Monday, 03 November 2014 07:24

“የኢትዮጵያን ፖለቲካ እንዲሰደድ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው”

Written by 
Rate this item
(8 votes)

የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ “በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያንን የፖለቲካ እንቅስቃሴ” በተመለከተ አሜሪካ ውስጥ ላለፉት ስድስት ወራት ጥናት ሲያደርጉ ቆይተው በቅርቡ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ በአሜሪካ ስለነበራቸው ቆይታ፣ ስለ ጥናታቸው፣ እንዲሁም በሃገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ ጋር ያደረጉት ቃለ-ምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡

ላለፉት ስድስት ወራት አሜሪካ ቆይተው ነው የመጡት፡፡ የጉዞዎ አላማ ምን ነበር?
“ናሽናል ኢንዶውመንት ፎር ዲሞክራሲ” በተባለ የአሜሪካ ተቋም ውስጥ ጥናት ሳደርግ ነው የቆየሁት፡፡ ዲሞክራሲ እና የኢትዮጵያ ዳያስፖራን በተመለከተ በተለይ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚደረገው ዲሞክራሲያዊ ትግል ውስጥ ያላቸውን ሚና ማየት ነበር የጥናቱ ዓላማ፡፡ የአሜሪካ ዋና ከተማ ዲሲ ውስጥ የኢትዮጵያ ሁለተኛ ዋና ከተማ በሚመስል ደረጃ ነው ኢትዮጵያውያኖች ያሉት፡፡ እዚያ አካባቢ ፖለቲካው ያገባናል ብለው የሚንቀሳቀሱትን አግኝቻለሁ፡፡ እንደ ሲያትል፣ ሳንዲያጎ፣ ላስቬጋስ፣ ሳንፍራንሲስኮ፣ ሚኒሶታ፣ ዳላስ፣ ፊላደልፊያ በመሳሰሉት የአሜሪካ ከተሞች ተዛዙሬም ኢትዮጵያውያንን አነጋግሬያለሁ፡፡ በዚያውም ለፓርቲያችን ድጋፍ ለማሰባሰብ ሞክሬያለሁ፡፡ ከሞላ ጎደል በውጭ ያለው ዳያስፖራ በሀገሩ ፖለቲካ ላይ እንዴት ነው? የሚለውን ነው ያየሁት፡፡ በ“ኢሳት” እና በ“ቪኦኤ” እንዲሁም በ“ኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ” ላይ የኢትዮጵያን ፖለቲካ በተመለከተ በስፋት ቃለምልልሶችንና ክርክሮችን ለማድረግ ሞክሬያለሁ፡፡ መጨረሻ ላይም አሜሪካውያንና ኢትዮጵያውያን በተገኙበት መድረክ ላይ የጥናት ውጤቱን አቅርቤአለሁ፡፡
መሰረታዊ ችግሮቻችንን ለመፍታት ከኢትዮጵያ መንግስት፣ በውጭው ዓለም ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ከዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ምን ይጠበቃል በሚሉት ሶስት መሰረታዊ ነገሮች ላይ ነው አስተያየት ለማቅረብ የሞከርኩት፡፡
በወቅቱ ፕሬዚዳንት ኦባማ፣ የአፍሪካ አምባገነን መሪዎችን ሰብስቦ ሲያነጋግር፣ እኔ ጥናት ያቀረብኩበት ዲሞክራቶች የሚመሩት ናሽናል ዲሞክራቲክ ኢንስቲቲዩት፣ እንዲሁም ዊልሰን ሴንተርና ፍሪደም ሴንተር የሚባሉ ተቋማት በጋራ የአፍሪካ ሲቪል ማህበረሰብ አባላትን ሰብስበው ነበር፡፡ በጣም ሰፊ ስብሰባ ነው፡፡ በመድረኩ ላይም ስለ አፍሪካ መሰረታዊ ችግሮች ማለትም ስለ ምርጫ፣ ስለ ፍትህ፣ ስለ ሰብአዊ መብት አከባበር… ሃሳቦች ተንፀባርቀው ውይይት ተደርጓል፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይም በተናጋሪነት ተሳትፌያለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህን ስራዎች ስሰራ ነው የቆየሁት፡፡
በዳያስፖራው ላይ ባካሄዱት ጥናት ምን ውጤት አገኙ?
ምንም ጥያቄ የለውም፤ ከዳያስፖራው ጋር በሁለት ነገሮች ላይ መግባባት ያስፈልገናል፡፡ እንደሚታወቀው ያለ ዳያስፖራው ድጋፍ መንቀሳቀስ ይከብዳል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ባለው የፖለቲካ ምህዳር፣ ከሃገር ውስጥ የፋይናንስ ድጋፍ ማግኘት የሚቻልበት ደረጃ ላይ አይደለንም፡፡ የዳያስፖራው ድጋፍ ያስፈልገናል፡፡ ዳያስፖራው ግን ድጋፉን ሲሰጠን ውሃ ልኩን ካላወቀ፣ ሃገር ውስጥ የሚደረገው ትግል መልኩን ሊስት ይችላል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ሰላማዊና ህጋዊ ትግል፣ ዳያስፖራው በውጪ ደረጃና ሚዛን ካየው እንዲሁም እንደዚያ ተንቀሳቀሱ ካለ፣ አገር ውስጥ በዚያ ደረጃ መንቀሳቀስ ስለማይቻል፣ ብዙ ተስፋ የመቁረጥ ዝንባሌ ይከሰታል፡፡ ይሄንንም በጥናቴ ተመልክቻለሁ፡፡ ሌላው ደግሞ ዳያስፖራው በሚሰጠው ድጋፍ መጠን በሚፈልገው አቅጣጫ ግፋበት የማለት ዝንባሌ ይታያል፤ እሱም ያስቸግራል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አስቸጋሪው ዳያስፖራው በተለይ በብሄር የመከፋፈሉ ነገር ነው፡፡ በብሄር ብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ዳያስፖራው ሃገር ውስጥ ካለነው በበለጠ ተከፋፍሏል፡፡   ምን ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ለውጥ መምጣት አለበት በሚለው ላይ ሀገር ውስጥ ያሉት ተቃዋሚዎችም ሆኑ ዳያስፖራው ስምምነት ላይ ካልደረሱ፣ ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል ወደፊት ለመግፋት ይቸግራል፡፡ በዳያስፖራው እና በሃገር ውስጥ ባለው ተቃዋሚ መካከል ኢትዮጵያ እንዴት ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ትሂድ በሚለው ላይ መግባባት መፍጠር ያሻል፡፡
ዳያስፖራው በፖለቲካ ብቻ ሳይሆን በሃይማኖትም ጭምር እስከ መከፋፈል ደርሷል በማለት የሚተቹ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ በጥናትዎ ምን ታዘቡ?
ከሃይማኖት ይልቅ በፖለቲካው ውስጥ ያለው ክፍፍል፣ በተለይ በብሄረሰቦች ጥያቄ ዙርያ ሁለት ፅንፍ አለ፡፡ መሃል መንገድ ላይ የሚሰባሰቡ ኃይሎች ተፈጥረው፣ የኢትዮጵያን ዕጣ ፈንታ ሊወስን የሚችል ዲሞክራሲያዊ ትግልን መልክ ማስያዝ እስካልቻሉ ድረስ ያለማጋነን የሁለት ፅንፎች እስረኛ እንሆናለን፡፡ አንዱ ኢትዮጵያ የሚባል ነገር አልሰማም ይላል፤ ሌላው ደግሞ የኢትዮጵያዊነት ሰርተፍኬት ሰጪም ከልካይም እኛ ነን ባይ ነው፡፡ ያ ደግሞ አገር ውስጥም ይንፀባረቃል፡፡ እነዚህ ነገሮች መልክ እንዳይዙ ያደረጉት የገዥው ፓርቲ ቀጥታም ሆነ ስውር እጆች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በሃገር ደረጃ ያለባት ፈተናም ይሄን የማለፍ እና ያለማለፍ ነው፡፡
ይሄ የዳያስፖራው ሁኔታ ሀገር ውስጥ ባሉ ተቃዋሚዎች ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ምንድን ነው?
በዚህ ምክንያት በአጠቃላይ ትግሉ ተጎድቷል፡፡ ክርር ወዳለው መስመር የመሰባሰብ ችግር አለ፡፡ አብዛኛው ሰውም በዚህ ሃይል ስር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሃገር ውስጥ ባለው ትግል ላይ ተፅዕኖ አለው፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን ባጠበበ ቁጥር ወደዚህ መሰሉ እንቅስቃሴ ብዙዎች መግባታቸው አይቀርም፡፡ ብሄረሰቦች እየተቻቻሉ፣ የተሻለች ዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን እንዳይፈጥሩ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ የገዥውን ፓርቲ አቅጣጫ መለወጥ ካልቻልን የትም አንደርስም፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩን የማስተካከል ኃላፊነት በግድም ሆነ በውድ የገዥው ፓርቲ ነው፡፡ በዳያስፖራው አካባቢ ላለው የከረረ ፖለቲካ ምንጩ ምንድን ነው? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ዋናው ምንጭ የፖለቲካ ምህዳሩ መጥበቡ፣ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የሚካሄድበት መድረክ መፈጠር ያለመቻሉ፣ ነፃ ሃሳብ የሚንሸራሸርበት ሚዲያ አለመኖሩ፣ በቀላል ቋንቋ ገዥው ፓርቲ “ስልጣን ወይም ሞት?” በሚለው አቋሙ መቀጠሉ ነው ይሄን የፈጠረው፡፡ ትግሉን ወደ ውጪ ያስወጣው እኮ ራሱ ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን የሚያሳድደውና ሰው ወደ ውጭ እንዲያይ የሚያደርገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ አገር ውስጥ ያለው ነገር ቢስተካከል የኢትዮጵያ ፖለቲካን ትግል ይዞ አሜሪካ ወይም አውስትራሊያ አሊያም ሌላ ሃገር የሚሄድበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄ አካሄድ ደግሞ ገዥውን ፓርቲም ቢሆን እየጠቀመው አይደለም፡፡ በዋናነት የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዲሰደድ ያደረገው ገዥው ፓርቲ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንዳይሰደድ ከፈለገ፣ እዚህ ያለውን የፖለቲካ ምህዳር መክፈትና ማስፋት አለበት፡፡
በአብዛኛው በዳያስፖራው አካባቢ የሚደረገው ትግል እየሰፋ የሚሄድበትና በዚያው መጠን ፖለቲካው የሚከርበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለውን ብዙ ሰው እየረሳ ነው፡፡ እዚህ ያለው የፖለቲካ ምህዳር ስለጠበበ፣ ስለማያሰራ፣ ወጣቶችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችን ስለሚያሳድድ ውጪ እየሄዱ እየተደራጁ፤ ውጪም ብቻ ሳይሆን ጫካም እየሄዱ እየተደራጁ፣ ባገኙት መንገድ ትግሉን መቀጠል ስለሚፈልጉ ነው፡፡
የዳያስፖራው ትግል ሃገር ውስጥ ባለው ስርአት ላይ ተጨባጭ ተፅዕኖ የመፍጠርና ለውጥ የማምጣት አቅም አለው ብለው ያስባሉ?
ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚደረገው ትግል ካልራቀ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ተጨባጭ የሆነ ለውጥ ማምጣት የሚችልበት እድል አለው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን ትግል በሃብት ሊረዳ ይችላል፡፡ በእውቀት፣ በዲፕሎማሲና በብዙ መንገድ ሊረዳ ይችላል፡፡ የኢትዮጵያ ባለስልጣናትም ጭምር አሁን የሚደረገውን የዳያስፖራውን ትግል እንደቀላል እያዩት አይደለም፡፡ ዳያስፖራው እኮ ምናልባትም የእነሱም የመጪው ጊዜ መኖሪያ ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት፣ ብዙ ወጪ እያወጡ ዳያስፖራ ውስጥ ኑሮአቸውን ለመመስረት እየሞከሩ ነው፡፡ የደርግ ባለስልጣናት ዛሬ ኑሮአቸው ዳያስፖራ ውስጥ ነው፡፡ ባለስልጣናት በሚሄዱበት ሃገር ምን እየገጠማቸው እንደሆነ እያየን ነው፡፡ እኛን በሃገራችን መኖር እንዳንችል አድርጋችሁ እናንተ እዚህ መቀመጥ አትችሉም እየተባሉ ነው፡፡ እነ ጁነዲን ሳዶ እኮ እየተደበቁ ነው የሚኖሩት፡፡ ሃገር ውስጥ ለሰሩት ወንጀል ምናልባት በህግ ልንጠየቅበት እንችላለን እያሉ ይጨነቃሉ፡፡ በሃገሪቱ ኢኮኖሚ ላይም የዳያስፖራው ሚና ቀላል አይደለም፡፡ በዓመት 4.5 ቢሊዮን ብር ወደ ሃገር ውስጥ ይልካሉ፡፡
በቅርቡ በአሜሪካ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከባንዲራ ጋር በተያያዘ ስለተፈጠረው ሁኔታ ምን ይላሉ?
የባንዲራው ጉዳይ ውስጥ ብዙ መግባት አልፈልግም፡፡ ኢህአዴግም ቢሆን ከማንም በላይ የባንዲራ ጠባቂ ነኝ ሊል የሚችል ድርጅት አይደለም፡፡ በተለይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ስለባንዲራ ምን ይሉ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ኢህአዴግ ያን ያል  የባንዲራ አስከባሪ መሆን አይችልም፡፡ ዋናው ነገር ኤምባሲዎች አካባቢ እንደዚያ ያለ ነገር ገፍቶ ከቀጠለ በአጠቃላይ ጥሩ ምልክት አይደለም፡፡ የሃገሪቱ ያለመቻቻል ፖለቲካ እዚያ ድረስ ሄዶ ሁላችንንም በማያስከብር መልኩ እየተንፀባረቀ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግስት የፖለቲካ ምህዳርን በመዝጋትና በማፈን ብዙ ነገሮችን አደርጋለሁ የሚለውን ደጋግሞ ቢያስብበትና ጩኸቱንም ቢሆን እዚሁ ሃገር ቤት ብንጯጯህ ይሻላል፡፡
ዳያስፖራው በተቻለው ሁሉ አሜሪካ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ተፅዕኖ እንድታሳርፍ ሲጥር መቆየቱ ይታወቃል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ በሰጡት መግለጫ፤ “ወዳጅነታችን ተጠናክሯል፣ ውጤታማ ውይይትም አድርገናል” ብለዋል፡፡ በዚህ ዙሪያ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
የአሜሪካ መንግስት ባለስልጣናት ፍቅራቸውና ሌላ ነገራቸው ብዙም አያሳስበኝም፡፡ እኔ የሚያሳስበኝ የቤት ስራችንን መስራትና አለመስራታችን ነው፡፡ እኔ ፖለቲካል ሣይንስ በተለይም የውጪ ፖሊሲ ላይ አስተምራለሁ፤ እናም “አሜሪካኖች ቋሚ ጥቅም እንጂ ቋሚ ፍቅር የላቸውም፡፡” ለምሣሌ የግብጽ መንግስት ገና መናጋት ሲጀምር “በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ወዳጃችን ነው” እያሉ ሲቀባጥሩ ነበር፡፡ ኋላ ላይ ግን ኦባማ “ሠላማዊ ተቃዋሚን መግደል ወንጀል ነው” ብሎ ተናገረ፡፡ ከዚያ በኋላ ጨዋታው ተቀየረ፡፡ ስለዚህ ዋናው ነገር ኢትዮጵያውያን በጋራ ትግሉን ማጠናከራቸው ነው፡፡ ያ ከሆነ የአሜሪካ መንግስት ትግሉን የማይደግፍበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ አሁን ሁለቱን መንግስታት ያወዳጀው የሽብር ጉዳይ ነው፡፡ ይሄ በግልጽ ይታወቃል፡፡ በፀረ-ሽብር ጨዋታ ውስጥ ተጠላልፈው ገብተው እያደረጉ ያለው ነገር ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን ዋናው እኔን የሚያስጨንቀኝ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ሃይሎች፣ የኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ሃይሎችና የኢትዮጵያ ሕዝብ የራሱን የቤት ስራ እየሰራ ነው? ለራሱ መብት፣ ክብርና ነፃነት እየታገለ ነው ወይ? የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
ካነሱት አይቀር አሁን ያለውን የተቃዋሚ ሃይሎች ፖለቲካ፣ የህዝቡን ፍላጐት እና የገዥው ፓርቲን ሁኔታ እንዴት ይገመግሙታል?
 ሁሉም ፓርቲ የአቅሙን ያህል እየሰራ ነው፡፡ የመከፋፈል ፖለቲካው ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡ ብዙ ፓርቲዎች የ97ቱን የመሠለ እንቅስቃሴ መፍጠር አልቻሉም፡፡ ያን ጊዜ ቢያንስ ሁለት ስብስቦች መፍጠር ተችሎ ነበር፤ አሁን ግን ሙከራዎች ቢኖሩም ወደፊት የሚያስኬድ አይመስልም፤ ክፍፍሉ አሁንም አለ፡፡ ነገር ግን ነፃና ፍትሃዊ የሚባለው አይነት የምርጫ ስርአት ከተዘረጋ ምንም ጥርጥር የለውም፣ ኢህአዴግ በአንድ ወር እንቅስቃሴ ይሸነፋል፡፡ ይሄን በሰሞኑ የመምህራን ስልጠና ላይም ተናግሬዋለሁ፡፡ ኢህአዴግን ለማሸነፍ ቀላል ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ ኢህአዴግ በአንድ በኩል ተቃዋሚዎች ተዳክመዋል ይላል፤ መቼም ሰይጣን አይደለም ተቃዋሚዎችን የሚያዳክመው፤ ኢህአዴግ ራሱ ነው፡፡ አሞሌና ዱላ ይዞ የሚዞረው ኢህአዴግ ነው፡፡ በአሞሌ ያልወደቀ በዱላ ይወድቃል፡፡ ኢህአዴግ አሞሌና ዱላ ይዞ መዞር ካቆመ፣ እሱን ማሸነፍ ትልቅ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንስ ከዚያ በኋላ ሃገር ለመምራት ተቻችሎ፣ ተግባብቶ የጋራ የፖለቲካ አጀንዳ ቀርፆ ለመንቀሳቀስ ይቻላል ወይ የሚለው ነው እኔን የሚያሳስበኝ፡፡
ኢህአዴግን ለማሸነፍ ያስቸግራል የሚል ግምት ግን የለኝም፡፡ ዋናው ኢህአዴግ የራሱን ዳኛ ይዞ ወደ ጨዋታ ሜዳ አለመግባቱ ነው፡፡ አሁን ዳኛም ተጫዋችም ነው፡፡ ሁልጊዜ ዳኛም ተጫዋችም ሆኜ እቀጥላለሁ ካለ ግን ምናልባትም እኛም ኢህአዴግም የማንፈልገው ነገር ኢትዮጵያ ውስጥ ሊፈጠር ይችላል፡፡
በአንድ በኩል ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ አይደለም የሚል ትችት ከተቃዋሚዎች ሲሰነዘር ይደመጣል፡፡ እነዚያው ፓርቲዎች ግን ባላመኑበት ምርጫ ሲሳተፉ እንመለከታለን፡፡ ቦርዱ ገለልተኛ አይደለም ካሉ በኋላ በምርጫው መሳተፍ ተገቢ ነው ይላሉ?
ሁለት ነገር ነው ያለው፡፡ ተቃዋሚ ስንል ህዝብ ተቃዋሚ ናቸው ብሎ የሚያምንባቸውን ነው እንጂ ኢህአዴግ የሚቀልባቸውን ማለት አይደለም፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች ይህ አይነቱ አዙሪት እንዲያበቃ በጋራ “አንሳተፍም” የሚል አቋም መያዝ አለባቸው፡፡ ብዙ ጊዜ እንዲህ ያለ ሃሳብ ማግኘት ያስቸግራል፡፡ አንዱ ትልቁ ችግር ይሄ ነው፡፡ ለምሣሌ በ2002 ምርጫ መድረክ አካባቢ የተሠባሰብነው ወደ ምርጫ ያለመግባት ሃሳብ ነበረን፤ ነገር ግን መኢአድ የስነምግባር ደንቡን በመፈረሙ፣ የተቃዋሚዎችን የጋራ አቋም ስላላገኘን፣ ጨዋታው ከሚበላሽብንና የፖለቲካ ትርፍ ቢገኝ ብለን ገባንበት እንጂ ውጤት ያመጣል ብለን አይደለም፡፡ የ97 ምርጫን ካየን፣ ህብረት በጨዋታው ሜዳ ላይ ተደራድሯል፡፡ የሚፈለገውን በአንድነት ገፍተን ባናገኝም የተወሰኑ ጥቃቅን ነገሮች ተሻሽለዋል፡፡
የሚዲያ አጠቃቀምን ማንሳት እንችላለን፡፡ በወቅቱ ኢህአዴግ የቆመበት መሬት እስኪከዳው ድረስ የገፋነው በሱ ነው፡፡ የ2002 ምርጫ ላይ ግን መግባቱ ጥቅም አልነበረውም፡፡ አሁንም የተቃዋሚዎች ሙሉ አቋምና ውሣኔ እስካልተገኘ ድረስ አንዱ ገብቶ ሌላው ሲቀር አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንዴ መቀመጫም ባናገኝ የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት የምንገባበት አጋጣሚም አለ፡፡ ሌላው ሁለት ምርጫ ላይ ያልተሳተፈ ይሰረዛል የሚል ህግ አለ፤ ያንን በመፍራትም ይገባል፡፡
አሁንስ የ8 ወር እድሜ ለቀረው የ2007 ብሔራዊ ምርጫ የተቃዋሚዎች ዝግጅት ከኢህአዴግ አንፃር እንዴት ይታያል?
ተቃዋሚዎች ዝግጅት ይኖራቸዋል፤ ነገር ግን ዋናው ጉዳይ የፖለቲካ ምህዳሩ እስካልሰፋ የትም አይደረስም፡፡ የ2007 ምርጫን ከአሁኑ ገምግም ከተባልኩ፣ ምናልባት ኢህአዴግ የተወሰኑ የመቀመጫ ፍርፋሪዎችን ለተቃዋሚዎች ለቆ እንደገና አሸነፍኩ ሊል ይችላል፡፡ ያ ማሸነፍ ለኢትዮጵያም፣ ለኢህአዴግም ለሁሉም የሚጠቅም አይመስለኝም፡፡ ምንጊዜም ህዝብን ተስፋ አታሳጣ፤ ህዝብን ተስፋ ካስቆረጥከው ተስፋ የቆረጠ ስራ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ አሁንም ሃገር ውስጥም ሆነ ውጪ ብዙ ነገሮች ጤናማ አይደሉም፡፡
ቀደም ብለው እንደነገሩኝ፤ በአሜሪካ ቆይታዎ ኢሣት ቴሌቪዥን ላይ ሰፊ ቃለ ምልልስና አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ደግሞ ጣቢያውን የ“አሸባሪዎች” ልሣን ነው በማለት የፖለቲካ ድርጅቶች ከጣቢያው ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲገቱ አስጠንቅቋል፡፡ ከዚህ አንፃር ጉዳዩ ስጋት ውስጥ አልከተትዎትም?
“ኢሣት” እንግዲህ የኢህአዴግ ወዳጅ ሃገር በሚባለው አሜሪካ በነፃ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀስ ጣቢያ ነው፡፡ ድጋፍ ከማህበረሰቡ እያሰባሰበ ነው የሚሠራው፡፡ እዚያ ጣቢያ ላይ መረራ የራሱን አስተያየት ነው የሰጠው እንጂ የኢሣትን ፕሮፓጋንዳ አይደለም ያንፀበረቀው፡፡
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ነው አስተያየቴን የሰጠሁት፡፡ ኢሣት ጠመንጃ የለውም፣ የትጥቅ ትግልም እያካሄደ አይደለም፡፡
 ስለዚህ እኔ እንደ ከባድ ነገር አላየውም፡፡ በነገራችን ላይ የኢህአዴግ ባለስልጣናትም አልፎ አልፎ አስተያየት ይሰጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥንን ባያፍን እኮ “ኢሣት” ጋ የምሄድበት የተለየ ምክንያት የለኝም፡፡ የውጪ ሚዲያ ጋ እንዳንሄድ ከፈለገ፣ የሀገር ውስጡን ይስጠን፡፡ መረራ “ኢሣት”ን ባይጠቀም ሌሎች ብዙ ሺህ ምሁራን ይጠቀሙበታል፡፡ እንደሚታወቀው የኛ ፓርቲ የሽብር ፕሮጀክት የለውም፤ በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ ነው የሚታገለው፡፡ “ኢሳት” ላይ የምናገረው ሃገር ውስጥ ባለው ቴሌቪዥን ጣቢያ እንድናገር እድል ቢሰጠኝ የምናገረውን ነው፡፡ እኔ ውጪም ሆነ ውስጥ ቋንቋዬ አንድ ነው፡፡

Read 5149 times