Saturday, 02 August 2014 10:59

መንግስት የእንግሊዝ እርዳታ በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶችን ለመጣስ ስለመዋሉ መጣራቱን ተቃወመ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

         በእንግሊዝ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ በጋምቤላ ክልል በተከናወነ አስገዳጅ የሰፈራ ፕሮግራም፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ደርሶብኝ፣ ለስደት ተዳርጊያለሁ ያሉ አንድ ኢትዮጵያዊ ገበሬ፤ በአገሪቱ ላይ የመሰረቱትን ክስ ያዳመጠው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ እንግሊዝ ለኢትዮጵያ የምትሰጠው እርዳታ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ለሚጥሱ ፕሮግራሞች መዋል አለመዋላቸው እንዲጣራ መወሰኑን የኢትዮጵያ መንግስት ተቃወመ፡፡ ብሉምበርግ ኒውስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን በተመለከተ ለንደን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል በላከው መግለጫ፤ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ማስተላለፉ አግባብነት እንደሌለው ገልጾ፣ ክሱ የተመሰረተው ያለምንም ተጨባጭ መረጃና የራሳቸውን ፖለቲካዊ ጥቅም ለማስከበር በሚፈልጉ ሃይሎች አነሳሽነት እንደሆነ ገልጿል፡፡

በክልሉ የተከናወኑ የሰፈራ ፕሮግራሞች በነዋሪዎች ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረቱና ማህበራዊ አገልግሎቶችን በማሻሻል የተበታተነ አሰፋፈር ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ማህበረሰቦችን ተጠቃሚ የማድረግ ግባቸውን በማሳካት ረገድም ውጤታማ እንደነበሩ መግለጫው አስታውሷል፡፡ መንግስት ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ በሚያከናውነው በዚህ የሰፈራ ፕሮግራሞች ላይ መሰል ውንጀላዎችና የተዛቡ አመለካከቶች እንዲፈጠሩ ከሚያደርጉ ምክንያቶች አንዱ የሰፈራ ፕሮግራሙን ዓላማ በአግባቡ አለመረዳት ነው ብሏል፡፡ ‘ሂዩማን ራይትስ ዎች’ የተባለው አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት በጋምቤላ ክልል የተከናወነው የሰፈራ ፕሮግራም፣ አስገዳጅና በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ለከፋ ስቃይና የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የዳረገ ነው ማለቱን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ፤ ፍርድ ቤቱ ይህን ውሳኔ ማስተላለፉ ይበል የሚያሰኝ ነው ሲል እንዳሞካሸውም ጠቁሟል፡፡

የእንግሊዝ ዓለምአቀፍ የልማት ተቋም በበኩሉ፣ “በጋምቤላ ክልል ብዙ ዜጎችን ያለፍላጎታቸው ከቀያቸው አፈናቅሏል፣ ለእስራት፣ ለድብደባና ለስቃይ ዳርጓል ለተባለው የሰፈራ ፕሮግራም” የገንዘብ እርዳታ እንዳልሰጠ መናገሩን ገልጿል፡፡ ከጋምቤላ ክልል ተፈናቅለው በኬኒያ በስደት የሚገኙ ስማቸው ያልተገለጸ ገበሬ፤ በእንግሊዝ መንግስት ላይ የመሰረቱትን ክስ የተቀበለው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ የእንግሊዝ የእርዳታ ድርጅት ለኢትዮጵያ የሚያደርገው ድጋፍ የአገሪቱን ዜጎች የሰብዓዊ መብቶች በማይጥስ ሁኔታ ጥቅም ላይ ስለመዋሉ ይጣራ ሲል ከሁለት ሳምንታት በፊት መወሰኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

Read 3641 times