Saturday, 27 September 2014 08:59

የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን መንግስት የታሰሩ ጋዜጠኞችን እንዲፈታ ጠየቀ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

              የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን የኢትዮጵያ መንግስት በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞችን እንዲፈታና በቅርቡ አገራቸውን ጥለው የተሰደዱ ጋዜጠኞችም፣ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ስራቸውን የሚቀጥሉበትን ምቹ ሁኔታ እንዲፈጥር ጠየቀ፡፡ አለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ባለፈው ረቡዕ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ በኢትዮጵያ የሚታየው የፕሬስ ነጻነት ጥሰት፣ የጋዜጠኞች እስርና ስደት ያሳስበኛል ብሏል፡፡ “በኢትዮጵያ የፕሬስ ነጻነትን የሚጥሱ ተግባራት መከናወናቸው መቀጠሉ እንዲሁም የሚታሰሩና አገር ጥለው የሚሰደዱ ጋዜጠኞች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ያሳስበናል” ያሉት የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ጋርባ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከመገኛኛ ብዙሃን ጋር ሃቀኛ ውይይትና ምክክር በማድረግ፣ ራሳቸውን ተቆጣጥረው በአግባቡ እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታዎችን እንዲፈጥር ጥያቄ ማቅረባቸውን ገልጸዋል፡፡በኢትዮጵያ ብሄራዊ ጋዜጠኞች ህብረትና በምስራቅ አፍሪካ የጋዜጠኞች ማህበር አዘጋጅነት በቅርቡ በአዲስ አበባ በተካሄደው የምርመራ ጋዜጠኝነት አውደ-ጥናት ላይ የተሳተፈውና ከምስራቅ አፍሪካ የጋዜጠኞች ማህበርና ከአለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን የተወከሉ 3 አባላት ያሉት የልኡካን ቡድን፣ ከመንግስት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መምከሩንም የፌዴሬሽኑ መግለጫ አስታውሷል፡፡

ከአካባቢው አገራት በበለጠ ሁኔታ ጋዜጠኞች የሚታሰሩትና የሚሰደዱት በኢትዮጵያና በኤርትራ እንደሆነ ለሚኒስትሩ የገለጹት የልኡካን ቡድኑ አባላት፣ የኢትዮጵያ መንግስት በእስር ላይ የሚገኙትን ሁሉንም ጋዜጠኞች እንዲፈታና በስደት የሚገኙትም ወደአገራቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ እንዲያመቻች መጠየቃቸውን ጠቁሟል፡፡ አቶ ሬድዋን በበኩላቸው ለልኡካን ቡድኑ በሰጡት ምላሽ፣ በቅርቡ አገር ጥለው የተሰደዱት ጋዜጠኞች ክስ እንዳልተመሰረተባቸውና ከአገር የሚያስወጣቸው ምክንያት እንደሌለ ፤ የአገሪቱ መንግስትም ሃሳብን የመግለጽ ነጻነትን ለማስከበር ቁርጠኛ አቋም ይዞ እየሰራ እንደሚገኝ መናገራቸውን መግለጫው አመልክቷል፡፡ የአፍሪካ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን በ40 የአህጉሪቱ አገራት ውስጥ የሚገኙ ከ50ሺህ በላይ ጋዜጠኞችን እንደሚወክል፣ አለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

Read 2288 times