Saturday, 30 August 2014 10:58

ቲማቲም የዘር ፍሬ እጢ ካንሰርን ይከላከላል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ቀይ ስጋ፣ ስብና ጨው የበዛባቸው ምግቦች አይበረታቱም  

በሳምንት ከ10 ፖርሽን (1 ፖርሽን ለአንድ ሰው የሚበቃ ምግብ መጠን ነው) በላይ ቲማቲሞችን የሚመገቡ ወንዶች በዘር ፍሬ ዕጢዎች ካንሰር (Prostate Cancer) የመያዝ አደጋን 20 በመቶ እንደሚቀንሱ በእንግሊዝ የተደረገ ጥናት ጠቆመ፡፡
የብሪስቶል ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ቡድን 20ሺህ የሚደርሱ ዕድሜያቸው ከ50-69 ዓመት የሆኑ የእንግሊዝ ወንዶችን የአመጋገብና የአኗኗር ዘዬ ያጠና ሲሆን, በየሳምንቱ ከ10 ፖርሽን በላይ ቲማቲሞችን (የተቆረጡ ቲማቲሞች፣ የቲማቲም ጭማቂ፣ በቲማቲም ሱጎ የተጋገረ ባቄላ) የተመገቡ ወንዶች በዘር ፍሬ እጢ ካንሰር የመጠቃት ዕድላቸው 18 በመቶ መቀነሱን ተመልክቷል፡፡
“የጥናት ውጤታችን ቲማቲም የዘር ፍሬ እጢ ካንሰርን በመከላከል ረገድ ጠቃሚ እንደሆነ ይጠቁማል” ያሉት ብሪስቶል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ት/ቤት ተወካይ ቫኔላ ኢር፤ ግኝታችንን ለማረጋገጥ ተጨማሪ ጥናቶች መካሄድ አለባቸው ብለዋል፡፡
“ወንዶች በርካታ የተለየዩ ዓይነቶች አትክልቶችና ፍራፍሬዎችን መመገብ፣ ጤናማ የሰውነት ክብደታቸውን መጠበቅና አካላዊ እንቅስቃሴ ማድረግ አለባቸው” ሲሉ መክረዋል ቫኔላ፡፡
ተመራማሪዎቹ የዘር ፍሬ እጢዎች ካንሰርን የሚከላከሉ ሌሎች ሁለት የምግብ ዓይነቶችንም መርምረዋል፡፡ ዳቦና ፓስታ በመሳሰሉት ከዱቄት የሚዘጋጁ ምግቦች ውስጥ የሚገኘው ሴሊኒየም የተባለ ንጥረ ነገር እንዲሁም ወተትና ቺዝ በመሳሰሉት የወተት ውጤቶች ውስጥ የሚገኘው ካልሲየም በፕሮስቴት ካንሰር የመጠቃት አደጋን እንደሚቀንሱ ተመራማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡ ቲማቲምንና ከላይ የተጠቀሱትን ሁለት የምግብ ንጥረ ነገሮች በቅጡ የሚጠቀሙ ወንዶች ለበሽታው የመጋለጥ ዕድላቸው ዝቅተኛ ነው ብለዋል አጥኚዎቹ፡፡
በጥናቱ ላይ አስተያየት የሰጡት ዶ/ር አያይን ፍሬም በፕሮስቴት ካንሰር የመያዝ አደጋን ለመቀነስ ይችሉ ዘንድ ወንዶች የትኞቹን የተወሰኑ ምግቦች መብላት እንዳለባቸው ተጨባጭ ጥቆማ ለመስጠት የሚያስችል በቂ ማስረጃ አልተገኘም ብለዋል፡፡
ወንዶች እንደ ቲማቲማ ባለ አንድ የምግብ ዓይነት ላይ ብቻ መተማመን የለባቸውም የሚሉት ዶ/ር ፍሬም፤ “ጤናማ፣ በዛ ያሉ አትክልትና ፍራፍሬዎችን ያካተተ የተመጣጠነ ምግብ ከመደበኛ የአካል እንቅስቃሴ ጋር ይበልጥ የተሻለ አማራጭ ነው” በማለት አስረድተዋል - ዶ/ር ፍሬም፡፡
የዩኬ ካንሰር ምርምር ተቋም ተወካይ ቶም ስታንስፌልድ በበኩላቸው፤ “ላይኮፒኒ በተባሉ ንጥረነገሮች የበለፀጉ እንደቲማቲም ያሉ ወይም ሴሌኒየም የያዙ ምግቦች የፕሮቴስት ካንሰር አደጋን ከመቀነስ ጋር ሊያያዙ ይችላሉ፤ ነገር ግን ይሄ ነገር አልተረጋገጠም፤ የአሁኑ ጥናት በምግብና በፕሮስቴት ካንሰር መካከል ግንኙነት ይኑር አይኑር ሊያረጋግጥ አይችልም” ብለዋል፡፡
ነገር ግን ሁሉም ወንዶች የፍራፍሬና አትክልት ይዘቱ ከፍተኛ የሆነ የተመጣጠነ ምግን እንዲያዘወትሩ እናበረታታለን ያሉት ቶም ስታንስፌልድ፤ ቀይና በፋብሪካ የተቀነባበረ ስጋ እንዲሁም ስብና ጨው የበዛባቸው ምግቦችን በእጅጉ መቀነስ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡
የዘር ፍሬ እጢዎች ካንሰር በመላው ዓለም በወንዶች ላይ በስፋት የተሰራጨ ሁለተኛው የካንሰር ዓይነት ሲሆን በእንግሊዝ በየዓመቱ 10ሺ ገደማ ወንዶች በበሽታው ይሞታሉ፡፡ 

Read 5192 times