Monday, 03 November 2014 07:44

ምርጫ ቦርድ የፓርቲዎችን ቅሬታ ለመፍታት ተዘጋጅቻለሁ አለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

*መጪው አገር አቀፍ ምርጫ ግንቦት 16 ይካሄዳል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የዘንድሮ አገራዊ ምርጫ የጊዜ ሰሌዳን ይፋ ያደረገ ሲሆን በተወዳዳሪ ፓርቲዎች የሚቀርቡ ቅሬታዎችን ለመፍታትም ቦርዱ ከምንጊዜውም በተሻለ መዘጋጀቱን አስታውቋል፡፡
ከትንት በስቲያ በሚኒስትር ማዕረግ የቦርዱ ሰብሳቢ ፕ/ር መርጋ በቃና እና ምክትሎቻቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤የ2007 አጠቃላይ ምርጫ ድምጽ የመስጫ ቀን ግንቦት 15 እንደሆነና የመጨረሻ የምርጫ ውጤቱም ሰኔ 15  ይፋ እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡
በምርጫ ለመወዳደር የሚችሉ ፓርቲዎች የመወዳደሪያ ምልክታቸውን ከህዳር 15 እስከ ህዳር 30 የሚመርጡ ሲሆን ተወዳዳሪዎች የድጋፍ ፊርማ የሚያሰባስቡት ከታህሳስ 6 እስከ ታህሳስ 25 ይሆናል፡፡
በምርጫ የሚወዳደሩ የፖለቲካ ድርጅቶችና በግል ለመወዳደር የድጋፍ ፊርማ ያሰባሰቡ እጩዎች፣ በምርጫ ክልል ፅ/ቤትና የምርጫ ጣቢያ ለይተው የመደቧቸውን ወኪሎቻቸውን ለምርጫ ክልል ፅ/ቤት የሚያሳውቁት ከታህሳስ 5 እስከ ግንቦት 5 እንደሆነ የቦርዱ የጊዜ ሰሌዳ ያመለከተ ሲሆን የፖለቲካ ፓርቲዎች የእጩ ተወዳዳሪዎች ምዝገባ ከታህሳስ 16 እስከ ጥር 27  ይከናወናል ተብሏል፡፡
የመራጮች ምዝገባ የሚከናወነው ከጥር 1 ቀን እስከ የካቲት 12 ሲሆነ የተወዳዳሪ እጩዎች ማንነት ለህዝብ ይፋ የሚደረገው የካቲት 1 ቀን እንደሆነ ታውቋል፡፡ እጩዎች የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን የካቲት 7 ጀምረው ግንቦት 13 ከምሽቱ 12 ሰዓት ያጠናቅቃሉ ተብሏል፡፡ የድምፅ መስጫ እለት ግንቦት 16፣  በጊዜያዊነት ውጤቱ ይፋ የሚደረገው ግንቦት 23፣ አጠቃላይ የምርጫ ውጤት የሚነገረው ደግሞ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም እንደሆነ  የቦርዱ ኃላፊዎች ገልጸዋል፡፡
ለምርጫው አስፈላጊ የሆኑ ቅድመ ዝግጅቶች በአብዛኛው ተጠናቀዋል ያሉት የቦርዱ ኃላፊዎች፤ ያለፉትን አራት ምርጫዎች ተመክሮ ያገናዘበ የምርጫ ዝግጅት መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ ከፓርቲዎች የሚቀርቡ ማናቸውንም ቅሬታዎች እየተቀበሉ መሆኑን የገለፁት ፕ/ር መርጋ፤ የቢሮ፣ የመሰብሰቢያና ሌሎች  ችግሮችን ጨምሮ የተለያዩ ቅሬታዎች ደረጃ በደረጃ እንዲፈቱ ጥረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
75 የፖለቲካ ፓርቲዎች ተመዝግበው እውቅና ማግኘታቸውን የጠቆሙት ሰብሳቢው፤ በአስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ ሁሉንም ፓርቲዎች ማወያየት እንችላለን ብለዋል፡፡

Read 1346 times