Monday, 03 November 2014 07:37

የ“የኛ”ን አርማ የያዘ 5 ሚሊዮን ጠርሙስ አምቦ ውሃ ሊሰራጭ ነው

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(0 votes)

አምቦ ጠበል የ “የኛ”ን አርማ የያዘ አምቦ ውሃ በማምረት፣በአዲስ አበባና በአማራ ክልል ሊያሰራጭ መዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡ አርማውን የያዘ ስቲከሮችን ለማሰራት ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ እንደፈጀ  ተገልጿል፡፡
ያለ ዕድሜ ጋብቻና እርግዝና፣ የፆታ ጥቃትና መሰል ችግሮች ላይ ለውጥ ለማምጣት የሚሰራው “የኛ” ፕሮግራም፤ አራተኛ ምዕራፉን በነገው እለት እንደሚጀምር በይፋ ባስታወቀበት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የአምቦ ውሃ ተወካይ እንደተናገሩት፤ ድርጅቱ በህብረተሰቡ ውስጥ ያለውን ሃላፊነት ለመወጣትና በ“የኛ” ፕሮግራም እየተከናወነ ያለውን ስራ ለማገዝ፣ ስምምነት መፈራረማቸውን ጠቁመው ይህንን አይነቱን የትብብር ሥራ ሲሰሩም ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የ “የኛ” ዳይሬክተር ወ/ሮ አይዳ አሸናፊ በበኩላቸው፤ “በፕሮግራሙ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን ለማሳካት ከኢትዮጵያዊውና ከባህላችን ከተወለደው አምቦ ጠበል ጋር መተባበሩ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፤ ከድርጅቱ ጋር የትብብር ስምምነት ተፈራርመናል፡፡” ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባና በአማራ ክልል  ይሰራጫል ተብለው የታሰቡት 5 ሚሊዮን ጠርሙስ የአምቦ ውሃ ምርቶች፣ በመጪዎቹ ስድስት ወራት ተሰራጭተው እንደሚጠናቀቁ ተገልጿል፡፡ 

Read 2042 times