Saturday, 15 November 2014 10:37

የመኢአድ የቀድሞ ፕሬዚዳንት “መፈንቅለ ሥልጣን ተፈፅሞብኛል” አሉ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

“መኢአድ አቶ አበባውን በፕሬዚዳንትነት አያውቃቸውም” አዲሱ ፕሬዚዳንት

ሰሞኑን ከስልጣን የተነሱት የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሃሪ ከፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ውጪ “መፈንቅለ ስልጣን ተፈፅሞብኛል” ያሉ ሲሆን አዲሱ የፓርቲው ፕሬዚዳንት አቶ ማሙሸት አማረ በበኩላቸው፤ መኢአድ አቶ አበባውን በፕሬዚዳንትነት አያውቃቸውም የተመረጡበት ጉባኤም ህገ ወጥ ነው ብለዋል፡፡
ፓርቲው ባለፈው ቅዳሜና እሁድ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላለፉት 4 አመታት ከፓርቲው አባልነታቸው ታግደው የቆዩትን አቶ ማሙሸት አማረን በፕሬዚዳንትነት የመረጠ ሲሆን እሳቸውና ሌሎች ታግደው የነበሩ የፓርቲው አባላት በድጋሚ የተመለሱት በመኢአድ አማካሪ ቦርድ ለአንድ ወር በተደረገ ጥረት በተፈጠረ እርቅ ነው ተብሏል፡፡
“በፓርቲው አመራር ውስጥ ሳልካተት በተራ አባልነት እቀጥላለሁ” ሲሉ ለፓርቲው ደብዳቤ የፃፉት አቶ አበባው መሃሪ በበኩላቸው፤ ሐምሌ 14 ቀን 2005 ዓ.ም በተደረገው የመኢአድ ጠቅላላ ጉባኤ በፕሬዚዳንትነት የመረጠው እሣቸውን መሆኑን አመልክተው “የትግሉ መስመር በአንዳንድ ብልጣብልጦችና የሴራና የአድማ አካሄድን በሚችሉ ግለሰቦች መጠለፉን ተገንዝቤያለሁ፤ ሆኖም ከንትርክና ከጭቅጭቅ በመውጣት በተራ አባልነት ለመቀጠል ወስኛለሁ” ብለዋል፡፡
አዲሶቹ የፓርቲው አመራሮች ከትናንት በስቲያ በጽ/ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የአቶ አበባው መሃሪን ካቢኔ የተካው ስራ አስፈፃሚ 20 አመራሮች እንዳሉት ጠቁመዋል፡፡
ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም በተደረገው የጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ፤ አቶ ማሙሸት አማረ ፕሬዚዳንት፣ ዶ/ር ታዲዎስ ቦጋለ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሁም አቶ እንድሪያስ ኤሮ ም/ፕሬዚዳንትና አቶ ተስፋዬ መላኩ ዋና ፀሐፊ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ በሌላ በኩል የአቶ አበባው ካቢኔ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩትና በአዲሱ ፕሬዚዳንት የትምህርትና ስልጠና ጥናትና ምርምር ተጠሪ ሆነው የተመረጡት አቶ ተስፋሁን አለምነህ፤ ከአዲሱ ካቢኔ ራሳቸውን ማግለላቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
አዲሱ አመራር ከህዳር 1 ጀምሮ ሥራውን በይፋ የጀመረ መሆኑን ያስታወቁት አዲሱ ፕሬዚዳንት፤ የሰሞኑን ጠቅላላ ጉባኤ ውጤትም ምርጫ ቦርድ ሁለት ታዛቢዎች ልኮ ሲከታተል ስለነበር ጉባኤውን ይቀበለዋል ብለን እናምናለን ብለዋል፡፡
በሐምሌ 2005 የተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ በምርጫ ቦርድ ተቀባይነት ያጣው የጉባኤው አባላት ተሟልተው ባለመገኘታቸው እንደነበር የጠቀሱት አቶ ማሙሸት፤ ሰሞኑን የተጠራው ጠቅላላ ጉባኤ ግን ቀድሞ የታገዱትንም ሆነ በስራ ላይ የነበሩ አመራሮችን ያካተተ በመሆኑ የተሟላ ነው፤ ምርጫ ቦርድም ይቀበለዋል ብለዋል፡፡
በአዲሱ የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ ውስጥ ከተካተቱት አመራሮች አብዛኛው ከእነ አቶ ማሙሸት ጋር ታግደው የነበሩ እንደሆነ ታውቋል፡፡
በፓርቲው የአማካሪ ቦርድ አማካኝነት የፓርቲው የበላይ ጠባቂ ኢ/ር ሃይሉ ሻውል በተገኙበት እርቅ መፈፀሙን የጠቆሙት የፓርቲው አመራሮች፤ በእርቅ ሂደቱም ማንንም ያላገለለ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በተወሰነው መሠረት ቀድሞ የታገዱትም ሆነ በአመራር ላይ የነበሩት በጋራ በጉባኤው መሰየማቸውን አስታውቀዋል፡፡
“ወደ ጠቅላላ ጉባኤው የገባነው ጉባኤው የሚወስነውን በፀጋ ለመቀበል ተስማምተን ነው” ያሉት አቶ ማሙሸት፤ በጉባኤው ውሣኔ ያኮረፈ ቡድን ስለመኖሩ አናውቅም፤ ጠቅላላ ጉባኤው በመግባባት የተቋጨ ነው ብለዋል፡፡
አቶ ማሙሸት ይህን ይበሉ እንጂ ከአቶ አበባው መሃሪ ጋር በጠቅላላ ጉባኤው ውሣኔ ቅር የተሰኙ የፓርቲው አባላት ሃሙስ ከሰአት በኋላ በኢየሩሣሌም ሆቴል በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ያላቸውን ቅሬታ ለጋዜጠኞች በዝርዝር ገልፀዋል፡፡
ላለፉት 4 ዓመታት ታግደው በእርቅ የተመለሱት እነ አቶ ማሙሸት ወደ አመራርነት ሳይመጡ በአባልነት ለሁለት አመት ቆይተው የባህሪ ለውጥ ማድረጋቸው መገምገም አለበት ተብሎ ቢወሰንም የፓርቲው የበላይ ጠባቂ ኢ/ር ሃይሉ ሻውል በራሳቸው ውሣኔ እኛን ከመድረክ አስወርደው እነሱን ሾመዋል” ያሉት አቶ አበባው፤ ከጠቅላላ ጉባኤው ውሣኔ ውጪ የሆነ መፈንቅለ ስልጣን ተፈጽሟል ብለዋል፡፡
የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንድ ፕሬዚዳንት ለሁለት ዓመት ማገልገል እንዳለበት ይደነግጋል ያሉት አቶ አበባው፤ እኛ ግን አንድ አመት ከ3 ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ይሄ ደንብ ተጥሶ፣ በኢ/ር ኃይሉ ፈላጭ ቆራጭነት ከስልጣን ተነስተናል ብለዋል፡፡
የእሁዱ ጠቅላላ ጉባኤ የተጠራው የ2005ቱን ጠቅላላ ጉባኤ ምልአተ ጉባኤ አሟልቶ በምርጫ ቦርድ እውቅና ለማሰጠት እንጂ አዲስ ፕሬዚዳንት ለማስመረጥ አልነበረም ሲሉ አቶ አበባው ተናግረዋል፡፡
አዲሱ ተመራጭ አቶ ማሙሸት በበኩላቸው፤ “የፓርቲው ህገ ደንብ በየሁለት ዓመቱ ጠቅላላ ጉባኤ ይካሄዳል እንደሚል ጠቁመው የሰሞኑ ጉባኤ አስቸኳይ እንጂ በደንቡ በየሁለት አመቱ ይካሄዳል የተባለው አይደለም፣ የፕሬዚዳንቱ የስልጣን ዘመን ሁለት አመት ነው የሚልም አልተቀመጠም፤ ምርጫ በየሁለት አመቱ ይካሄዳል ነው የሚለው” ብለዋል፡፡ አቶ አበባው በ2005 ተካሂዷል የሚሉት ጠቅላላ ጉባኤ ህገ ወጥ ነው ያሉት አቶ ማሙሸት፤ “መኢአድ አቶ አበባውን በፕሬዚዳንትነት አያውቃቸውም፤ ጠቅላላ ጉባኤው አልመረጣቸውም፤ ስለዚህ መፈንቅለ ስልጣን ተፈፅሞብኛል ማለት አይችሉም” ሲሉ አጣጥለዋል፡፡
 ትክክለኛው ጠቅላላ ጉባኤ ተካሂዶ ፕሬዚዳንት የተመረጠው በዚህኛው ጉባኤ ነው አቶ ማሙሸት፤ “ እነ አቶ ማሙሸት ለሁለት አመታት በተራ አባልነት ይገምገሙ የሚል ሃሳብ በጠቅላላ  ጉባኤው አልቀረበም” ሲሉም አስተባብለዋል፡፡  
የፓርቲው ህጋዊ ማህተም በእነ አቶ አበባው መሃሪ እጅ እንደሚገኝ የጠቆሙት አቶ ማሙሸት፤ ማህተሙ ህገወጥ ስራ እንዳይሠራበትና ለህጋዊ ስራ አስፈፃሚው እንዲመለስ ለፖሊስ አመልክተው ምላሽ እየተጠባበቁ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል አዲሶቹ አመራሮች 6 ወር ብቻ ለቀረው ምርጫ ያላቸውን ዝግጅት አስመልክቶ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ “ከምርጫው በፊት ያሉት ሂደቶች ዲሞክራሲያዊነትና አሳታፊነት ፓርቲው ወደ ምርጫው ይገባል አይገባም የሚለውን ይወስናሉ” ያሉት አቶ ማሙሸት፤ የሰላማዊ ሰልፍ ጉዳይ፣ የህዝባዊ ስብሰባ፣ የታዛቢዎች ገለልተኛነት፣ የመገናኛ ብዙሃን ፍትሃዊ አጠቃቀም የመሳሰሉት በህገመንግስቱ መሠረት በስራ ላይ መዋላቸውን ከገመገምን በኋላ እንወስናለን” ብለዋል፡፡ከአንድነት ፓርቲ ጋር ተጀምሮ የነበረውን ውህደት በተመለከተም፤ ለውህደቱ የተካሄዱ ውይይቶችን ከሰነዶች ላይ ከመረመርን በኋላ አካሄዱን ፈትሸን፣ በቀጣይ ምን ይሆናል በሚለው ላይ መግለጫ እንሰጥበታለን ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ ጽ/ቤት፣ ሰኔ 26 ቀን 2006 ዓ.ም ውህደቱን አስመልክቶ ለመኢአድ በፃፈው ደብዳቤ፤ ከአንድነት ጋር ለሚካሄደው ውህደት ጉድለት አለበት የተባለውን ጠቅላላ ጉባኤ ፓርቲው ማሟላት እንዳለበት አሳስቦ ነበር፡፡

Read 3227 times