Saturday, 06 September 2014 10:55

ክረምት አልፎ በጋ መስከረም ሲጠባ…

Written by  ኤፍሬም እንዳለ
Rate this item
(6 votes)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እንኳን ለአዲስ ዓመት ዋዜማ አደረሳችሁማ!
ፊታችን ሳይጨፈግግ፣ ልባችን በስጋት ሳይነጥር፣ ስሜታችን የነሀሴ ሰማይ ሳይመስል… እንድንቀበለው ያድርግልንማ!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል፣ አንዳንዴ ግራ የሚገባችሁ ነገር አለ፡፡ ‘እንደ ሌላው ዓለም ለመሆን’ እንደ ገናና አዲስ ዓመት የመሳሰሉ በዓላትን “ለምን ወደ እነሱ አቆጣጠር አንለውጥም!” የሚሉ ‘ስልጣኔ እግር ተወርች የጠፈራቸው’ ሰዎች ገጥመዋችሁ አያውቁም! ይሄ የፈረደበት ገና ጭራውን ከቀንዱ ለይተን ማየት ያቃተን ግሎባላይዜሽን የሚሉት ነገር… አለ አይደል… ብዙዎቻችንን የሆንን ‘በቀደዱልን ቦይ እንድንፈስ’ እያደረጉን ነው፡፡
በአምባሰል ምት ላይ ቅልጥ ያለ ራፕ ተጨምሮ “ጊዜው የግሎባላይዜሽን ነው…” የሚባል ‘ብሮፌሰሮች’ እንኳን ያልደረሱባት ‘እውቀት’ አለችላችሁ፡፡ የ‘ፈረንጅን ጆሮ’ ይድፈንልንማ! ልጄ… ግሎባላይዜሽን የሚሉት ነገር እንዲሁ “ጊዜው የግሎባላይዜሽን ነው…” እየተባለ የሚታለፍ አይደለም፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ምን ያህል ‘ከጨዋታ ውጪ’ እንደሆንን እኮ በየቀኑ በዜናዎች ላይ እንሰማለን፡፡ አንድ የሆነ ‘እነሱ የማይመቻቸው’ ነገር ሲፈጠር ሲኤንኤን ቢቢሲ ምናምን ነገሩ “ዓለም አቀፉን ህብረተሰብ…” (International community) እንዳስቆጣ ይናገራሉ፡፡ ‘የተቆጡት’ እኮ የሁለት ወይም የሦስት ጡንቸኛ አገሮች መሪዎች ናቸው! እናላችሁ…ግሎባላይዜሽን ምናምንም እንደዛው ነው!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ቀደም ባለው ጊዜ አዲስ ዓመት ሲመጣ ቃል የምንገባቸው መአት ነገሮች ነበሩ፡፡ “ማጨስ አቆማለሁ…”  “መጠጥ አቆማለሁ…” “ውጪ ማምሸት አቆማለሁ...” ምናምን ይባል ነበር፡፡
ደግሞላችሁ…“ትምህርቴን እገፋለሁ…” “መሥሪያ ቤት እቀይራለሁ…” “የግል ሥራ እጀምራለሁ…” ምናምን የሚባሉ ነገሮች ነበሩ፡፡ ዘንድሮ ብዙ ሰው እንዲህ ሲል አትሰሙም፡፡ የምር ጊዜ ተለውጧል፡፡ ልጄ…የሰፈረብን ዛር እንዲህ በቀላሉ የሚለቀን አይመስልም፡፡
የምር ግን… በዚህ በአዲስ ዓመት ዋዜማ…አለ አይደል… ነገሮችን ሳንቀባባ፣ በ‘ትክክለኛ ቀለማቸው’ አይተን ለመገንዘብ ፈቃደኛ ካልሆንን “የሚወጣው አሮጌ ዓመት እንዴት ነበር?” ሲባል ያቺ የለመድናትን “ከሚቀጥለው ይሻላል…” ምላሽ እየሰጠን እንዲሁ የቀን መቁጠሪያ ዲዛይን ስንለውጥ ልንኖር ነው፡፡
ስሙኝማ…ይሄን ሰሞን ያው ‘ዳያስፖራዎች’ ከተማችንን ‘በቁጥጥር ስር እንድሚያውሏት’ (‘እንደሚያሳድሯት’ ልል ፈልጌ ይሉኝታ ይዞኝ መሆን አለበት! ቂ…ቂ…ቂ…) እንኳንስ ደህና መጣችሁ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ብዙ ጊዜ በተለይ በውጪ ሀገራት ጥቂት ዓመታት ከረም ብለው የመጡ አንዳንድ ሰዎች…አለ አይደል… “ክትፎ ቤቱ ግፊያ ነው፣ ውስኪ ቤቱ ግፊያ ነው፣ ሬስቱራንቱ ሁሉ ግፊያ ነው…ሰዉ ተቸግሯል የምትሉት ምንድነው?” ምናምን አይነት ነገር ይላሉ፡፡ ወዳጆቼ…የኢትዮዽያ ህዝብ ጥቂት አሥር ሺዎች አለመሆኑን ልብ ይባልልንማ! የመጠጥ ቤቶች መሙላት ‘የምቾት ምልክት’ ከመሰላችሁ… በየቀኑ ጢም ብለው የሚሞሉትን የየመንደሮቹ ጠላና ጠጅ ቤቶችንም በእኛ ወጪ ለማሳየት ፈቃደኛ ነን፡፡ (እንትና…ያ ‘ኤክስፐርመንት’ እንዴት ሆነ? ጠጃችን በቮድካ ተበለጠ እንዴ!)
‘ሚዛኑን’ አታበላሹብንማ!
ስሙኝማ…እንግዲህ አዲስ ዓመት ዋዜማ ላይ አይደለን! የወጣቱ ትውልድ የወደፊት ዕጣ ፈንታ አያሳስባችሁም! ምንም እንኳን ‘በትክክለኛው ሀዲድ’ ላይ ያሉ በርካታ ወጣቶች ቢኖሩም፣ ደግሞላችሁ… ከእነሱ በብዙ ቁጥር የላቁ ከሀዲዱ ሲወጡ ስታዩ የምርም… “ወዴት እየሄድን…” እንደሆነ ግራ ይገባችኋል፡፡ በአንድ በኩል በርካታ መሥሪያ ቤቶች በወጣቶች ተሞልተው ስታዩ (ስለ ‘አገልግሎት ጥራት’ እያወራን አይደለም!) የሆነ ተስፋ ነገር ይታያችኋል፡፡ በተለይም የተለያዩት የስነ ጥበብና የኪነ ጥበብ ዘርፎች በወጣቶች ፊት አውራሪነት ሲካሄዱ ስታዩ ተስፋ ነገር ይታያችኋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ተስፋ የሚያስቆርጡ ነገሮች መአት ናቸው፡፡ ወጣቶች ራሳቸውን መሆን ትተው ሌላ ‘ማንነት’ ለመያዝ ሲሞክሩ ስታዩና ከማንነት ‘ግራ መጋባት’ ጋር የተያያዙ ቀውሶች ውሎ አድሮ የሚያስከትሏቸውን የቀጥታም ይሁን የጎንዮሸ አበሳዎች ስታስቡ… እንደ ተስፋ መቁረጥ ይቃታችኋል፡፡ እነኚህ ወጣቶች ነገ በግድ የራሳችን ካላደረግነው ያሉት ‘ማንነት’ “ለአሁኑ አልተሳካላችሁም…” አይነት ነገር ሲገጥማቸው፣ ያኔ ሉሲፈር ሙሉ ለሙሉ የሚሰፈርበት ‘ነጻ ሰው’ አገኘ ማለት ነው! እናማ…የአገሪቱን ‘ማስተር ኪይ’ ይቀበላል የምንለው ወጣት፤ “እውን ያንን ኃላፊነት የመቀበል አቅም ይኖረው ይሆን!” ብላችሁ ስጋትና ተስፋ መቁረጥ ቢጤ ይቃጣችኋል፡፡
እናላችሁ… እያሳሳቀ እንደሚወስደው ወንዝ፣ ወጣቱን ትውልድ ‘እያሳሳቁ የሚወስዱት’ ነገሮች በዝተዋል፡፡ ስሙኝማ…ይሄ ወጣቱን ትውልድ የማዳን ነገር ብዙ ጊዜ በየሚዲያው እየተነሳ ምንም ተጨባጭ ነገር ሲደረግ አለማየታችን አይገርማችሁም! ኮሚክ እኮ ነው…የሚመለከተን ሁሉ…አለ አይደል…“የራሳቸው ጉዳይ፣ እኛ በአንቀልባ ልናዝንላቸው ነበር!” አይነት ነገር የምንል ይመስላል፡፡
ምን ግርም ይልሀል አትሉኝም…በየቦታው ያሉት ወጣት ማዕከላት በጠረጴዛ ኳስና በ‘ጆተኒ’ ተሞልተው ስታዩዋቸው “እውን በዚህ ብቻ ነው የወጣቱ አእምሮ የሚጐለምሰው!” ብላችሁ ስጋት ቢጤ ይቃጣችኋል፡፡
መጪው ዓመት ወጣቱን ትውልድ ‘ከሀዲዱ የሚያወጡ’ ነገሮችን ሲሆን ሙሉ ለሙሉ የሚጠፉበት አለበለዛ በእጅጉ የሚቀንሱበት ይሁንልንማ!
መጪው ዓመት… አለ አይደል… “እንደው አምላኬ ምን ታደርገን ይሆን?” የምንለው አሁን፣ አሁን እየባሰ የመጣ ስጋታችን ተቀርፎ… አለ አይደል…ደግ፣ ደግ ነገሮችን የምናወራበት፣ በሥራችንም፣ በኑሯችንም “እንኳን ደስ ያለህ!” የምንባባልባቸው ነገሮች የሚበዙበት ዓመት ይሁንልንማ!  
አንዱ ‘የፈረንጅ ስታንድ አፕ ኮሜዲያን’ ምን አለ መሰላችሁ…“ልጅ ማሳደግ በከፊል ደስታ፣ በከፊል ደፈጣ ውጊያ ነው፡፡” አሪፍ አባባል አይደል! መጪው ዓመት ለሀገራችን ወላጆች ልጅ ማሳደግ ደፈጣ ውጊያ ሳይሆን ደስታ የሚሆንበት ዓመት ይሁንልንማ!
እብሪት ከእነ ጦስ ጥንቡሳሱ ውልቅ ብሎ ይጥፋልንማ!
ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ብዙዎቻችን በአንድ ወይም በሌላ ምክንያት ‘ወፍረን’… አለ አይደል… “መንገዱን ልቀቁልኝ!” አይነት ነገር ይሞክረናል፡፡ ወይ በስልጣን፣ ወይ በወንበር፣ ወይ ‘በኔትወርክ’  (ቂ…ቂ…ቂ…) ‘እንወፍር’ና “ነጋሪት ጎስሙልኝ!” ለማለት ይቃጣናል፡፡
አባቶቻቸን ‘አሞሌ ሲወፍር ወንዝ አውርዳችሁ እጠቡኝ ይላል…’ የሚሏት አባባል አለቻቸው፡፡ እናማ…ምን መሰላችሁ… ‘እንደ ወፈረ’ አሞሌ… “ወንዝ አውርዳችሁ እጠቡኝ…” የምንል በዝተናል፡፡ ‘እብሪታችን’ እይታችንን ጋርዶናል፡፡ ገንዘብና ስልጣን የሁሉ ነገር ‘የበርሊን ግንባችን’ የሚመስለን በዝተናል፡፡
መጪው አዲስ ዓመት… “ወንዝ አውርዳችሁ እጠቡኝ!” ማለትን የምንቀንስበትና አሞሌ ሆዬ፤ “ወንዝ አውርዳችሁ እጠቡኝ!” ያለ ቀን የሁሉም ነገር ‘አርማጌዶን’ እንደሚሆን የምንገነዘብበት ዓመት ይሁንልንማ!
ከልባችን…
ክረምት አልፎ በጋ መስከረም ሲጠባ
አሮጌ ዓመት አልፎ አዲሱ ሲገባ
በአበቦች መአዛ ረክቷል ልባችሁ
ህዝቦች ሁሉ በጣም እንኳን ደስ አላችሁ፤
ብለን በጋራ የምንዘምርበትን ጊዜ ያቅርበውማ!
መልካም የዋዜማ ቀናት፣ መልካም የአዲስ ዓመት መግቢያ ይሁንልንማ!
ደህና ሰንበቱልኝማ!

Read 4609 times