Saturday, 13 September 2014 12:51

ቱርክ በኢትዮጵያ ኢንቨስት በማድረግ መሪነቱን ከቻይና ተረከበች

Written by 
Rate this item
(4 votes)

           ቱርክ በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንቱ ዘርፍ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ ቀዳሚነቱን ይዛ የቆየችውን ቻይናን በመብለጥ መሪነቱን መረከቧን የኢንቨስትመንት ኤጀንሲን መረጃ በመጥቀስ ወርልድ ቡሊቲን ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
በኢትጵዮያ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ ቀድመው የተሰማሩት የቻይና ባለሃብቶች እንደሆኑ ያስታወሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን ዘግይተው ወደ ኢንቨስትመንቱ የገቡት የቱርክ ባለሃብቶች፣ ሰፋፊ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በመዘርጋት፣ በአገሪቱ ኢንቨስትመንት ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ ረገድ በቻይናውያኑ ተይዞ የቆየውን መሪነት ለመረከብ መቻላቸውን ጠቁሟል፡፡
የቱርክ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች 1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር በማውጣት ቀዳሚነቱን እንደያዙ የጠቆመው ዘገባው፤ ቻይናውያን ባለሃብቶችም ባለፉት አስር አመታት በአገሪቱ 836 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ኢንቨስትመንት መዘርጋታቸውን አስረድቷል፡፡
በተለይ በጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪው ዘርፍ በስፋት እየሰሩ የሚገኙት የቱርክ ባለሃብቶች በትላልቅ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ላይ ሲሰማሩ፣ ቻይናውያኑ በበኩላቸው፤ በአብዛኛው በአነስተኛና በብዙ አትላልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ተሰማርተው እየሰሩ እንደሚገኙም ታውቋል፡፡
ቱርክ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ ረገድ መሪነቱን ብትይዝም፣ የስራ ዕድል በመፍጠር ቻይና ቀዳሚነቷን ይዛ እንደቀጠለች ጠቅሶ ዘገባው አስታውቋል፡፡ ቻይና በኢትዮጵያ በተሰማራችባቸው የኢንቨስትመንት መስኮች ከ75 ሺ 500 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል ስትፈጥር፣ ቱርክ በበኩሏ 20 ሺህ 900 ያህል የስራ ዕድል መፍጠሯን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገሪቱ ብዙ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶችን በማከናወንም ቻይና ቀዳሚነቱን እንደያዘች ገልጿል፡፡
ቻይና 437 ፕሮጀክቶች ሲኖሯት፣ ቱርክ 100 ፕሮጀክቶችን በማንቀሳቀስ ላይ ትገኛለች ብሏል፡፡

Read 3870 times