Saturday, 23 August 2014 11:46

የህጻናት የስዕል ችሎታ አእምሯዊ ብቃታቸውን ያሳያል ተባለ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የስዕል ተሰጥኦ ከዘረመል ጋር ግንኙነት አለው ተብሏል

ህጻናት በአራት አመት እድሜያቸው ላይ ሆነው የሚስሏቸው ስዕሎች አጠቃላይ ሁኔታና የስዕል ችሎታቸው፣ በቀጣይ የህይወት ዘመናቸው የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት በተወሰነ መልኩ የሚያመላክት እንደሆነ በጥናት መረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ለንደን ውስጥ በሚገኘው ኪንግስ ኮሌጅ የሥነ አዕምሮ ተቋም ተመራማሪዎች በጥናታቸው ያካተቷቸውን 7ሺህ 752 ጥንድ መንታ ህጻናት፣ የአንዲትን ህጻን ፎቶግራፍ በወረቀት ላይ እንዲስሉ በማድረግ የህጻናቱን የስዕል ችሎታ የገመገሙ ሲሆን የስዕሎቹ ውጤትም ህጻናቱ ከአስር አመታት በኋላ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት እንደሚያመላክት ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል፡፡
በአይን የተመለከቱትን ነገር በወረቀት ላይ በስዕል መልክ ማስፈር መቻል ለሰው ልጆች የተሰጠ ልዩ ክህሎት ነው ያሉት የተመራማሪዎች ቡድኑ መሪ ዶ/ር ሮዚላንድ አርደን፤ የስዕል ችሎታ የሰዎችን መረጃን በአእምሮ የማቆርና በተፈለገው ጊዜ የማውጣትና የማሰብ ብቃት የሚያመለክት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የስዕል ችሎታ ህጻናት ሲያድጉ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት የሚያመለክት ቢሆንም፣ ይህ ችሎታ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስን አለመሆኑን የገለጹት ዶ/ር አርደን፤ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስኑ ሌሎች ተፈጥሯዊና አካባቢያዊ ምክንያቶች እንደሆኑም ተናግረዋል፡፡
“በስዕል ችሎታና በአእምሯዊ ብቃት መካከል ያለው ግንኙነት የተወሰነ በመሆኑ፣ ወላጆች የልጆቻቸው የስዕል ችሎታ አነስተኛ በመሆኑ ሊሰጉ አይገባም” ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
ተመራማሪዎቹ ከዚህ በተጨማሪም፣ ጥናት ያደረጉባቸው መንታ ህጻናት የሳሏቸውን ስዕሎች በመገምገም፣ የስዕል ችሎታ በዘር የሚተላለፍ መሆን አለመሆኑን ለማጥናት የሞከሩ ሲሆን፣ በዚህም የስዕል ችሎታ ከዘረመል ጋር ግንኙነት እንዳለው ድምዳሜ ላይ ደርሰዋል፡፡

Read 2370 times