በኢትዮጵያ ከ104 ሺ በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ይገኛሉ
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፣ በየዕለቱ ከ200 በላይ ኤርትራውያን ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ መግለጹን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በኤርትራ መንግስት አስተዳደር የተማረሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ያስታወሰው የተመድ ሪፖርት፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን አደገኛ ድንበር እያቋረጡ በህገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ስደተኞች ቁጥር ካለፈው መስከረም ወር አንስቶ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ነው ብሏል፡፡ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ ከ3ሺህ 500 በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን የገለጸው የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሪፖርት፣ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ቁጥር ከ104 ሺህ በላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
የስደተኞችን ቁጥር እንዲጨምር ያደረገው ምክንያት በሪፖርቱ እንዳልተገለጸ የጠቆመው ዘገባው፤ይሄም ሆኖ ግን አንዳንድ የመብት ተሟጋች ቡድኖች ኤርትራውያን በአገሪቱ መንግስት የሚደርስባቸው ጭቆና እየከፋ መምጣቱ ለስደቱ መባባስ በምክንያትነት እንደሚያስቀምጡት ገልጧል፡፡
Published in
ዜና