Saturday, 13 December 2014 10:22

አንድነት በዘንድሮው ምርጫ “ኢህአዴግ ያበቃለታል አለ”

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(22 votes)

በጠራው አስቸኳይ ጉባኤ፤ የአባላት ቁጥር በህገ ደንቡ እንዲካተት አድርጓል

        አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ /አንድነት/ ትናንትና ባካሄደው አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ፤ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ቁጥርን በህገ ደንቡ ያካተተ ሲሆን ሌሎች ህገ ደንቦችንም አሻሽሏል፡፡ ፓርቲው መጪውን ምርጫ አስመልክቶ ለጠቅላላ ጉባኤ አባላትና በመላ አገሪቱ ለሚገኙ የፓርቲው የአመራር አካላት ቀንና በማታ ሲሰጥ የቆየውን ስልጠና ዛሬ ያጠናቅቃል፡፡ ለጠቅላላ ጉባኤው ከተጠሩት 320 አባላት ውስጥ 250 ያህሉ በጉባኤው ተገኝተዋል፡፡ ካባለፈው ሃምሌ ወር ጀምሮ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው እንዲያስተካክል ያቀረበለት ዘጠኝ ጥያቄዎች እንደነበሩ ያስታወሱት የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃ፤ ከዘጠኙ ጥያቄዎች ስምንቱ መመለሳቸውንና የጠቅላላ ጉባኤ አባላትን ቁጥር አሳውቁ የሚለው ጥያቄ ቀርቶ እንደነበር ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ቁጥር 320 መሆኑን ፓርቲው ለቦርዱ አሳውቆ የነበረ ቢሆንም ቁጥሩን በተሻሻለው ህገ ደንብ ውስጥ አስገቡ የሚል ምላሽ ከቦርዱ እንደመጣላቸው አስታውሰው፣ ይህንኑ ለማድረግ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ መጠራቱን አቶ አስራት ተናግረዋል፡፡ “እግረ መንገዱን ጠቅላላ ጉባኤው ከተጠራ አይቀር አንዳንድ መሻሻል ያለባቸው ህገ ደንቦችም ተሻሽለዋል” ብለዋል፡፡
ፓርቲው ሊያከናውናቸው ካቀዳቸው ስራዎች ውስጥ የቀረው ከምርጫው አስቀድሞ ስለ ምርጫውና በምርጫው ወቅት መደረግ ስላለባቸው ጉዳዮች ለጠቅላላ ጉባኤ አባላትና በመላ አገሪቱ ለሚገኙ የፓርቲው የአመራር አካላት ስልጠና መስጠት እንደነበር የገለፁት ኃላፊው፤ ስልጠናው ከሃሙስ ጀምሮ ከጠቅላላ ጉባኤው ጎን ለጎን ቀንና ማታ ሲካሄድ ቆይቶ ዛሬ ማምሻውን እንደሚጠናቀቅ ተናግረዋል፡፡ ለስልጠናና ለጠቅላላ ጉባኤው የመጡት አባላት ቁጥር ከ500 በላይ መሆኑን የጠቆሙት አቶ አስራት፤ ከ400 ሺህ ብር በላይ ወጪ እንደሚያስፈልግና ገንዘቡ ከውጭ ደጋፊዎችና ከአባላት የሚሰበሰብ እንጂ በእጅ የሌለ ገንዘብ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡  ስልጠናው በዋናነት ምን ላይ እንደሚያተኩር የጠየቅናቸው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው፤ አንድነት በምርጫው እንደሚሳተፍ ቀደም ሲል ማሳወቁን አስታውሰው፤ ምርጫው በሚካሄድበት ወቅት ፓርቲው የራሱን ታዛቢዎች ለማስቀመጥ፣ የአንድነት ደጋፊዎች ለመምረጥ እንዲመዘገቡ፣ በወቅቱ የምርጫ ካርድ እንዲወስዱ፣ በአግባቡ ድምፅ ቆጥሮ ለመረከብ የሚያስችሉትን ሁኔታዎች ለማመቻቸት እንዲችል የሚያደርጉ ስልጠናዎች  ለአመራሮቹ እንደተሰጠና ከስልጠናው እንደተመለሱ አመራሮቹ ህዝቡን የማንቃትና ስልጠና የመስጠት ሥራ እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡
“አንድነት በምርጫ ለመሳተፍ የወሰነው በፖለቲካ ምህዳሩ የተገኘ አዲስ ነገር ኖሮ ሳይሆን ፓርቲያችን በራሱ ጥረት የኢህአዴግ ስርዓት በዘንድሮው ምርጫ እንዲያበቃ ለማድረግ ነው” ያሉት አቶ አስራት፤ በአሁኑ ሰዓት ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ሳይሆን፣ አማራጭ ሚዲያዎች ሳይገኙና በመሰል አጣብቂኝ ውስጥ ታፍኖ የሚካሄድ ምርጫ መሆኑን ግን ፓርቲያቸው እንደሚያውቅ ተናግረዋል፡፡

Read 5391 times