Monday, 03 November 2014 07:45

አምነስቲ በኦሮሚያ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እየተፈጸመ ነው

Written by 
Rate this item
(2 votes)
  • በ“ክልሉ ባለፉት ሶስት አመታት ብቻ 5ሺህ ያህል ሰዎች ታስረዋል”
  • የእንግሊዝ ጋዜጦች ኢትዮጵያ በየአመቱ የሚሰጣትን ከ9 ቢ. ብር በላይ እርዳታ ተቃውመውታል
  • የኢትዮጵያ መንግስት የእነአምነስቲን ሪፖርት መሰረተ ቢስ ነው ይላል

        በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ሶስት አመታት 5ሺህ ያህል ሰዎች ኦነግን ትደግፋላችሁ፣ መንግስትን ትቃወማላችሁ በሚል ጥርጣሬ  ክስ ሳይመሰረትባቸው እንደታሰሩና በርካቶችም ለስቃይና ለሞት እንደተዳረጉ “አምነስቲ” የገለጸ ሲሆን የእንግሊዝ ጋዜጦች በየአመቱ፣ ለኢትዮጵያ የሚሰጠውን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ እርዳታ ተቃውመውታል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተቋማት የሚያወጡት ሪፖርት፤ የውጭ ሃይል ጣልቃገብነትን የሚያራምድ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ይላል፡፡
አምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፤ የኢትዮጵያ መንግስት በኦሮሞ ተወላጆች ላይ የሚፈጽመው በደል እየከፋ መምጣቱንና ሰላማዊ ተቃውሞ ባደረጉ ዜጎች፣ በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትና በተማሪዎች እንዲሁም በክልሉ በሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ በጥርጣሬ ላይ የተመሰረተ እስር፣ ስቃይና ግድያ እንደሚፈጸም ገልጿል፡፡
በክልሉ በርካቶች ለእስር የተዳረጉት ሌሎች ሰዎች መንግስትን እንዲቃወሙ አነሳስታችኋል በሚል እንደሆነ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የተጠርጣሪዎች ቤተሰቦችም ጥቃት እንደሚደርስባቸው አስታውቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ የጦር ካምፖች ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ታስረው እንደሚገኙና አብዛኞቹም ከጠበቆችና ከቤተሰቦቻቸው ጋር እናዳይገናኙ እንደተከለከሉ ሪፖርቱ አብራርቷል፡፡
አለማቀፋዊና ክልላዊ የሰብዓዊ መብት ተቋማት በአፋጣኝ በጉዳዩ ጣልቃ ሊገቡና በክልሉ የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ገለልተኛ የሆነ ምርመራና ማጣራት ሊደረግባቸው ይገባል ብሏል አምነስቲ፡፡
በተያያዘ ዜና የእንግሊዝ መንግስት ከፍተኛ እርዳታ ከሚሰጣቸው አገራት ኢትዮጵያ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ትናንት የዘገበው ቴሌግራፍ፣ ባለፈው አመት ብቻ ከ329 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ እርዳታ መቀበሏን ጠቅሶ የጸጥታ ሃይሎች ዜጎችን ለሚያሰቃዩባት ኢትዮጵያ እርዳታ መሰጠቱን ተቃውሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በየአመቱ ከእንግሊዝ የሚያገኘውን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ እርዳታ ለልማት ማዋል ሲገባው ዜጎችን ለመጨቆን እያዋለው ይገኛል ያለው ጋዜጣው፣ ድርጊቱን አውግዞታል፡፡ ዴይሊ ሜይልም በተመሳሳይ ሁኔታ እንግሊዝ ባለፉት ሶስት አመታት ብቻ ለኢትዮጵያ 1 ቢሊዮን ፓውንድ በእርዳታ መስጠቷን አስታውሶ፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባወጣው ሪፖርት በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በመንግስት ሃይሎች ለእስራት፣ ለሞትና ለስቃይ እየተዳረጉ እንደሚገኙ ማስታወቁን ገልጧል፡፡

Read 1901 times