Print this page
Saturday, 13 December 2014 10:29

ባለሀብቶች ለበዓሉ 4 ሚ.ብር ለግሰዋል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

           ዓምና በጅጅጋ በተከበረው የብሄር ብሄረሰቦች ቀን ላይ ቀጣዩን 9ኛ በዓል የቤኒሻንጉል ክልል ርዕሰ መዲና አሶሳ እንድታስተናግድ ስትመረጥ፣ ከታዳጊ ክልልነቷ አንፃር እንዴት ይቻላታል የሚል ስጋት ተፈጥሮ ነበር፡፡ ሆኖም የክልሉ መንግስት ከግል ባለሃብቶች ጋር ተቀናጅቶ ወደ 5 ሺህ የሚጠጉ እንግዶችን ማስተናገድ ችሏል፡፡ በአሉ የሚከበረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በሚገነባበት ክልል እንደመሆኑ የእንግዶች ቁጥር ከተገመተው በላይ ነበር፡፡
በአጠቃላይ 3577 እንግዶች በበአሉ ይሳተፋሉ ተብሎ የተጠበቀ ቢሆንም ከ1 ሺህ በላይ ያልተጠበቁ እንግዶች በበአሉ ታድመዋል ተብሏል፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የክልሉ መንግስት በአሉን በጋራ ያዘጋጁት በመሆኑ በተናጥል የቀረበ የበጀት ሪፖርት ባይገኝም የክልሉ መንግስት ነባር መንገዶችን ለመጠገንና ለማደስ እንዲሁም የማስዋብ ስራ ለመስራት ወደ 11 ሚሊዮን ብር ገደማ ወጪ ማድረጉ ተጠቁሟል፡፡
የአሶሳ ብሄራዊ ስታዲየም በሼክ መሃመድ አላሙዲ ድጋፍ በ6 ወር ጊዜ ውስጥ ለበአሉ እንዲደርስ ተብሎ የተገነባ ሲሆን የግል ባለሃብቶችም በዘመቻ መልክ ለእንግዶች ማረፊያ የሚሆኑ ፔንሲዮኖችንና ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችን ገንብተዋል፡፡ ከአመት በፊት አሶሳን ያውቃት የነበረ አንድ ወዳጄ ፤ ከተማዋ ጥሩ ማስተር ፕላን ቢኖራትም አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በጥራትም በብዛትም አልነበራትም ብሎኛል፡፡ መንገዶቹ ከፊል አቧራማ እንደነበሩም ያስታውሳል፡፡ ለበአሉ ሲባል በተሰራው ስራ ግን ሙሉ ለሙሉ የከተማዋ ገፅታ መቀየሩን ይኸው ወዳጄ ይመሰክራል፡፡ በተለይ የመንገዶች ማስፋፊያና ዋና ዋና አደባባዮችን የማስዋብ ስራ የከተማዋን ገጽታ ፍፁም ቀይሮታል፡፡  
አንዳንድ የከተማዋ ነዋሪዎችም አንቀላፍታ የነበረችው አሶሳ በብሄር ብሄረሰቦች በአል ምክንያት መነቃቃት መጀመሯን መስክረዋል፡፡ የብሄር ብሄረሰቦች በአልን ደግሞ ደጋግሞ ያምጣልን ሲሉም ተደምጠዋል፡፡
የቤኒሻንጉል ክልል በአሉን ለማክበር 10 ኮሚቴዎችን አዋቅሮ ሲሰራ እንደከረመ “አወደ-ቤጉ” የተሰኘው የክልሉ ልሳን ጋዜጣ ይጠቁማል፡፡ ኮሚቴዎቹ የከተማዋን ባለሃብቶች በማስተባበርም የመስተንግዶ ስራውን ያከናወኑ ሲሆን ባለሃብቱ ለበአሉ አጠቃላይ 4 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገንዘብ ማዋጣቱን ጋዜጣው ዘግቧል፡፡
“የምግብ እና የመጠጥ ኮሚቴ” የአቅርቦቱንና የመስተንግዶውን ጉዳይ ለአንድ የሽርክና ማህበር እንደሰጠ የጠቆመው ጋዜጣው፤ ማህበሩም በ6 ቦታዎች የምግብ ማብሰያ ጣቢያዎችን በማቋቋም ሲተጋ ሰንብቷል፡፡ ለበአሉ 100 ኩንታል ጤፍ የተዘጋጀ ሲሆን በየቀኑ እስከ 15 የሚደርሱ በሬዎችን 120 በጐች እንዲሁም እስከ 250 የሚሆኑ ዶሮዎችን ለእርድ ቀርበዋል፡፡የሽርክና ማህበሩ ለ2955 እንግዶች ምግብና መጠጥ ያቀረበ ሲሆን ወጪውን የሸፈነው የክልሉ መንግሥት የፌዴሬሽን ም/ቤት ነው፡፡ የ622 እንግዶችን ወጪ ደግሞ የፌደሬሽን ምክር ቤት እንደሸፈነ ተጠቁሟል፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ የተከበሩ አቶ ካሳ ተክለብርሃን በበአሉ ማጠናቀቂያ ላይ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ም/ቤቱ ከገመተው በላይ እንግዶች መገኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
እንግዶች በተለያዩ ቦታዎች ያደሩ ሲሆን ለየብሄረሰቡ የባህል ትርኢት አቅራቢዎች በአሶሳ ዩኒቨርስቲ ለጋዜጠኞችና ለኪነጥበብ ባለሙያዎች በአሶሳ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት መኝታ ተዘጋጅቶላቸው ነበር፡፡ ሆኖም አብዛኛው ጋዜጠኛ በከተማዋ በሚገኙ የተለያዩ ሆቴሎች እንዲያድሩ ተደርጓል፡፡
በዚህ መልኩ እንግዶቿን ያስተናገደችው አሶሳ፤ 10ኛውን የብሄር ብሄረሰቦች በአል የማዘጋጀት ኃላፊነቱን ለጋምቤላ አስረክባለች፡፡ የጋምቤላ ርእሰ መስተዳድር ባደረጉት ንግግርም፤ “በ10ኛው በአል ላይ የተሻለ መስተንግዶ ጠብቁ” ሲሉ ከወዲሁ ቃል ገብተዋል፡፡
ጥቂት ስለ ህዳሴው ግድብ
የህዳሴው ግድብ ግንባታ 40 በመቶ መድረሱ የተገለፀ ሲሆን ከመሬት  ከአንድ እግር ኳስ ሜዳ በላይ በሆነ ውፍረት 60 ሜትር ከፍታ ላይ ደርሷል፡፡ ግድቡ ሲጠናቀቅ 145 ሜትር ከፍታ የሚኖረው ሲሆን በ10 ተርባይኖች 6ሺህ ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ከ270 ካሬ ኪ.ሜ በላይ ስፋት ያለው ሰው ሰራሽ ሃይቅ እንደሚፈጠርም ታውቋል፡፡ የበአሉ ታዳሚዎች ህዳር 27 ቀን ግድቡን የጎበኙ ሲሆን አዳራቸውን እዚያው ነበር ያደረጉት፡፡ በእለቱ ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ተገኝተው ነበር፡፡ የህዳሴው ግድብ በ24 ሰአታት ውስጥ 16.949 ሜትር ኪዩብ አርማታ በመሙላት በቻይና ተይዞ የቆየውን የግንባታ ሪከርድ እንደሰበረ መገለፁ ይታወሳል፡፡
የአልበሽር ጉብኝት
የአሶሳ ስታዲየም ህዳር 29 ቀን በተከበረው የብሔር ብሄረሰቦች በአል ላይ  ሞቅ ያለ አቀባበል የተደረገላቸው የሱዳኑ ፕሬዚዳንት አልበሽር፤ ከሰአት በኋላ በህዳሴው ግድብ ያልተጠበቀ ጉብኝት  አድርገዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ የጅቡቲው ፕሬዚዳንት እስማኤል ኦማር ጊሌም የተገኙ ሲሆን ጉብኝቱ ትልቅ ትርጉም እንዳለው የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ ካሳ ተ/ብርሃን ተናግረዋል፡፡
 አልበሽር ባደረጉት ንግግርም፤ መንግስታቸው ለግድቡ መገንባት  ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና የሃገራቸው ህዝብም በግድቡ ግንባታ ደስተኛ መሆኑን በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡      

Read 5236 times