Saturday, 08 November 2014 11:18

አምባገነንነት እንደ ፖሊዮ ከምድረገፅ መጥፋት አለበት!

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(5 votes)

         ባለፈው ሳምንት ቡርኪናፋሶን ለ27 ዓመታት እንደ ግል ንብረታቸው ሲያዙባት የከረሙት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬ፤ የሥልጣን ዘመናቸውን ለማራዘም ሲሉ ህገመንግስቱን ለማሻሻል ያደረጉት (ንቀትና ድፍረት የተቀላቀለበት ነው) ሙከራ ያስከተለው ውጤት ያልጠበቁት ነበር፡፡ (አመዳቸውን ቡን ሳይል አልቀረም!) ምንም ቢሆን የህዝብ አመፅ አይጠብቁማ፡፡ መቼም የሥልጣን እህል ውሃቸው ቢያልቅ ነው እንጂ አምባገነኖች እንዲህ በቀላሉ ከቤተመንግስት እኮ አይወጡም፡፡ (ያውም በአንዲት ቀን አብዮት?!) አመጽና ተቃውሞን በሃይል ለመመከትና ለማፈን ሁሌም ታማኝና አስተማማኝ ወታደራዊ ኃይል ከጎናቸው አይጠፋም፡፡ የስልጣን ገመዳቸው ተበጠስ ያለው ጊዜ ግን ወታደሩም ፊቱን ያዞርባቸዋል፡፡ በአምባገነኖቹ የአፍሪካ መሪዎች በእነ ጋዳፊ፣ ሁስኒ ሙባረክ…አይተነዋል፡፡
የአምባገነን መሪዎችን ባህሪና ነገረ ስራ እንደ አዲስ ለመፈተሽ ያነሳሱኝ (Inspiration ሆነውኛል!) ከስልጣን ከተወገዱ የሳምንት ዕድሜ ብቻ ያስቆጠሩት የቡርኪናፋሶው የቀድሞ መሪ ናቸውና ምስጋና ይገባቸዋል (አምባገነን ማመስገን ነውር ነው እንዳትሉኝ!) እናላችሁ ፍተሻዬን ውጤታማ ለማድረግ በአምባገነን መሪዎች ዙሪያ ያልበረበርኩት መረጃ የለም፡፡ (ዕድሜ ለእነ ጐጉል!) የእያንዳንዱን አምባገነን ታሪክ (ሥልጣን ከተቆናጠጠበት እስከተገረሰሰበት) በሰከንዶች ቅጽበት ማግኘት ይቻላል፡፡ ዲሞክራሲያዊ መብቶች ባልተከበሩበት አገር፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሊስፋፋ እንደማይችል ልብ ይሏል፡፡ (ነፃነት ሳይኖር ፈጠራ እሺ አይልም!) በነገራችሁ ላይ “ስኬታማ አምባገነን የመሆን ምስጢር” በሚል ርዕስ በታተመ መጽሐፍ ላይ እንዳነበብኩት፤ አምባገነን መሪዎች በአገር ስም ብዙ ገንዘብ እየተበደሩ፣ ቀጣዩን ትውልድ ለዕዳ በመዳረግ ዝነኛ ሲሆኑ መሰረተ ልማቶችን ለማስፋፋት ደሞ ዳተኞች ናቸው፡፡ አቅም በማጣት ብቻ እንዳይመስላችሁ፡፡ አንዳንዴ ሆን ብለው ነው፡፡ መንገድ ከተስፋፋ የሚቀናቀናቸው የፖለቲካ ቡድን ከሸመቀበት ወጥቶ ቤተመንግስት ድረስ ዘው እንዳይል ክፉኛ ይሰጋሉ፡፡ (የስልጣን አወጣጣቸውን ያውቁታላ!!)
እናላችሁ… ዛሬ የጥቂት አምባገነን መሪዎችን እንግዳ ባህርያት አብረን እየቃኘን እንደመም፡፡ እናንተ…ሥልጣን እንዲህ ያሳብዳል? ሥልጣን እንዲህ ያቃዣል? ሥልጣን እንዲህ ያስዋሻል? ሥልጣን እንዲህ ያስቀላምዳል? በሉ አብረን “አጃኢብ” እንበል፡፡
ራሳቸውን “የዕድሜ ልክ ፕሬዚዳንት” ብለው በመሰየም የሚታወቁት የሃይቲው የቀድሞ አምባገን መሪ (እ.ኤ.አ ከ1907-1971 ገዝተዋል) ፍራንሶይስ ዱቫሊየር፤ ለ14 ዓመት የዘለቀው የስልጣን ዘመናቸው በጥርጣሬና በፍርሃት የተሞላ ነበር፡፡ (ሥራቸው እኮ ነው የሚያስፈራቸው!?) በነገራችሁ ላይ በየትኛውም የዓለም ክፍል የነበሩና ያሉ አምባገነኖች በአብዛኛው ይመሳሰላሉ (ለእነሱ “የእናት ሆድ ዥንጉርጉር” አይሰራም!) እናላችሁ… የሃይቲው አምባገነንም ቢፈሩና ቢጠራጠሩ አይፈረድባቸውም፡፡ አንደኛ የፈፀሙትን ግፍና ጭካኔ ያውቁታል፡፡ ሁለተኛ ሥልጣን አንዴ ከእጅ ከወጣ አይመለስም፡፡
ዱቫሊየር ለስልጣናቸው ስጋት የመሰሏቸውን ሁሉ አንድ በአንድ አስወግደዋል፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን (ቦይ ስካውቶችን ሳይቀር) ያገዱ ጠርጣራ መሪ ነበሩ፡፡ ባዕድ አምልኮ የተጠናወታቸው የሃይቲው የቀድሞ መሪ፤ ወር በገባ በ22ኛው ቀን የሚጠብቀኝ መንፈሳዊ ኃይል አለ ብለው ያምኑ እንደነበር ይነገራል፡፡ በስልጣን ዘመናቸው የመጨረሻ ዓመታትም ወር በገባ በ22ኛው ቀን ብቻ ነበር ከቤተመንግስት የሚወጡት፡፡ (ስልጣን ሊያልቅ ሲል ያሳሳል!)  
አንዴ የሃይቲ የፓርላማ ቡድን መሪ የነበሩ ክሊመንት ባርቦት የተባሉ የፖለቲካ ተቀናቃኛቸው፤ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርገውባቸው ተሰውረው ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ እኚህ “ህገመንግስት በሃይል ለመናድ” የሞከሩ ተቀናቃኝ፤ ከተሸሸጉበት ተይዘው እንዲመጡላቸው ለፖሊስ ትዕዛዝ ያስተላልፋሉ፡፡ ሆኖም ፖሊስ “አስሼ አስሼ አጣኋቸው” ይላቸዋል፡፡ ይሄኔ ዱቫሊየ ምን ቢሉ ጥሩ ነው? “ባርቦት ራሱን ወደ ጥቁር ውሻ ቀይሮ ነው” አሉና አረፉት፡፡ ከዚያም በሃይቲ የሚገኙ ጥቁር ውሻዎች በሙሉ እንዲገደሉ አዘዙ (የሃይቲ ውሾች ሳይቀሩ የአምባገነን ሰለባ ሆኑ!) የማታ ማታ ግን የተሰወሩት ባርቦት ተገኙ፡፡ እሳቸውንም አልማሯቸውም፡፡ የሞት ቅጣት ፈረዱባቸው፡፡ ጭንቅላታቸውን ቆርጠውም ለሚያምኑበት ባዕድ መንፈስ እንዳስቀመጡለት ይነገራል፡፡
አንድ ጊዜ ምን እንደታያቸው አይታወቅም፡፡ ምርጫ ይካሄድ አሉ - ነፃ ምርጫ፡፡ 100 ፐርሰንት ድምፅ አግኝተው አሸነፉ (ድንቄም ነፃ ምርጫ!) በነገራችሁ ላይ እኚህ አምባገነን መሪ ስድስት የግድያ ሙከራዎችን (በራሳቸው ጥበብ ይሁን በባዕድ መንፈስ ኃይል አልታወቀም!) ...አምልጠዋል፡፡ በመጨረሻም የተወሰነ ጊዜ ታመው እ.ኤ.አ በ1971 ዓ.ም ሞቱ፡፡ ህዝቡ እሳቸውን ቢገላገልም የሥልጣን መንበሩን የተረከበው ልጃቸው ነበር፡፡
ወደ አፍሪካ ስንመጣ የቀድሞውን የኡጋንዳ አምባገነን መሪ ኢዲ አሚንን (ከ1920-2003) እናገኛለን፡፡ እኚህን አምባገን ሳስባቸው የስፔናዊው ደራሲ ሴርቫንቴ “ዶን ኪሆቴ” መፅሃፍ ላይ ያለው ዋና ዶን ኪኾቴ የተባለ ገፀ ባህርይ ትዝ ይለኛል (አወይ መመሳሰል አሉ!) ራሳቸውን “የህይወት ዘመን ፕሬዚዳንት”፣ “የታላቋ ብሪታኒያ ግዛት አስገባሪ”፣ “የስኮትላንድ የመጨረሻው ንጉስ” እያሉ የሚጠሩት ኢዲ አሚን፤ ፊልድ ማርሻል የተባለውን የመጨረሻ ከፍተኛ ወታደራዊ ማዕረግ ለራሳቸው የሸለሙ ዕብሪተኛ መሪ ነበሩ፡፡
የኢዲ አሚን አስገራሚና ቅጥ አምባሩ የጠፋ ባህርይ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ የአንድ ታዋቂና ሃብታም እስያዊ ቤተሰብ ልጅ የሆነች ኮረዳን ለትዳር ጠይቀው አዎንታዊ ምላሽ ያላገኙት አሚን፤ የአፀፋ እርምጃቸው አስደንጋጭ ነበር፡፡ በኡጋንዳ የሚኖሩ እስያዊያንን በሙሉ ከአገሪቱ አባረሩ፡፡ (እብሪት ነው እብደት?) የአፍሪካ ህብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ የሰሩት አስገራሚ ድራማም ተጠቃሽ ነው፡፡ ወደ ስብሰባው አዳራሽ የገቡት ዙፋን በሚመስል ወንበር ላይ ተቀምጠውና አራት ነጮች ከእነ ወንበራቸው ተሸክመዋቸው ነበር፡፡ የዚህን ምክንያት በአግራሞት ለተሞሉት የአፍሪካ ሚኒስትሮች ሲያስረዱም፤ “እኛ አፍሪካውያን አውሮፓውያንን ስንሸከም ኖረናል፡፡ አሁን ደግሞ የሚሸከሙን እነሱ ናቸው፡፡ እኛ አሁን ጌታ መሆናችንን ለማሳየት ብዬ ነው” አሉ - ሞኝ ይሁኑ ብልህ የማይታወቁት አሚን፡፡ ኢዲ አሚን ይሄ ተግባራቸው እንዳሰቡት አድናቆትን አላተረፈላቸውም፡፡ እንደውም በአፍሪካ መሪዎች ዘንድ ክፉኛ አስተችቷቸዋል (ሌሎቹም ከእሳቸው ብዙ ባይለዩም!)
ኢዲ አሚን፤ ዋና ፉክክራቸው ከእንግሊዟ ንግስት ኤልዛቤት ጋር ነበር (ንግስቲቷ ነገሬ ባትላቸውም!) እናም አንድ ጊዜ “የጋራ ገበያ አገራት ሊቀመንበር መሆን ያለብኝ እኔ እንጂ ንግስቲቷ አይደለችም” ሲሉ በድፍረት ተናግረው ነበር (አምባገነንነት ላይ እብደት ሲታከልበት ውጤቱን አስቡት!) እኔ መቼም ሰውየው “አምባገነን ነበሩ” በሚል ብቻ አላልፋቸውም፡፡ እንዴ ከዚህ የበለጠ እበደት አለ እንዴ? በነገራችሁ ላይ አሚን…ለንግስት ኤልዛቤት በርካታ የፍቅር ደብዳቤዎችን እንደፃፉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ (ንግስቲቱ ምን ብለው ይሆን?)
አምባገነኑ መሪ፤  ዋና ዋና የፖለቲካ ተቀናቃኞቻቸውን አድራሻ በማጥፋት የሚደርስባቸው አልነበረም፡፡ እንዴት? ለኢዲ አሚን ቀላል ነበር፡፡ ያስገድሏቸዋል፡፡ ይገድሏቸዋል፡፡ የእሳቸው ነገር በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ የሰው ስጋ ይበሉ ነበር ይባላል፡፡ ተቀናቃኞቻቸውን ካስገደሉ ወይም ከገደሉ በኋላ  አንድም ራሳቸው ይበሏቸዋል አሊያም ደሞ ለለማዳ አዞዎቻቸው ቀለብ ያደርጓቸዋል ይባል ነበር፡፡ ይሄ በሁነኛ ማስረጃ ባይረጋገጥም በአንድ ወቅት አማካሪያቸውን ከእራት በፊት ጠርተው፤ “ያንተን ልብ እፈልገዋለሁ፤ ልጆችህንም ልበላቸው እሻለሁ” በማለት ክው እንዳደረጉት ተዘግቧል፡፡
አሚን ከአምስት በላይ ሚስቶች የነበራቸው ሲሆን (በተመሳሳይ ጊዜ እኮ ነው!) ከእነዚህ ሚስቶቻቸውም ከደርዘን በላይ ልጆችን ወልደዋል፡፡ አሳዛኙ ነገር አንደኛዋ ሚስታቸው በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድላ ፍሪጅ ውስጥ መገኘቷ ነው፡፡ (የአምባገነንነት መጨረሻ ጭራቅነት ሳይሆን አይቀርም!!)
እ.ኤ.አ ከ1940-2006 ዓ.ም የቱርክሜኒስታን ፕሬዚዳንት የነበሩት ሳፓርሙራት ኒያዞቭ ደግሞ በህዝባቸው ውስጥ የራሳቸውን አምልኮተ-ስብዕና በመገንባት ወደርየለሽ ነበሩ፡፡ 15 ሜ. (50 ጫማ) ቁመት ያለው የወርቅ-ቅብ ሃውልታቸውን በቁማቸው ያሰሩ ዕብሪተኛ መሪ ናቸው፡፡ ሃውልታቸው ሁልጊዜ ፊቱ  ወደ ፀሐይ አቅጣጫ እንዲሆን ታስቦ የሚሽከረከር ሆኖ ነበር የተሰራው፡፡
ፎቶአቸውን በየግንቡና በየህንፃው ላይ ማየት የሚያስገርም አልነበረም፡፡ በአገሪቱ የገንዘብ ኖቶች ላይ ሳይቀር ምስላቸው ነበረ፡፡ አብዛኛው ህዝብ በድህነት ሲዳክር በነበረበት በዚያ ዘመን ኒያዞቭ፤ በበረሃነቷ በምትታወቀው ቱርክሜኒስታን እምብርት ላይ ግዙፍ የበረዶ ቤተመንግስት ያሳነፁ አምባገነን ነበሩ፡፡ (በነገራችሁ ላይ ሰሞኑን ቢቢሲ እንደዘገበው፤ የአሁኑ የቱርክ መሪ ከ600 ሚ.ዶላር በላይ አውጥተው ያሳነፁት ቤተመንግስት የህዝብ ተቃውሞ አስነስቷል!) አምባገነኖች አንድ ናቸው አልተባባልንም!
ሰውየው እልም ባለ በረሃ ላይ ሰው ሰራሽ ሃይቅ እንዲገነባላቸውም ትዕዛዝ ሰጥተው ነበር፤ ይሰራ አይሰራ ባይገለፅም፡፡ እኚህ አምባገነን እንደ ሌሎች አምባገነኖች ሁሉ ሥልጣን በያዙ ማግስት የመጀመሪያ ሥራቸው ያደረጉት የመንገዶችን፣ ህንፃዎችን፣ ከተሞችን፣ ፓርኮችን ወዘተ… ስያሜዎች መቀየር ነበር (አብዛኞቹን በራሳቸው ስም ሰይመዋቸዋል!) ይሄ ብዙም ላያስገርም ይችላል፡፡ (አምባገነን ሁሉ ያደርገዋላ!) በጣም  የሚገርመው ግን ምን መሰላችሁ? የዓመቱን ወራት… እነ ጃንዋሪ፣ ፌብሯሪን በራሳቸው፤ በቤተሰባቸውና በመጽሐፋቸው ስም መሰየማቸው ነው፡፡ (አጃኢብ እኮ ነው!) ሌላው ቀርቶ Bread ወይም “ዳቦ”ን እንኳን አልተውም፡፡ በእናታቸው ስም ሰይመውታል፡፡
አምባገነኑ የቱርክሜኒስታን የቀድሞ መሪ ይበልጥ የሚታወቁት ግን በደነገጓቸው አስገራሚ ህጐች ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ እ.ኤ.አ በ1997 ዓ.ም ሲጋራ ማጨስ ማቆማቸውን ተከትሎ ሚኒስትሮቻቸው በሙሉ እንደሳቸው ማጨስ እንዲያቆሙ ጥብቅ ትዕዛዝ ሰጥተው ነበር፡፡ እንደ ሳዳም ሁሴንና ጋዳፊ ሁሉ እሳቸውም መፅሃፍ ፅፈዋል፡፡ (አምልኮተ - ስብዕና የመገንባት አባዜ እኮ ነው!)የመፅሃፉ ርዕስ “ሩክህናማ” ወይም “የነፍስ መፅሃፍ” የተሰኘ ሲሆን ትክክለኛውን መንገድ የሚያስተምርና ከአሉታዊ ተፅዕኖዎች የሚከላከል እንደሆነ ይነገርለት ነበር፡፡ የሚያስገርመው ታዲያ ምን መሰላችሁ? ይሄ መፅሃፍ በት/ቤቶችና ዩኒቨርሲቲዎች የትምህርት ሥርዓት ውስጥ እንዲካተት መደረጉ ነው፡፡ በዚህ ብቻ ግን አያበቃም፡፡ የመንግስት ሠራተኞች ከስራቸው እንዳይባረሩ ከፈለጉ መጽሐፉን በቃላቸው መሸምደድ ይጠበቅባቸው ነበር፡፡ ዜጐች የመንጃ ፈቃድ ሊያወጡ ሲሉ ዋናው መስፈርት የፕሬዚዳንቱን መጽሐፍ ከጫፍ እስከጫፍ እጥብ ማድረግ ነው፡፡ ከመጽሐፉ የወጡ ጥያቄዎችን በተገቢ ሁኔታ ያልመለሰ መንጃ ፈቃድ አይሰጠውም፡፡ (የአምባገነንነትን ጥግ አያችሁልኝ!) ፕሬዚዳንቱ የደነገጓቸውን ህጐች ረሳናቸው እኮ፡፡ ወንዶች ፀጉርና ፂም እንዳያስረዝሙ እገዳ ተጥሎባቸው ነበር፡፡ ለቲቪ ዜና አቅራቢዎች ሜክአፕና የወርቅ ጥርስ አይፈቀድም ይላል - ህጋቸው፡፡
አምባገነኑ የቱርክሜኒስታን የቀድሞ ፕሬዚዳንት የፈረስ አፍቃሪ ነበሩ፡፡ ይሄን ፍቅራቸውን ለመወጣትም በ20 ሚ.ዶላር የፈረስ መዝናኛ ማዕከል ያስገነቡ ሲሆን ማዕከሉ የመዋኛ ገንዳ፣ የአየር ማቀዝቀዣና የህክምና አገልግሎቶች የተሟሉለት ነበር፡፡ (ይሄ ሁሉ ድሆች በሞሉባት አገር እንደነበር አትዘንጉብኝ!) እኚህ አምባገነን መሪ ከስልጣን የወረዱት በ2006 ዓ.ም ሲሞቱ ነው፡፡ የወርቅ ቅብ ሃውልታቸው ደሞ ከአራት ዓመት በኋላ በ2010 ዓ.ም ከተተከለበት ስፍራ ተወግዷል (ደርግ ሲገረሰስ የተገነደሰው የሌኒን ሃውልት ትዝ አለኝ!) እሳቸውን የተኳቸው ፕሬዚዳንት ደግሞ የፈረስ የቁንጅና ውድድር በ2011 እንዳዘጋጁ ተዘግቧል  (ማለቂያ የሌለው የአምባገነኖች እብደት…አትሉም!)
እኔ ሳስበው ግን አምባገንነት የአገዛዝ ሥርዓት ወይም የግለሰቦች ባህርይ (ስብዕና) አይመስለኝም፡፡ እብደት ወይም ለእብደት አንድ ሃሙስ የቀረው የአዕምሮ መታወክ በሽታ ነው፡፡ ፍርሃት…ጥርጣሬ…ቅዠት…ጀብደኝነት…ጭካኔ…እብሪት…የበሽታው ምልክቶች ናቸው፡፡ የአምባገነንነትን ደዌ እንደ ፖሊዮ ከምድረገጽ ለማጥፋት ብዙ ትጋትና ጥረት ይጠይቃል፡፡ (ከአምባገነንነት የፀዳች ዓለም እኮ ገነት ናት!)

Read 3910 times