የለን ሲሆኑ፣ የአሜሪካን ተቀማጭ ገንዘብ ተቋም እንዲመሩ በመመረጥ በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያዋ ሴት ናቸው፡፡ እሳቸውን ተከትለው በዝርዝሩ የተካተቱት፣ ቤኒያሚን ኔታኒያሁ (የእስራኤል ጠ/ሚንስትር) እና ሽሞን ፔሬዝ (የእስራኤል ፕሬዚዳንት) ናቸው፡፡
አቪግዶር ሊበርማን (የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር)፣ የር ላፒድ (የእስራኤል የገንዘብ ሚንስትር) እና ናፋታሊ ቤኔትም (የእስራኤል የኢኮኖሚ ሚንስትር)፣ በዘንድሮው ተጽዕኖ ፈጣሪ ቤተ እስራኤላውያን ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱ ታዋቂና በአለም አቀፍ ደረጃ ተጽዕኖ መፍጠር የቻሉ ግለሰቦች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

Read 4147 times