Wednesday, 11 March 2015 11:54

“ተማሪዎቼ ጥናት ሲሰሩ አድማስን ይጠቀማሉ

Written by 
Rate this item
(11 votes)

አቶ ተሻገር ሽፈራው
(በአ.አ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር)

     አድማስን ከሌሎች ጋዜጦች ለየት የሚያደርገው በርካታ ጉዳዮች አሉት፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ አጫጭር ልቦለድ ሳያቋርጥ ማስተናገዱ ሲሆን ሌላው የርዕሰ አንቀፁ ይዘትና አፃፃፍ ነው፡፡ የአማርኛ ቋንቋ አጠቃቀሙም ጥንቃቄ የተሞላበት መሆኑ ይሰማኛል፡፡ እየተጀመሩ መቋረጥ የአገራችን ጋዜጦች መገለጫ በሆነበት ዘመን፣ አዲስ አድማስ 15 ዓመታትን መዝለቁም ልዩ ያደርገዋል፡፡ አድማስን ማንበብ የጀመርኩት ገና ሲጀመር ነው፡፡ በደንብ አውቀዋለሁ፡፡ ላለፉት 15 ዓመታት የራሱን ማንነት (የጋዜጣ ሰብዕና) ገንብቶ ቀጥሏል፡፡ እኔ በማስተምርበት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎቼ ለምረቃ ጥናት ሲሰሩና አሳይመንት ስሰጣቸው አዲስ አድማስን በብዛት ይጠቀማሉ፡፡
በአጠቃላይ ጋዜጣው “አዲስ አድማስ” ተብሎ ባይፃፍበት እንኳን የሚታወቅና ለሁሉም አንባቢ የቤተሰባዊነት ቀረቤታ ያለው ሲሆን ከማነባቸው ሁለትና ሶስት ጋዜጦች ቀዳሚው ጋዜጣ ነው፡፡ በህትመት ዋጋ መናር ይመስለኛል የገፁ ብዛት እየሳሳ መጥቷል፡፡ ያም ሆኖ አድማስን ማንበብ አላቆምኩም፡፡ ለተወሰኑ አመታት እየገዛሁ አስቀምጠው ነበር፡፡ አሁንም አጓጊና ቀልብን የሚስቡ ዜናዎች ሲኖሩት እገዛዋለሁ፡፡ ቅዳሜ ቅዳሜ መግዛት የማልችልበት ቦታ ብሆን እንኳ በዌብሳይት  ሳላነብ የምቀርበት ጊዜ የለም፡፡ በሁላችንም ህሊና ውስጥ በጎ ተፅዕኖ ያሳረፈ ጋዜጣ ነው፡፡ የተዋጡና እንደ ጎደሉ የሚሰሙ አምዶችና ጸሐፍት አሉት፡፡ የቀድሞዎቹም የአሁኖቹም ግን እንደየጊዜያቸው አሪፎች ናቸው፡፡ በተረፈ ጉድለቶቹን እየሞላ፣ እያስተካከለ፣ እያገለገለን ሌሎች አስራ አምስት ዓመታትን እንዲቀጥል እመኛለሁ፡፡

Read 2809 times