Saturday, 31 January 2015 13:14

የቁልቁለት መንገድ

Written by  መሐመድ ነስሩ
Rate this item
(14 votes)

      ኤደን ወልዳ ተኝታለች፡፡ አራስ ቤት ሆና ሰላም ልታገኝ ግን አልቻለችም፡፡ በህይወትዋ ውስጥ የተከሰቱ ብዙ ታሪኮች አሉ፡፡ የምትወዳቸውም የማትወዳቸውም፡፡ ታዲያ ታሪክዋ ታሪክ ብቻ ሆኖ አልተገኘም፡፡ ወደ ኋላ ይስቧታል፡፡ ወደ ድሮ ይጎትቷታል፡፡
ከናትናኤል ጋር ተጋብተዋል፡፡ ተጋብተዋል ግን አልተግባቡም፡፡ ትወደዋለች ግን ትፈራዋለች። ታፈቅረዋለች ግን ታፍረዋለች። ለዚህ የዳረጋት ታሪክዋ ነው፡፡ ከናትናኤል ጋር ህይወትዋ ውስጥ አራት ሰው አለ፡፡ ከመጀመሪያው ስንጀምር፡-
የመጀመሪያው ሰው
ሱራፌል ይባላል፡፡ የታክሲ ሹፌር ነው፡፡ አንድ ቀን ከካሳንቺስ ወደ ፒያሳ ስትጓዝ የቆመላት ታክሲ ውስጥ ገባች፡፡ ቆንጆ ናት፡፡ ቁንጅናዋ የትኛውንም ወንድ እንደ ማግኔት ከሩቅ ይስባል። ሱራፌል ቆንጆ ሴት አይቶ የማያልፍ ዓይነት ሰው ነው፡፡ ቆንጆና እሸት አይታለፍም ከሚሉት ውስጥ ነው፡፡
“መነፅርሽ በጣም ያምራል!” አላት
“አመሰግናለሁ!”
“ምነው እኔስ አላምርም ወይ ነው ያልሽኝ?”
“ኧረ ታምሪያለሽ … መነፅሩ ራሱ ያማረው እኮ ያንቺ ፊት ውበት ተጋብቶበት ነው … እመብርሃንን!”
 ፈገግ ብላ “አመሰግናለሁ!” አለች በድጋሚ
“ምስጋና ኪስ አይገባም ሲባል አልሰማሽም?”
ዝም አለችው፡፡
“እግዜርን ግን በጣም ልታመሰግኚው ይገባሻል።”
“ለምን?”
“ይህቺን የመሰለች .. መልአክ የምትመስል ሴት አድርጎ ስለፈጠረሽ፡፡”
እንደ መሽኮርመም አለች፡፡ ወሬ ተጀመረ፡፡ ተግባቡ፡፡ ከመውረድዋ በፊት
“ስልክሽን አንዴ ታውሺኝ?!” አላት፤ በግራ እጅዋ ወደያዘችው ስልክዋ እጁን እየዘረጋ፡፡
“ለምን?”
“ስልኬ ባላንስ የለውም፤ የሆነ ቦታ ሚስኮል ላደርግ ፈልጌ ነው”
ሰጠችው፡፡ ተቀበላት፡፡ በስልኳ ወደ ስልኩ ደወለ፡፡ ስልክ ቁጥርዋን ስልኩ ላይ መዘገበ፡፡ አመስግኖ ስልክዋን መለሰላት፡፡
“ለምኑ ነው የምታመሰግነኝ?” አለችው
“ቀኔ ብሩህ እንዲሆን ስለረዳሽኝ አመሰግናለሁ!”
ደረሰች፡፡ ወረደች፡፡ በስልክ ግንኙነታቸው     ቀጠለ፡፡ በየቀ ይደውላል፡፡ በየቀኔ ታወራዋለች። አንዴ ተገናኙ፡፡ ሁለቴ ተገናኙ፡፡ ሶስቴ ተገናኙ። አራቴ ተገናኙ፡፡ በመጨረሻ ፍቅረኛሞች ሆኑ ተገኙ። ያልሆኑትና ያላደረጉት ነገር የለም፡፡
ተዋደዱ፡፡ ተሻሹ፡፡ ተሳሳሙ፡፡ ምን ቀረ? ምንም!
ሁለተኛው ሰው
ተመስገን ይባላል፡፡ መካኒክ ነው፡፡ የራሱ ጋራጅ ቤት አለው፡፡ በድርጅቱ በር ስታልፍ አያት፡፡
“አንድ ጊዜ እንድናወራ ትፈቅጂልኛለሽ?” አላት መንገድ ላይ አስቁሟት፡፡
“ስለ ምን?”
“ዝም ብለን ስለ አንዳንድ ነገር ብናወራ ደስ ይለኝ ነበር”
“አይመቸኝም!” ብላ ጥላው ልትሄድ ስትል እጅዋን አፈፍ አድርጎ እያስቆማት፤
“ይቅርታ…ከድፍረት አትቁጠሪብኝና የግድ ዛሬ መሆን የለበትም፤ የሆነ የሚመችሽ ቀን ሻይ ቡና እያልን ብናወራ ደስ ይለኝ ነበር፡፡” አላት፡፡
“ወንድሜ … እኔና አንተን የሚያገናኘን ምንም የጋራ ነገር ያለንም፡፡ ስለዚህ …”
ተለያት፡፡
በሚቀጥለው ቀን አስቁሞ ትንሽ አወራት፡፡ በሚቀጥለው ቀንም ትንሽ አወራት፡፡ በኋላ ላይ ካፌ ገብቶ ለመጨዋወት ፈቀደች፡፡ ገቡ፡፡ አወሩ።
“ፍቅር ያዘኝ” አለ፡፡
ግንኙነት ጀመሩ፡፡ ተሳሳሙ፡፡ ተቃቀፉ፡፡ አንሶላ ተጋፈፉ፡፡
ሶስተኛው ሰው
ስምኦን ይባላል፡፡ መሀንዲስ ነው፡፡ መሀንዲስ ብቻ ሳይሆን የሰፈርዋ ልጅም ነው፡፡ የወንድ ቆንጆ ነው፡፡ ከጓደኞችዋ ጋር “ቆንጆው ልጅ” እየተባባሉ ያወራሉ፡፡
“ቆንጆው ልጅ መጣ …”
“ቆንጆው ልጅ አለፈ …”
“ቆንጆው ልጅ ሰላም አለኝ …”
“ቆንጆው ልጅ …”
“ቆንጆው ልጅ …”
ተግባቡ፡፡ አብረው ጊዜ ማሳለፍ ጀመሩ። አብሮ ፊልም ማየት መጣ፡፡ ተላመዱ፡፡ ተዋደዱ። ፍቅር ደራ፡፡ ክርና መርፌ ሆኑ፡፡
ሦስቱን ወንዶች የተዋወቀችውና ግንኙነት የጀመረችው በአንድ ዓመት ውስጥ ነው። በወራት ልዩነት! ሱራፌል የሚያውቀው ከእሱ ጋር ብቻ እንደሆነችና እንደምትወደው ነው። ተመስገን የሚያውቀው ከ‘ሱ ሌላ ወንድ ቀና ብላ የማታይ እና እንደሚወዳት ሁሉ አብዝታ የምትወደው መሆኗን ነው፡፡ ስምኦን የሚያውቀው እሱ ብቸኛው ፍቅረኛዋ እንደሆነና ሌላ ወንድ እንደማታውቅ ነው፡፡
አንዱ ሰኞ ከተቀጠረ፤ ሌላኛው ማክሰኞ ይቀጠራል፡፡ አንዱ እሮብ ካገኛት፤ ሌላው ሀሙስ ያገኛታል፡፡ ከአንዱ ጋር መልካም ቅዳሜ፤ ከሌላው ጋር ቆንጆ እሁድ ታሳልፋለች። አንዳንዴም አንዱን ጠዋት ሌላውን ከሰዓት ታገኛለች፡፡ አንዱን ረፋድ ላይ፤ ሌላውን አመሻሽ ላይ! አንዱን ቀትር ላይ፤ ሌላውን ማታ! (ማታ ላይ)… ስትጀምረው እንደ ቀልድ ነው፡፡ ሲቆይ ግን ህይወትዋ ሆነ፡፡
አንድ ለሶስት
አንዲት ሴት በሶስት ወንዶች ተይዛለች፡፡
ጨዋታው አንድ ለሶስት ሆኗል፡፡
ከአንዱ ጋር ረጅም ሰዓት ስልክዋ ስለሚያዝ ሌሎቹ መንጨርጨራቸው አልቀረም። ሚስጥሩን አውቀው ሳይሆን እንዲሁ ጠርጥረው። አለ አይደል?! … እንዲሁ!
“ወንድ ልጅ ሞኝ ነው፡፡” ብሎ የለ ዘፋኙ?! ሶስቱም እውነቱን አላወቁም፡፡ ሶስቱም ፍቅር ውስጥ ናቸው፡፡ ሶስቱም ይደውላሉ፡፡ ሶስቱም ያገኝዋታል። ከሶስቱም ጋር አንሶላ ትጋፈፋለች፡፡ “ወንድ ልጅ ሞኝ ነው …” … ፍቅር አልያዛትም፡፡ ሶስቱንም ግን ትወደዋለች፤ ወይም የወደደቻቸው ይመስላታል። ብቻዋን ስትሆን ተሰልፈው ተራ በተራ በፊትዋ  ያልፋሉ፡፡
ሱራፌል ጨዋታውና ቀልዱ ይማርካል። ከሌሎች በተለየ ከእሱ ጋር እንደ ስኳር ድንች የሚጣፍጥ ትዝታ አላት፡፡ መቼም የማትረሳቸው! ከእሱ ጋር ነው ለመጀመሪያ ጊዜ ትንፋሽ  ለትንፋሽ የተማማገችው፤ ሩካቤ ስጋ የፈፀመችው፡፡ እሱ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ አካሉን ከአካልዋ ያዋሃደውና ያዋደደው፡፡ ድንግልናዋን የገረሰሰ ወንድ ነው። የወንድ ጀግና! ማንም ያልሄደበትን መንገድ የሄደ። ስለዚህ አሻራውን ውስጥዋ ትቷል፡፡ ሌሎች በተሄደው መንገድ ላይ ነው የሄዱት፡፡ አሻራቸው አካልዋ ላይ አልታተመም፤ ቢታተምም ግን እንደ‘ሱ በደማቁና በትልቁ ሳይሆን በስሱና በትንሹ ነው።
…ተመስገን ቁምነገረኛነቱ ይደንቃታል። በጣም ሲበዛ ቁምነገረኛ ነው፡፡ ለቁም ነገር እንደሚፈልጋት ይነግራታል፡፡ የወሬው ጭብጥ ትዳር ነው፡፡
“አገባሻለሁ!” ይላታል
“አገባሽና ልጅ ትወልጂልኛለሽ … ከዚያ በደስታ ልጃችንን እያሳደግን በደስታ አብረን እንኖራለን፡፡”
“እሺ!” ትለዋለች፡፡
“ግን ስንት ልጅ ነው የምንወልደው?”
“ስምንት፤ … ዘጠኝ፤ … አስር፤ … አስራሁለት ወይም አስራ አራት … ኧረ ከዛም በላይ!”
ልጅ ይወዳል፡፡ እና ብዙ ቢወልድ ደስ ይለዋል፡፡
እሷ ግን ትለዋለች፤
“ኧረ ባክህ … እኔ ዝም ብዬ ልጅ ስቀፈቅፍ ልኖርልህ ነው?”
“እሺ ታዲያ ስንት እንውለድ?” ይላታል፤ ፍም የመሰለውን ጉንጭዋን በእጁ እየቆነጠጠ፡፡
“ሁለት!” ትለዋለች
“እንዴ … ሁለትማ ያንሳል … አይሆንም … አይሆንም …”
ልጅ አሁኑኑ የሚመጣ ይመስል በሚወልዱት ልጅ መጠን ላይ ይከራከራሉ፡፡ እየተከራከሩና እየተጨቃጨቁ ረጅም ጊዜ ይቆያሉ፡፡ በተገናኙ ቁጥር ባይሆንም አልፎ አልፎ ንትርኩ አይቀርም፡፡
ስምኦን አለባበሱ ይመቻታል፡፡ ዘናጭ ነው። ዘመናዊ ልብሶች ይለብሳል፡፡ ዘመናዊ ጫማዎች ይጫማል፡፡
አንዳንዴ ዲዛይነር ሁሉ ይመስላታል፡፡ እንደሚገነባው ህንፃ ዲዛይን፤ ለ‘ራሱም ዲዛይን ያወጣል፡፡ ወይም ይመስላል፡፡ ቤት መስራት፤ ህንፃ መገንባት ብቻ ሳይሆን ‘ራሱን መስራት፤ ማንነቱን መገንባትም ይችልበታል፡፡ እና እሱን ማየት ደስ ይላታል፡፡ አታፍርበትም፡፡ ከሰው ጋር ስታስተዋውቀው ኩራት ይሰማታል፡፡ የትም ይዛው ትገኛለች፡፡ ከሦስቱ ፍቅረኞችዋ ጓደኞችዋ የሚያወቁት እሱን ብቻ ነው፡፡ ሌሎቹ በሚስጥር የተያዙ ናቸው፡፡ ሌላው ከስምኦን የምትወደው አሳሳሙን ነው፡፡ ሲስማት ልብዋ ጥፍት ይላል፡፡
እየሳማትና እየሳመችው እጁ ላይ እንደ ጨው ትሟሟለች፡፡ ከየት እንደሚያመጣው አታውቅም። ግን ይችልበታል፡፡ አሳሳሙን ጥበባዊ ያደርገዋል። ዛሬ የሳማትን አሳሳም፤ ነገ ላይደግም ይችላል። ብቻ ግን ባገኛትና በሳማት ቁጥር ሌላ ዓለም ውስጥ ያስገባታል፡፡ አየር ላይ ትንሳፈፋለች፡፡ መሬት ትርቃለች፡፡ ሰማይ ይቀርባታል፡፡ ጨረቃዋን መንካትና መጨበጥ፣ ፀሐይዋን መዳበስና መዳሰስ ይቃጣታል፡፡
*   *   *
በድርጊትዋ ደስተኛ አይደለችም፡፡ እንደዚህ መሆን፤ እንደዚህ መኖር አትፈልግም። ሳታስበውና ሳትዘጋጅ የገባችበት ህይወት ነው። ራስዋን ትንቃለች፡፡ በ‘ራስዋ እፍረት ይሰማትና ስቅቅ ትላለች፡፡  እስከመቼ ነው እንደዚህ የምቀጥለው? ብላ ታስባለች፡፡ አታላይ፣ አምታች፣ ውሸታም መሆንዋ አንገት ያስደፋታል።
አንድ ለሶስት!
መወሰን ግን አቃታት፡፡ ከሶስቱ ሁለቱን ምን አድርጋ፤ እንዴት ሆና መገላገል እንዳለበት ግራ ገባት፡፡ ሶስቱን ማወዳደሩና ከሶስቱ አንዱን መምረጡ ራሱ ‘ራሱን የቻለ የቤት ስራ ነው። ማን ይቅር? … ማን ይሸኝ? … ድንግልናዋን የገረሰሰው፤ ሁሌ የሚያስቃትና የሚያዝናናት ሱራፌል፤ ወይስ እንደ ሚስቱ የሚንከባከባት፤ በስጦታ የሚያንበሸብሻትና ሚስት ሊያደርጋት የሚመኘውን ተመስገን  ወይስ በአለባበሱ የሚማርካትና በአሳሳሙ ልብዋን የሚያጠፋው ስምኦን ወይስ … ማን?!
መወሰን እንዳቃታት ወራት ነጎዱ፡፡ ዓመቱ መጣ። መጨረሻ ላይ ያላሰበችው ነገር ተከሰተ። ወርሃዊ ደሞዝዋ ሳይመጣ ቀረ፡፡ የወር አበባዋ የውሃ ሽታ ሆነ፡፡ ኤደን አረገዘች፡፡ ከማን እንዳረገዘች ልታውቅ አልቻለም፡፡ በዚያን ሰሞን ከሶስቱም ጋር አንሶላ ትጋፋ ነበር፡፡ ልጁ የማን ነው? የሱራፌል? … የተመስገን? … የስምኦን? … ወይስ የሶስቱም ወይስ የሌላ የአራተኛ ሰው ወይስ የማን?!
ልታስወርድ አልፈለገችም፡፡ ማስወረድ ሀጢያት ነው ብላ ልትወልደው ወሰነች። ጓደኞችዋ ፅንሱ ቀን ሳይገፋና ሳያድግ ቶሎ እንዲወጣ እናድርገው ቢልዋት፤ የሰው ነፍስ አላጠፋም ብላ በውሳኔዋ ፀናች፡፡ … ሱራፌል ጋ ሄደች፡፡
“ፀንሻለሁ!” አለችው፡፡
“ስትቀልጂ መሆን አለበት” አለ፤ ኮስተር ብሎ፡፡
“የምን ቀልድ ነው የምታወራው፤ ካንተ ልጅ አርግዤያለሁ እኮ ነው የምልህ …” አለችው፡፡
“እኔ የማውቀው ነገር የለም! … የልጁን አባት ሄደሽ እዚያ የምትፈልጊበት ፈልጊ” ብሎ ሸኛት፡፡
ተመስገን ጋ ሄደች፡፡
“አርግዣለሁ! ልጁ የአንተ ነው” አለችው፡፡
“ጥሩ ነው … አንድ ላይ እንጠቃለላለን” አላት፡፡
“ቤተሰቦቼ ጋ ሽማግሌ ላክ” አለችው፡፡
“የምን ሽማግሌ መላክ ነው … ነይና ቤቴ ግቢ፤ ሽማግሌውን ባይሆን በኋላ ለእርቅ እንልካለን እንጂ አሁን አያስፈልግም…”
አልተዋጠላትም፡፡ እንዲደገስ ትፈልጋለች። የሰርግዋን ዕለት መኖርና ማየት ትፈልጋለች፡፡ በክብር ሽማግሌ ተልኮ፤ የቤተቦችዋን ይሁንታ አግኝቶ፤ ቬሎ ለብሳ፤ ተደግሶ፤ ተሰርጎ “የኛ ሙሽራ …” እንድትባል ፈለገች፡፡ ተመስገን ይሄን አላደርግም አለ፡፡
ስምኦን ጋ ሄደች፡፡
“ልጅህን በሆዴ ይዣለሁ!” አለችው፡፡
“የኔ ስለመሆኑ ማረጋገጫሽ ምንድን ነው?” ሲል ጠየቃት፡፡
“እንዴ … አታምነኝም?” አለችው ዓይንዋን ቅልስልስ አድርጋ፡፡
“ማመን አለማመን አይደለም፡፡ ሳልደብቅ የምነገርሽ አንድ ነገር አለ፡፡ እኔ በዚህ ዕድሜዬ ልጅ እንዲኖረኝ አልፈልግም፡፡ ገና የራሴን ልጅነትም ያልጨረስኩ ሰው ነኝ፡፡ እና የልጁን አባት ሄደሽ ሌላ ቦታ ብትፈልጊ መልካም ነው፡፡” ብሎ ተሰናበታት፡፡
ኤደን ግራ ገባት፡፡ ኤደን ተጨነቀች፡፡ ኤደን የምትገባበት ጠፋት፡፡ ወደ ሰማይ ብትመነጠቅ በወደደች፡፡ መሬት አፍዋን ከፍታ ብትውጣት በተደሰተች፡፡ ሁሉም አልሆነም፡፡ “ሁሉም ነበረን፤ ግን ሁሉንም አጣን” ዓይነት ሆነ፡፡ ማስወረዱን “ፈፅሞ የማላደርገው ነገር ነው!” ብላ ደመደመች። ዘጠኝ ወር ጠብቃ በእናት በአባትዋ ቤት ልጅዋን ወለደች፡፡ ወንድ ልጅ ከነቃጭሉ ዱብ!…
*   *   *
ወራት ነጎዱ፡፡ ዓመታት አለፉ፡፡ ልጅዋ ድክድክ ከማለትም አልፎ በእግሩ መሄድ ጀመረ፡፡  ከናትናኤል ጋ ተዋወቁ፡፡ ወደዳት! ሊጋቡም ወሰኑ፡፡ ሽማግሌ ተላከ፡፡ ቤተሰብ በክብር ሰጠው፡፡ የሰርጉ ቀን ሲቃረብ ሽር ጉድ ተጧጧፈ፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተጠሩ። ተደገሰ፡፡ የሰርጉ ዕለት ሙሽራውና ሚዜዎቹ መጥተው ይዘዋት ወጡ፡፡ ጉዞ ወደሱ ቤት ሆነ፡፡
ናትናኤል ስለ ኤደን የኋላ ታሪክ ብዙ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ ስለምንም አላነሳችበትም። በትዋን ዓይቶ ወደዳት፡፡ እና ቸኩሎ አገባት፡፡ አብረው እየኖሩ ሳሉ ከዕለታት ባንዱ ጉዱን ሰማ፡፡ ኤደን ልጅ አላት! ተናደደ፡፡
“እንዴት ሳትነግሪኝ” አለ፡፡ ተርበተበተች፡፡ ከውሃ እንደ ወጣ እንቁራሪት ሆነች፡፡
“ማነው የነገረህ?” አለችው፡፡
“ማን እንደነገረኝ ማወቅ ምን ያደርግልሻል?” አላት፡፡
“ተደብቆ የሚቀር መስሎሽ ነበር?” ብሎ ጮኸባት፡፡
ከዚያን ቀን ጀምሮ የናትናኤል ባህሪ ተለወጠ። ትቀፈው ጀመር፡፡ ባያያት ደስ ይለዋል። ባይሰማት ደስ ይለዋል፡፡ አንድ ማዕድ ላይ አብረው ባይቀርቡ ደስ ይለዋል። አንድ አልጋ ላይ አብረው ባይተኙ ደስ ይለዋል። ይህ ስሜት በሱ ውስጥ እየገነነ ስር እየሰደደ በመሄድ ላይ ባለበት ወቅት ኤደን ማርገዝዋን አወቀች፡፡ ከወራት በኋላም ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ብትወልድም የናትናኤል ባህሪ አልተስተካከለም። እንደ እንቁ ያያትና እንደ እንቁላል ይንከባከባት እንዳልነበረ ለዓይኑም ጠላት፡፡ ከስራ እንደወጣ ወደ ቤት አይገባም፡፡ ሌላ ቦታ አምሽቶ ለመኝታ ብቻ ነው የሚገባው፡፡ ከቤት መብላትም አቆመ። ሰራተኛዋ እራት ስታቀርብለት “በልቻለሁ!” ነው መልሱ፡፡ በአጋጣሚ በምሳ ሰዓት መጥቶ እንደሆነ ምሳ ስታቀርብለትም “በልቻለሁ!” ይላታል፡፡ ቁርስ  ስታቀርብለትም “አሁን አላሰኘኝም” ብሎ ይወጣል። ቤቱና ናትናኤል ሆድና ጀርባ ሆኑ፡፡
ኤደንም ምን ማድረግ እንዳለባት ግራ እንደገባት በተኛችበት ስትተክዝ ውላ፤ ስትቆዝም ታድራለች፤ እራስዋ ኤደን!

Read 7331 times