Saturday, 07 February 2015 13:54

ግብጽ 230 አብዮተኞችን በእድሜ ልክ እስራት ቀጣች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በ189 ዜጎች ላይም የሞት ቅጣት ጥላለች

   የቀድሞውን የግብጽ ፕሬዚዳንት ሆስኒ ሙባረክ በአመጽ ከስልጣን ለማውረድ ከአራት አመታት በፊት በተቀሰቀሰው አመጽ ተሳትፈዋል የተባሉ 230 የአገሪቱ አብዮተኞች ባለፈው ረዕቡ በካይሮ የእድሜ ልክ እስራት እንደተፈረደባቸው  ቢቢሲ ዘገበ፡፡
እ.ኤ.አ በ2011 ታህሳስ ወር ላይ በካይሮው ታህሪር አደባባይ በተካሄደው አመጽ ከአገሪቱ የጸጥታ ሃይሎች ጋር ተጋጭተዋል፣ የተለያዩ የመንግስት ህንጻዎችንና ተቋማትን በእሳት አቃጥለዋል የተባሉት እነዚሁ ተከሳሾች፣ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው የቅጣት ውሳኔው እንደተላለፈባቸው ዘገባው ጠቁሟል፡፡ ተከሳሾቹ ከእስራቱ በተጨማሪ በድምሩ 2ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር በቅጣት መልክ እንዲከፍሉ በፍርድ ቤቱ ተውስኖባቸዋል፡፡
ቅጣቱ ከተላለፈባቸው ግለሰቦች መካከል በችሎቱ ተገኝቶ የፍርድ ውሳኔውን ያደመጠው ብቸኛ ተከሳሽ፣ አመጹን በማቀጣጠልና በመምራት ጉልህ ሚና እንደተጫወተ የሚነገርለት የ26 ዓመቱ አህመድ ዱማ፤ ዳኛው ክሱን በሚያነቡበት ወቅት በማጨብጨብና ጮክ ብሎ በመናገር፣ ተቃውሞውን ለማሰማት ሞክሯል ተብሏል፡፡
የተከሳሾቹ ጠበቆች በበኩላቸው፤ ፍርድ ቤቱ ያስተላለፈውን ውሳኔ የተቃወሙ ሲሆን ዳኛው በተከሳሾቹና በጠበቆቻቸው ላይ ተጽዕኖ ሲፈጥሩ ነበር፣ የፍርድ ሂደቱ በአግባቡ አልተከናወነም፣ ውሳኔውም በአገሪቱ ታሪክ አስደንጋጭና የማይጠበቅ ነው ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፍርድ ቤቱን ውሳኔ የተቃወመ ሲሆን፣ የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይም በአገሪቱ የሚታየው የጅምላ እስራትና ቅጣት ከዲሞክራሲያዊ መርሆዎች ጋር የሚጋጭ ነው ብለዋል፡፡ የአውሮፓ ህብረት በበኩ፤ ግብጽ አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ግዴታዎችን ስትጥስ ቆይታለች፤ የግብጽ ባለስልጣናት ይህንን ግዴታ ማክበርና ፍትሃዊ የፍርድ ውሳኔ እንዲሰጥ ማድረግ ይገባቸዋል ብሏል፡፡
ውሳኔውን ያስተላለፉት ዳኛ ባለፈው ሰኞም የእስላማዊ ቡድን አባላት ናቸው ተብለው በተጠረጠሩ 183 ግለሰቦች ላይ ባለፈው ሰኞ የሞት ፍርድ መበየናቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አለማቀፍ የሰብዓዊ መብት  ተሟጋች ተቋማት ፍርዱን መቃወማቸውን እንደገለጹ አመልክቷል፡፡

Read 1560 times