Print this page
Monday, 09 March 2015 11:51

“ብርቱካናማው ጥለት”

Written by  (ፊያሜታ
Rate this item
(6 votes)

ከአስር አመታት በፊት...
ከአንድ ጠኔያም አርብ... ከአንድ ችጋራም ሌሊት... ከብዙ ማፏሸክና መራብ በኋላ...
እንዳይነጋ የለም ነጋ!...
ጦማችንን ያደርን ሶስት ጓደኛሞች፣ ከእነ ርሃባችን ከእንቅልፋችን ነቃን፡፡ የተለየ ነገር የለም፡፡ ኮሜዲኖው ላይ ካለው የሰነበተ ደረቅ ዳቦ በቀር፣ በጠባቧ የጓደኛችን ዳኜ ቤት ውስጥ እህል የሚባል ነገር የለም፡፡
አንድ ሁለት ስንል አመሸን፡፡ ሰዓቱ ገፋ፣ ኪሳችን ሳሳ፡፡ ሂሳባችንን ከፍለን ወጣን፡፡ ምሽቱ ገፍቷል፡፡ የቄራ ታክሲዎች ወደማደሪያቸው ከትተዋል፡፡ ኮንትራት ታክሲ ለመያዝ ደግሞ፣ ገንዘብ የለንም፡፡ ስለዚህ እዚያው ቄራ አካባቢ ያለችው የኪራይ ቤቱ ውስጥ እንድናድር ከጓደኛችን ከዳኜ የቀረበልልን ግብዣ የማንቀበልበት ምክንያት የለንም፡፡
የአከራዮቹን አመለ ክፉነት እየተረከልን ወደ ቤቱ አዘገምን፡፡ ድምጻችንን አጥፍተን ገብተን፣ በሰላም እንድንተኛ እያሳሰበን ነበር፡፡ ማሳሰቢያውን አክብረን፣ የተረፈንን ሽንት ከመንገድ ዳር አራግፈን፣ ኮቴያችንን አጥፍተን ወደ ግቢው ገባን፡፡ የጠባቧን ቤቱን በር በጥንቃቄ ከፍቶ አስገባን፡፡
“መብራት ከበራ አከራዮቼ ነቄ ስለሚሉ ነው!...” በሚል ማብራሪያ፣ በሞባይሉ ብርሃን ወደ ፍራሹ ጠቆመን፡፡
“እራት እና መብራት አይንሳህ!” ትለኝ ነበር አያቴ። ምን እያለችኝ እንደሆነ የተገለጸልኝ አሁን ነው፡፡ ዛሬ እራትም መብራትም ነስቶኛል፡፡ ቢሆንም አላማረርኩም። እራት እና መብራት እንጂ፣ ትራስ አልነሳኝም፡፡ ጨለማን ተከናንቤ አስሬ እያፏሸክሁ ፍራሽ ላይ ኩርምት ማለቴን ያየው ዳኜ፣ እንተራሰው ዘንድ የሆነ የስፖንጅ የማይመስል ጠንከር ያለ ነገር አቀበለኝ፡፡
እንዳይነጋ የለም ነጋ!...
ዳኜ ቀድሞን ከእንቅልፉ ነቅቶ ሲቀሰቅሰን፣ የሆነ ቁርስ ቢጤ አዘጋጅቶ እንደሚጠብቀን እርግጠኞች ነበርን፡፡
በሚጨናበሱ አይኖቼ ዙሪያውን አማተርኩ፡፡ የተመሰቃቀለች ጠባብ ክፍል፡፡ የእንቁላል ጥብስ ሽታ የማያውዳት ደረቅ ቤት፡፡ ምላስ የመሰለች ፍራሽ... ዳማ የመሰለ ብርድ ልብስ... የስፖንጅ ያልሆነ ጠንካራ ትራስ!...
ትራሱን አየሁት - ጥቅል ጋዜጣ ነው፡፡ ኮሜዲኖውን አየሁት - ክምር ጋዜጣ ነው፡፡ ጠረጴዛውን አየሁት - ቁልል ጋዜጣ ነው፡፡
ለጊዜው ከጋዜጣው እንቆቅልሽ ይልቅ፣ የርሃብን እንቆቅልሽ መፍታት ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ዳኜ ማታ ሂሳብ ሲከፍል የተወሰነ ገንዘብ እንደተመለሰለት ትዝ ይለኛል፡፡ ያ የተወሰነ ገንዘብ፣ የተወሰነ ዳቦ (የተወሰነ ህይወት) መግዛት ይችላል፡፡
“በማታው መልስ የሆነ ነገር ግዛና እንቀማምሳ!?...” ስል ጠየቅሁት ዳኜን - ሞት ሞት እያገሳሁ፡፡
የዳኜን መልስ፣ የበሩ ድምጽ ቀደመው፡፡
በሩ ዳግም ተንኳኳ፡፡ ዳኜ ፈጠን ብሎ ሄዶ ከፈተው። ቀደም ብሎ ልኮ ነበር ማለት ነው አልኩ በደስታ ተውጬ፡፡ በበሩ ክፍተት ውስጥ፣ በፌስታል የተጠቀለለ ዳቦ እና የታሸገ ወተት ብቅ ሲል ለማየት ጓጉቻለሁ፡፡
ዳኜ ከጠይም እጅ የተጠቀለለ ጋዜጣ ተቀበለ። ዳኜ  ለጠይሙ እጅ የተጠቀለለ ብር ሰጠ (ከማታ የተረፈውን)፡
ጋዜጣውን አየሁት - ከውስጡ የተጠቀለለ ዳቦ የሌለበትን!...
“ምንም የለውም እንዴ?” አልኩት እንደመናደድ እያደረገኝ፡፡
“ሁሉም አለው!...” አለኝ ዳኜ ፈገግ ብሎ፣ የተጠቀለለውን ጋዜጣ እየፈታ፡፡
አይኖቼን ተጠራጥሬ እንደገና አየሁት፡፡ ግንባሩ ላይ ብርቱካናማ ጥለት ያረፈበት ጋዜጣ ከፊት ለፊቴ ተዘረጋ፡፡ ግራ ተጋብቼ ዙሪያዮን ተመለከትኩ፡፡ የጋዜጣ ትራስ፣ የጋዜጣ ጠረጴዛ፣ የጋዜጣ ወንበር... እና ደግሞ... ከጓደኛዬ ፊት ላይ ሲንቀለቀል የሚታይ ʻብርቱካናማʼ የጋዜጣ ፍቅር!...
ዳኜ ገንዘብ አጥቶ እራት ላይበላ ይችላል፡፡ ለቁርስ ቸግሮት ጦሙን ሊያረፍድ ይችላል፡፡ የወር የቤት ኪራይ ይከፍለው አጥቶ፣ ከአከራይ ጥላ ሊሸሽ ይችላል፡፡ ብዙ--ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን፣ ሳምንት ጠብቆ ቤቱ ድረስ ለሚመጣለት ለብርቱካናማው ጋዜጣ ይከፍለው ገንዘብ አያጣም፡፡
ይህ ከሆነ ከአመታት በኋላ...
እኔም የዳኜን ልክፍት ተለከፍኩ፡፡ ብርቱካናማው ጥለት ይናፍቀኝ ጀመር፡፡ ቅዳሜ ሳምንት ጠብቃ ፍንትው የምትል ብርቱካናማ ናፍቆት ሆነችብኝ፡፡
እዚህ ቀለም ውስጥ...
ከብዙዎች ጋር ዋኝቻለሁ፡፡ በብዙዎች የብዕር ጠብታ ውስጤን አረስርሻለሁ፡፡ ከብዙዎች ጋር አውግቻለሁ፡፡ ተገርሜያለሁ፡፡ ተደምሜያለሁ፡፡ ለአመታት “የተጠበለ” የሳምንት ጥዋ ጠጥቻለሁ፡፡ ወር ተራዬ ደርሶኝ፣ “እኔ አለሁ ባለወር ባለሳምንት!...” ብያለሁ፡፡ ከኑሮ ከፍ ዝቅ በተረፈኝ ፋታ፣ ያቅሜን ያህል ደግሻለሁ... አረረም መረረም የመቻሌን ታህል ነፍስ ያፈራውንʼ አቃምሻለሁ፡፡
እዚህ ቀለም ውስጥ...
ብዙ ስሜቶቼን ነክሬ አቅልሚያለሁ፡፡ ከውጭ ሆኜ መናፈቄን ትቼ፣ በለስ ቀንቶኝ ራሴን ከቀለሙ ጋር ለውሻለሁ፡፡ እዚህ ጋዜጣ ገጾች ውስጥ፣ የውስጤን ስሜት አፍስሻለሁ፡፡ እነዚያ ቅዳሜዎች ላይ፣ ብዙ መከፋቶቼን፣ ብዙ መደሰቶቼን፣ ብዙ እየቅል ስሜቶቼን አትሜ አልፌያለሁ፡፡
አስራ አምስተኛዋ አደይ ስትፈካም... የመስቀል ወፍ ከአዲስ አድማስ ስር ዳግም ለአስራ አምስተኛ ጊዜ ክንፎቿን እየጠፈጠፈች ከተፍ ስትልም... እኔ ከዚህ ቀለም ጋር ነኝ!... ብርቱካናማው ጥለት አብሮኝ አለ!...

Read 2469 times