Saturday, 28 June 2014 13:01

እንደ ንጉስ የኖሩት ተራማጁ ፊደል ካስትሮ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ታጋዮች የህዝብ ጫማ ናቸው፤ ታጋዮች የግል ጥቅምና ምቾታቸውን በሰፊው ህዝብ ጥቅምና ምቾት የቀየሩ የህዝብ መድህኖች ናቸው፤ ታጋዮች ለህዝባቸው ምቾትና ድሎት ሲሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚከፍሉ የህዝብ ቤዛዎች ናቸው፡፡…
እነዚህን የመሳሰሉ የአብዮታውያን የፕሮፓጋንዳ ርግረጋዎች የኢትዮጵያ አብዮት በግብታዊነት ፈነዳ ከተባለበት ከየካቲት 1966 ዓ.ም ጀምሮ አብዮታዊና ተራማጅ ነን ከሚሉ ሃይሎች ዘንድ ስንሰማው የኖርነውና ዛሬም እየሰማነው ያለነው ጉዳይ ስለሆነ ምንም አስደናቂ ነገር የለውም፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ይህ የአብዮታውያኑ መሀላ፣ የታጋዮቹን ሰውነትና የሰውን ልጅ ባህርይ በወጉ ከግምት ውስጥ ያስገባ አይደለም፡፡ እናም ነገሩ አብዛኛውን ጊዜ የሚባለውን ያህል ትክክል ወይም እውነት ሆኖ አይገኝም፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ደግሞ ማስረጃ ፍለጋ የአለም አብዮተኞችን የታሪክ መዝገብ ማገላበጥ ጨርሶ አያስፈልገንም፡፡ የሀገራችን አብዮተኞች ታሪክ ከበቂ በላይ ነው፡፡
የጊዜያዊ ወታደራዊ መንግስት መሪዎች በስልጣን ላይ በቆዩበት አስራ ሰባት አመታት ሰፊውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከአስከፊ ድህነት ለማላቀቅ ሲሉ አንድም ቀን እንኳ ሳይደላቸውና ሳይስቁ ከፍተኛ መስዋዕትነት ይከፍሉ እንደነበር በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር፡፡ እነዚህ አብዮታውያን ወታደራዊ መሪዎች በተግባር ያደረጉት ግን ካለፈው እጅግ የከፋ ድህነትን ለሰፊው ህዝብ እኩል በማካፈል፣ ራሳቸውንና የራሳቸውን ወገን ከድህነት ማላቀቅ ነው፡፡
“አብዮታዊውን” ወታደራዊ መንግስት ለአስራ ሰባት አመታት በዘለቀ የትጥቅ ትግል የዛሬ 23 አመት አሸንፎ ስልጣን የተቆጣጠረው ኢህአዴግ፣ ተራራ ያንቀጠቀጡት ታጋዮቹ በግል ጥቅምና ምቾት የማይንበረከኩ፣ የህዝብ ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና የመጀመሪያም የመጨረሻም የትግል ግባቸው እንደሆነና ለዚህም ግብ መሳካት የህይወት መስዋዕትነት እንደከፈሉ በተደጋጋሚ ሊያስረዳን ሞክሯል፡፡
ጥረቱ ያላቋረጠና ከባድ መሆኑ ሲታይ ደግሞ ኢህአዴግም እንደሌሎቹ አብዮታዊ ድርጅቶች ሁሉ የታጋዮቹን ሰውነት ጨርሶ የረሳ አስመስሎት ነበር፡፡ የማታ ማታ በተግባር የታየው ግን በቃል ከተወራው በእጅጉ የተለየ ነበር፡፡ የራሳቸውን ጥቅምና ብልጽግና ከምንም ሳይቆጥሩ ለህዝባቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና እውን መሆን የህይወት መስዋዕትነት ለመክፈል ለአፍታም እንኳ አያመነቱም ተብለው ብዙ እጅግ ብዙ የተነገረላቸው “አብዮታውያን” ታጋዮች “የከተማ ስኳር ፈታቸው፤ የድል ማግስት ህይወት ጽኑ የትግል መንፈስና ስሜታቸውን ሰልቦ ከማይወጣው የትግል አላማቸው አሳታቸው” ተብሎ በራሳቸው ድርጅት አንደበት ተነገረባቸው፡፡
ይህንን በይፋ የተናገረው ድርጅታቸው ኢህአዴግ፤ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ በማግስቱ እንደ ከፍተኛ የድርጀቱና የሀገር መሪነታቸው ለሌሎች አርአያ መሆን ሲገባቸው፣ በከተማው ስኳር ተታለው ከህዝብ ጥቅምና ብልጽግና ይልቅ ለራሳቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና ሌት ተቀን ሲጥሩና ህገወጥ ድርጊቶችን ሲፈጽሙ አግኝቻቸዋለሁ ያላቸውን ከፍተኛ የኢህአዴግና የመንግስት ባለስልጣናት እንደ እጅ ስራቸው መጠን ህግ ያውጣቸው ብሎ ዘብጥያ አወረዳቸው፡፡
የአብዮታዊቷ ኩባ ታሪክም ከኢትዮጵያም ሆነ ከሌሎቹ አብዮተኛ ሀገራት የተለየ አይደለም፡፡ እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር በ1959 ዓ.ም የባቲስታን መንግስት በትጥቅ ትግል አስወግደው ስልጣን ስለተቆጣጠሩት የኩባ አብዮታዊ ታጋዮች ያልተባለና፣ ያልተነገረ ገድል አለ ለማለት ያስቸግራል፡፡ በተለይ ደግሞ የኩባ አብዮት ግንባር ቀደም መሪና የኩባ ጭቁን ህዝብ አባት ስለሚባሉት ስለ ጓድ ፊደል ካስትሮ በቃል ያልተነገረ፣ በጽሑፍ ያልተፃፈ፣ በፊልምም ያልቀረበ… እራስን ለህዝብ ጥቅም አሳልፎ ስለመስጠት ገድል.. ለሞት መድሃኒት እንኳ ፈልጐ ማግኘት አይቻልም፡፡
ራሳቸውን ለሰፊው ጭቁን የኩባ ህዝብ ፍፁም አሳልፈው የሰጡና ከወታደር ካኪ ሌላ የረባ ልብስ እንኳ የላቸውም እየተባለ ነጋ ጠባ የሚወደሱት ጓድ ፊደል ካስትሮ ግን እንደሚወራላቸው አይነት ሰው ሳይሆኑ ይልቁንም ልክ እንደ አንድ ታላቅ ንጉስ እጅግ በተንደላቀቀ ሁኔታ በምቾት የኖሩ ሰው እንደሆኑ ከተለያዩ ወገኖች በሹክሹክታ ሲወራ ቢከርምም ማረጋገጥ ሳይቻል ቆይቶአል፡፡
ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ የተባለ የ65 አመት ጐልማሳ ኩባዊ ግን ይህንን የሚያረጋግጥ ማስረጃ በቅርቡ ይፋ አድርጓል፡፡ ከ1977 እስከ 1994 ዓ.ም የፕሬዚዳንት ካስትሮ የቅርብ አማካሪና ከታናሽ ወንድማቸው ከራውል ካስትሮ ቀጥሎ እጅግ ጥብቅ ሚስጥረኛቸው የነበረው ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ፣ በቅርቡ ባሳተመው መጽሐፍ፤ ፕሬዚዳንት ጓድ ፊደል ካስትሮ 20ትላልቅ የቅንጦት መኖሪያ ቤቶች፣ የግል ደሴትና የመዝናኛ ጀልባ አሏቸው፡፡
የኩባው አብዮተኛ ጀግና ጓድ ፊደል ካስትሮ፤ በተጠቀሰው አመት ውስጥ በከፍተኛ ሚስጥር ይካሄድ በነበረ የእፅ ዝውውር ንግድ ውስጥ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ሀቫና ከተማ አቅራቢያ ባቋቋሙት የወታደራዊ ማሰልጠኛ ካምፕ ውስጥም እንደ አይ አር ኤ የመሳሰሉ ታጣቂ የሽብር ቡድኖችን ያሰለጥኑ ነበር፡፡     

Read 5117 times