Saturday, 13 September 2014 12:54

ተቃዋሚዎችና ኢህአዴግ ለኢትዮጵያ ህዝብ የዲሞክራሲ ዘመን ተመኙ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(4 votes)

        የተቃዋሚ ፓርቲዎች አዲሱ ዓመት ዲሞክራሲያዊ ስርአት የሚያብብበት፣ የህግ የበላይነት የሚረጋገጥበትና የፖለቲካ ምህዳር የሚሰፋበት ዓመት እንዲሆን በመመኘት፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ የመልካም ዘመን ምኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡የኢትዮጵያ ዲሞክራሲውያን ፓርቲ (ኢዴፓ) ለአዲስ አድማስ በላከው የመልካም ምኞት መግለጫ፤ መጭው ዘመን የመድብለ ፓርቲ የፖለቲካ ስርአት የሚጠናከርበት፣ የጥላቻና የኩርፊያ ፖለቲካ ታሪክ የሚሆንበት፣ የመቻቻልና የመከባበር ፖለቲካ የሚጎለብትበት፣ የጭፍን ተቃውሞና ድጋፍ በአማራጭ የፖለቲካ ሃሳብ የሚተካበት እንዲሁም፣ ምክንያታዊ ፖለቲካ የሚያብብበት እንዲሆን ተመኝቷል፡፡
ህዝቡ በመጭው አገራዊ ምርጫ በተሳትፎው ስልጡን መሆኑን ዳግም የሚያረጋግጥበትና የፖለቲካ ምህዳሩ ሁሉንም አሳታፊ በሆነ መልኩ የበለጠ የሚሰፋበት እንዲሆን የተመኘው ኢዴፓ፣ የሀገር ዳር ድንበር በማስከበር ስራ ላይ ለተሰማሩ የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ ለህግ ታራሚዎች እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንላችሁ ብሏል፡፡
ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ (ቅንጅት) በበኩሉ፤ ለ2007 ምርጫ ሰፊ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ጠቁሞ አዲሱ ዓመት የህግ የበላይነት የተረጋገጠበት፣ የዜጎች ሰብአዊ መብት ያለገደብ የሚከበርበት፣ ድህነት ተወግዶ ብልፅግና የሚመጣበት እንዲሁም ዜጎችን እኩል የሚያደርግ ዲሞክራሲዊ ስርአት የሚሰፍንበትና በህዝብ ለህዝብ” የቆመ መንግስት የሚመሰረትበት ይሆን ዘንድ ተመኝቷል፡፡ የኢህአዴግ አንዳንድ ካድሬዎች በቅንጅት አባላት ላይ ወከባ እየፈፀሙ ነው ያለው ቅንጅት፤ ነፃነትን ገድቦ የምርጫ በእንቅስቃሴ ውስጥ መግባት ተገቢ ባለመሆኑ፣ ኢህአዴግ በአዲስ ዓመት ጉዳዩን በአንክሮ ሊያስብበት እንደሚገባ አሳስቧል፡፡
አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት)፤ በበርካታ የሃገሪቱ ከተሞች ህዝባዊና ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ከ97 ዓ.ም ወዲህ በህብረተሰቡ ውስጥ የሰረፀውን ፍርሃት ፖለቲካ ድባብ በማስወገድ ከፍተኛ ጥረት ማድረጉን የጠቆሙት የፓርቲው ፀሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ፤ የአባላት እስርና እንግልትን ጨምሮ በርካታ ተግዳሮቶች ቢገጥሙትም አላማውን አሳክቷል ብለዋል፡፡
ፓርቲው ከመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጋር ውህደት ለመፈፀም ከጫፍ ላይ ደርሶ እንደነበር አቶ ስዩም አስታውሰው፤ ሂደቱ ቢሳካ ኖሮ 2006 ዓ.ም ይበልጥ ስኬታማ ዓመት ይሆንልን ነበር ብለዋል፡፡ ውህደቱም በአዲሱ ዓመት በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሳካል ብለን እናምናለን ሲሉ ተስፋቸውን ገልፀዋል፡፡ ቀጣዩ አመትም ሰብአዊና ዲሞክራሲዊ መብቶች እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች ፍትሃዊ በሆነ መንገድ የሚከበሩበት፣ ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነበት፣ እንዲሆን ከመንግስት በርካታ ስራዎች እንደሚጠበቁ ጠቁመው፤ ለኢትዮጵያ ህዝብ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የጤናና መልካም ምኞቱን ገልጿል፡፡ አገሪቱ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን በእኩልነት የምትመች፣ ዜጐች ስደትን የማይመርጡባት አገር እንድትሆንም አንድነት ተመኝቷል፡፡ የኢህአዴግ የህዝብ ተሳትፎ አደረጃጀት ፅ/ቤት ኃላፊና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ ደስታ ተስፋው በበኩላቸው፤ ያለፈው ዓመት ኢህአዴግ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ተግባራዊ በማድረግ በርካታ ውጤት እያስመዘገበ ያሳለፈበት ዓመት መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይ ከድህነት ለመውጣት እየተደረገ ያለው ርብርብ አይቻልም የሚለውን መንፈስ የሰበረ ነው፡፡
2007 ዓ.ም የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የመጨረሻ ዓመት በመሆኑ ከምንጊዜውም በላይ ለላቀ ውጤት የምንነሳበትና የምንረባረብበት ዓመት ነው” ያሉት አቶ ደስታ፤ በዚህ ዓመት ምርጫ እንደሚካሄድ አስታውሰው፤ ህዝቡ ህገ-መንግስቱ የሰጠውን መብት ተግባራዊ የሚያደርግበት ዓመት ነው ብለዋል፡፡ ለኢህአዴግ ልዩ ትርጉም የሚሰጠው ዓመት መሆኑን የገለፁት አቶ ደስታ፤ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝቦች የሰላም፣ የብልፅግናና የእድገት ዓመት እንዲሆን፣ ልዩነቶችን በሰለጠነ መንገድ እየፈቱ፣ በሃገራዊ መግባባት እጅ ለእጅ ተያይዘን ሃገራችንን ለላቀ ውጤት የምናበቃበት ዓመት ይሁን ሲሉ ተመኝተዋል፡፡ ያለፈው ዓመት ለመኢአድ አባላት ከባድ ጊዜ እንደነበር አስታውሰው ፓትሪውንም የተለያዩ አካላት ለማፍረስ ጥረት ያደረጉበት አመት ነበር ብለዋል፡፡ አክለውም የዲሞክራሲው ሂደት ወደ ኋላ እንጂ ወደፊት የሚሄዱበት ዓመት አልነበረም ብለዋል፡፡
“የ2007 ዓ.ም ደግሞ ህዝቡ በንቃት መሪዎቹን የሚመርጥበት ዓመት ይሁን፣ መንግስትና ምርጫ ቦርድ ቦታ ከሰጡን ለመወዳደር እንዘጋጀለን፤ ካልሰጡን ይቀራል” ያሉት አቶ አበባው፤ ዓመቱ ለኢትዮጵያ ህዝብ የሰላምና የብልፅግና እንዲሆን በፓርቲያቸው ስም መልካም ሞኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የመድረክ ስራ አስፈፃሚ አቶ ጥላሁን እንደሻው በበኩላቸው፤ መድረክ ለኢትዮጵያ ህዝብ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የብልፅግናና የጤና ዓመት እንዲሆን ተመኝተው በሃገሪቱ ያለው የፖለቲካ ምህዳር ችግር በሰላማዊ ውይይት ተፈትቶ ህዝቡ የስልጣን ባለቤት ለመሆን በፍትሃዊ ምርጫ ድምፁን የሚጥበት አመት ይሆን ዘንድ ተመኝተዋል፡፡

Read 2509 times