Tuesday, 29 July 2014 14:49

ጋዜጠኛ ዘሪሁን ሙሉጌታ አገር ጥሎ ተሰደደ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(1 Vote)

“በደህንነቶች የሚደርስብኝን ጫና መቋቋም አልቻልኩም”

    በ“ሰንደቅ” ጋዜጣ ላይ ከሪፖርተርነት እስከ ከፍተኛ አዘጋጅነት ድረስ የሰራውና በቅርቡ የተመሰረተው “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው ጋዜጠኛ ዘሪሁን ሙሉጌታ አገር ጥሎ ተሰደደ፡፡ ከሶስት ዓመት በፊት ጀምሮ የደህንነት ኃይሎች ሲያደርጉበት የነበረውን ክትትል ተቋቁሞ ስራውን ሲሰራ እንደነበር የጠቆሙት ምንጮች፤ ዘንድሮ ከጥቅምት ወር ጀምሮ አዲስ በተመሰረተው የጋዜጠኞች ማህበር (ኢጋመ) የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆኖ ከተመረጠ በኋላ ግን የደህንነቶቹ ክትትልና ወከባ እረፍት እንደነሳው ተናግረዋል፡፡ የማህበሩን መመስረት አስመልክቶ ከማህበሩ ፕሬዚዳንት ከጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ጋር ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ቃለ-ምልልስ ከሰጠ በኋላ በደህንነት ሰዎች መዋከቡ እንደተባባሰ የገለፁት ምንጮች፤እነዚሁ ደህንነቶች የሚሰራበት ተቋም ድረስ በመሄድ ስለማህበሩ መረጃ እንዲሰጥ አሊያም ማህበሩን እንዲለቅ ማስጠንቀቂያ እንደሰጡትና በዚህም ምክንያት ለተወሰነ ጊዜ ከማህበሩ ለመራቅ መገደዱን ጠቁመዋል፡፡
ዘንድሮ በመጋቢት ወር ላይ በኬኒያ ናይሮቢ ለጋዜጠኞች በተዘጋጀ ስልጠና ላይ ተካፍሎ ከተመለሰ በኋላ ከሌሎች የኢጋመ አመራር አባላት ጋር በ “አርቲክል 19” የሰለጠነ በማስመሰል በአዲስ ዘመን ጋዜጣ በሽብርተኝነት ከተወነጀሉት መካከል አንዱ ሆኖ መውጣቱ ስጋቱን ይበልጥ እንዳባባሰበት የገለፁት ምንጮች፤ በደረሰበት ከፍተኛ ጫናም ለአጭር ጊዜ ከማህበሩ ጋር የነበረውን ግንኙነት አቋርጦ እንደነበረ ተናግረዋል፡፡
በቅርቡ ደግሞ ማህበሩ ያካሄደውን ውይይት ተከትሎ የማያውቃቸው ሰዎች  “በዞን ዘጠኝ ጦማሪዎች ላይ እንድትመሰክር እናደርጋለን፤ ካልሆነም መታሰረህ አይቀርም” በሚል እንዳስፈራሩት ምንጮች ጠቁመው፤ በዚህም የተነሳ አገሩን ጥሎ መሰደዱን ገልፀዋል፡፡
የጋዜጠኛ ዘሪሁንን መሰደድ በተመለከተ ያነጋገርነው የሰንደቅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ፍሬው አበበ፤ ጋዜጠኛው መሰደዱንም ሆነ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ እንደማያውቅ ጠቁሞ፤ ከ10 ቀን በላይ በስራ ገበታው ላይ ባለመገኘቱና ስልኩ ዝግ በመሆኑ፤ ወደ ስራ ገበታው እንዲመለስ የሚገልጽ ደብዳቤ በዝግጅት ክፍሉ መለጠፉን ተናግሯል፡፡
ጋዜጠኛ ዘሪሁን ምንም ሳይናገር አድራሻውን በመሰወሩ፣ ሲጨነቁ መሰንበታቸውን ዋና አዘጋጁና የሥራ ባልደረቦቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

Read 3256 times