Saturday, 31 January 2015 13:06

ቻይና የአፍሪካን መዲናዎች በትራንስፖርት አስተሳስራለሁ አለች

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቱን ርዕሰ መዲናዎች በመንገድ፣ በባቡርና በአየር በረራ ማስተሳሰር ያስችላል የተባለ ትልቅ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ ከቻይና መንግስት ጋር የትራንስፖርት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ከቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚያንግ ሚንግ ጋር የመግባቢያ ስምምነቱን የተፈራረሙት የህብረቱ ሊቀመንበር ንኮሳዛ ድላሚኒ ዙማ፣ ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ የተፈረመውን ስምምነት ህብረቱ እስካሁን ከአጋሮች ጋር ከተፈራረማቸው ስምምነቶች ሁሉ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው ነው ብለውታል፡፡
ዚያንግ ሚንግ በበኩላቸው፤ የመግባቢያ ስምምነቱ የምዕተ አመቱ ትልቅ ሰነድ ነው፣ በአየር በረራ መስክ የተፈረመው ስምምነትም በአፍሪካ ህብረት እና በቻይና መካከል ያለውን ትብብር ወደ አዲስ መስክ ያሰፋ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከአንደኛው የአፍሪካ ክፍል ወደ ሌላኛው ለመጓዝ የተሻለ አማራጭ ተደርጎ የሚወሰደው የአውሮፓን የበረራ መስመር የተከተለ አካሄድ ነው ያሉት ሚንግ፣ አህጉሪቱ ሰፊ እንደመሆኗ በአውሮፓ የበረራ መስመሮች ላይ ጥገኛ ያልሆነና አገራቱን በቀላሉ የሚያስተሳስር የራሷ የትራንስፖርት አውታር ሊኖራት ይገባል ሲሉ መናገራቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

Read 1433 times