Saturday, 30 August 2014 10:46

የአውሮፓ አገራት ጫት መከልከላቸው አወዳይን ፈተና ውስጥ ጥሏታል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

እንግሊዝን ጨምሮ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ጫት ራሱን የቻለ አደንዛዥ ዕጽ ነው በማለት እንዳይገባ መታገዱን  ተከትሎ ወደ አውሮፓ ይላክ የነበረው ምርት ሙሉ ለሙሉ በመቋረጡ፣ አገሪቱ ለአለማቀፍ ገበያ ከምታቀርበው የጫት ምርት አብዛኛውን የምትሸፍነው አወዳይ ከተማ የኢኮኖሚ ፈተና ውስጥ መውደቋን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡ለኢትዮጵያ ጫት በሯን በመዝጋት የመጨረሻዋ የአውሮፓ አገር የሆነችው እንግሊዝ፣ ባለፈው ሰኔ ወር ጫትን ህገወጥ ዕጽ በማለት እንዳይገባ መከልከሏን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይህም በሺዎች በሚቆጠሩ የአወዳይ ጫት አምራች ገበሬዎች፣ ነጋዴዎችና ላኪዎች ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ተጽዕኖ ማድረሱን  ጠቁሟል፡፡
በአወዳይ አካባቢ በጫት ልማትና ንግድ ላይ ተሰማርተው የሚገኙ አርሶ አደሮችንና ነጋዴዎችን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው፤ አብዛኛው የአካባቢው ህዝብ የገቢ ምንጭ ከጫት ጋር የተያያዘ በመሆኑ፣ ክልከላውን ተከትሎ የተከሰተው የገበያ መቀዛቀዝ በአካባቢው እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጥሯል፡፡
እንግሊዝ ጫትን ከመከልከሏ በፊት፣ በወር ከሶስት ቶን በላይ ጫት ወደዚያው ይልክ እንደነበር ያስታወሰው ሙስጠፋ የተባለ በጫት ኤክስፖርት ዘርፍ የተሰማራ ነጋዴ፣ ከክልከላው በኋላ ግን ምርቱን የሚያቀርበው ለአገር ውስጥ ገበያ ብቻ በመሆኑ ገቢው በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘጋቢ ተናግሯል፡፡ በኬንያም ተመሳሳይ የገበያ ችግር እንደተፈጠረ ተጠቁሟል፡፡
በአወዳይ አካባቢ የሚኖሩ ለውጭ ገበያ የሚላክ ጫት ደላሎች፣ በአንድ ኪሎ ጫት እስከ 30 ዶላር ገቢ ያገኙ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ በአሁኑ ሰዓት ግን ገቢው ወደ 5 ዶላር ማሽቆልቆሉን አመልክቷል፡፡
በጫት ንግድ ዘርፍ የተሰማራ አንድ ሌላ የአካባቢው ነጋዴም፣ አንዳንድ አርሶ አደሮች የገቢውን መላቅ በማየት ሌሎች የእህል አይነቶችን ማምረት ትተው ወደ ጫት እርሻ ጠቅልለው መግባታቸውን በማስታወስ፣ ችግሩ በርካታ የአካባቢውን አርሶ አደሮች እንደሚጎዳ ጠቁሟል፡፡
አገሪቱ በአሁኑ ሰዓት የጫት ምርቷን የምትልከው ሶማሊያና የመንን ለመሳሰሉ አገራት መሆኑን የጠቀሰው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ፤ እ.ኤ.አ በ2012/13 ጫት በአገሪቱ የኤክስፖርት ምርት ደረጃ የአራተኛነትን ቦታ ይዞ እንደነበርና  270 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደተገኘም አስታውሷል፡፡

Read 4390 times