Monday, 16 March 2015 10:06

አዘውትሮ ቡና መጠጣት ከልብ ህመም ይታደጋል ተባለ

Written by 
Rate this item
(10 votes)

 በየዕለቱ የተወሰነ ስኒ ቡና አዘውትሮ መጠጣት ከደም ስር መዘጋት ችግር እንደሚታደግና በሰውነት ውስጥ ያለው የደም ዝውውር በአግባቡ እንዲከናወን በማድረግ ለልብ ህመም ከመጋለጥ እንደሚታደግ በጥናት መረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የኮርያ ተመራማሪዎች በ25 ሺህ ወንዶች እና ሴቶች ላይ የሰራውን ጥናት ዋቢ በማድረግ ዘገባው እንዳለው፣ በየዕለቱ ከሶስት እስከ አምስት ስኒ ቡና አዘውትረው የሚጠጡ ሰዎች ለልብ ህመም የመጋለጥ እድላቸው አነስተኛ እንደሆነ ተረጋግጧል፡
ቡና በልብ ጤንነት ላይ የሚያሳድረውን ተጽእኖ በተመለከተ ከዚህ በፊት የተሰሩ ጥናቶች የተለያዩ ድምዳሜዎች ላይ እንደደረሱ ያስታወሰው ዘገባው፣ አንዳንዶቹ ቡና ለልብ ህመም ያጋልጣል ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ በአንጻሩ ጠቀሜታው የጎላ ነው ማለታቸውን ገልጧል፡፡
የኮርያ ተመራማሪዎች ያወጡት የጥናት ውጤት በቡና እና በልብ ጤንነት መካከል ያለውን ትክክለኛ ግንኙነት በተመለከተ ግልጽ መረጃ እንዳልሰጠ የጠቆመው ዘገባው፣ ጉዳዩ አነጋጋሪ መሆን መጀመሩን አስረድቷል፡፡
የብሪቲሽ የልብ ፋውንዴሽን ባልደረባ የሆኑት ቪክቶሪያ ቴለርም፣ የተመራማሪዎቹን የጥናት ውጤት ለማረጋገጥና በቡና እና በልብ ጤንነት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጥራት ተጨማሪ ምርምር ማድረግ ይገባል ብለዋል፡፡ 

Read 13660 times