Saturday, 07 February 2015 13:58

ሳዳም ሁሴን የተሰቀሉበትን ገመድ ለመግዛት ፉክክሩ ተጧጡፏል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

አንድ ተጫራች 7 ሚሊዮን ዶላር አቅርቧል

የኢራን፣ የእስራኤልና የኩዌት ዜግነት ያላቸው ባለጸጎች፣ ቤተሰቦችና ተቋማት የቀድሞው የኢራቅ ፕሬዚዳንት ሳዳም ሁሴን በስቅላት የተገደሉበትን ገመድ በከፍተኛ ገንዘብ በመግዛት የራሳቸው ለማድረግ የጦፈ ፉክክር ውስጥ ገብተዋል ሲል ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ተቀማጭነቱ በለንደን የሆነውን አል አራቢ አል ጃዲድ ድረገጽ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ግለሰቦቹ በቀድሞው የኢራቅ ብሄራዊ ደህንነት አማካሪ ሞዋፋቅ አል ሩባይ እጅ ውስጥ የሚገኘውን ይህን ገመድ የራሳቸው ለማድረግ እየተፎካከሩ ነው፡፡
ግለሰቡ በመኖሪያ ቤታቸው ከነሃስ በተሰራ የሳዳም ሃውልት አንገት ላይ ገመዱን አጥልቀው የሚያሳየውን ፎቶግራፍ ከሁለት አመታት በፊት ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ ገመዱን በእጃቸው ለማስገባት ፍላጎት የሚያሳዩ ግለሰቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉን አንድ የወቅቱ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን ተናግረዋል፡፡
ገመዱን ለማግኘት በሚደረገው ፉክክር ከተሳተፉት መካከል፣ ሁለት የኩዌት ባለጸጎች፣ አንድ የኢራን የሃይማኖት ተቋም እና አንድ የእስራኤላውያን ሃብታሞች ቤተሰብ እንደሚገኝበት የጠቆመው ዘገባው፣ አንድ ተጫራች 7 ሚሊዮን ዶላር ማቅረቡን አክሎ ገልጧል፡፡
የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ገመዱን ለማግኘት የተጀመረውን ጨረታ የተቃወሙ ሲሆን፣ ጨረታው የሚቀጥል ከሆነ ግን የሚገኘው ገንዘብ የአገሪቱን ህዝቦች ተጠቃሚ ለሚያደርግ ተግባር መዋል ይገባዋል ብለዋል፡፡

Read 8564 times