Monday, 02 March 2015 08:59

የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የአዲስ አድማስን ዘገባ ተቃወመ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

‹‹የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች የፓትርያርኩን እገዳ ተቃወሙ›› በሚል ርእስ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ፣ በወጣው የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ የቀረበው ዘገባ የስም ማጥፋት ዘመቻ መኾኑን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ገለጸ፡፡
የአዲስ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጋራ በመተባበር የየአድባራቱን የሰንበት ት/ቤቶች የሥራ አመራር የካቲት 7 ቀን 2007 ዓ.ም ሰብስቦ የማደራጃ መምሪያው ሊቀ ጳጳስና የመምሪያው ምክትል ሓላፊ በተገኙበት የሥራ አመራር እንደሰጣቸው መምሪያው በደብዳቤው አስታውሷል፡፡ ይኹን እንጂ በጋዜጣው ላይ በቀረበው ዘገባ÷ ዓላማው በውል ባልታወቀ ኹኔታ፣ በወቅቱ ያልተባለና ኾን ተብሎ የተቀነባበረ የስም ማጥፋት ዘመቻ በአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አመራር ላይ እንደተፈጸመ በደብዳቤው አስታውቋል፡፡
ማደራጃ መምሪያው አያይዞም ‹‹የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን የበላይ አመራርና የበታች አካላት ለማለያየት፣ ከዚህም ጋራ መንግሥታችን ለምርጫው በሰላም ዙሪያ በሚሠራበት ወቅት ሕዝብን ለመበጥበጥ እንዲሁም ወጣቱ የሰላም ተልእኮውን በአግባቡ እንዳይወጣ ለማድረግ›› ኾን ተብሎ እንደተቀነባበረ ገልፆ ‹‹የሃይማኖቱን ተከታዮች በእጅጉ አሳዝኖናል›› ብሏል፡፡
የዝግጅት ክፍላችን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤትና የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት በዕለቱ ስላደረጉት የግማሽ ቀን ውይይት የስብሰባውን ተሳታፊዎች በምንጭነት በመጥቀስ መዘገቡ ይታወሳል፡፡

Read 2589 times