Saturday, 28 March 2015 08:55

የዘውዲቱ ሆስፒታል ሊፍት ሰው ገደለ

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(13 votes)

የዛሬ ሳምንት ከሰዓት በኋላ ነው፡፡ የ72 ዓመቱ አዛውንት አቶ ካሣሁን አበበ ታምማ ዘውዲቱ ሆስፒታል የተኛች እህታቸውን ለመጠየቅ ሄዱ፡፡ ሆስፒታል ደርሰው እህታቸው ወደተኙበት ክፍል ለመሄድ የሊፍቱን መጥሪያ ሲጫኑት ተከፈተ፡፡
ሊፍቱ ተበላሽቶ ስለነበር ሰው መጫኛው ወለል አልነበረም፡፡ አቶ ካሳሁን ወለሉ ያለ መስሏቸው ዘው ብለው ሲገቡ ጉድጓድ ውስጥ እንደገቡ ልጃቸው ፍቅርተ ካሳሁን ተናግራለች፡፡
አቶ ካሳሁን “እርዱኝ እርዱኝ” እያሉ ሲጣሩ አንድ የጽዳት ሠራተኛ ሰምታ ሰው በመጥራት ተረባርበው ካወጧቸው በኋላ ወደ ድንገተኛ ክፍል እንደወሰዷቸው የገለፀችው ፍቅርተ፤ ወደ 10 ሰዓት ገደማ ቤተሰብ ተጠርቶ ሲደርስ አቶ ካሳሁን በፅኑ ይተነፍሱ እንደነበርና ጣቶቻቸው ከመጋጋጣቸው በስተቀር የሚፈስ ደም እንዳልነበረ ጠቁማለች። ልብሳቸው በተቃጠለ ዘይት ተለውሶ እንደነበር ጠቅሳ ትንሽ ቆይቶ ሕይወታቸው እንዳለፈ ፍቅርተ ገልጻለች፡፡  አደጋው ስለተከሰተበት ሁኔታ ለማወቅ ዘውዲቱ ሆስፒታል ብንሄድም የሆስፒታሉ አስተዳዳሪ ዕረፍት ላይ ስለሆኑ ልናገኛቸው አልቻልንም። እሳቸው የወከሏቸው ሜዲካል ዳይሬክተር “አሁን ስብሰባ ላይ ነኝ፡፡ ስለጉዳዩ ድንገተኛ ክፍል ጠይቁ። ለእኔም የነገሩኝ እነሱ ናቸው” ብለውናል። ድንገተኛ ክፍል ስንጠይቅ በዕለቱ ተረኛ የነበሩትን ዶክተሮች አነጋግሩ የተባልን ሲሆን ተረኛ ዶክተሮቹ በበኩላቸው፤ ኦፕሬሽን እያደረግን ስለሆነ እስክንጨርስ ጠብቁ አሉን። ሆኖም ማተሚያ ቤት የመግቢያ ሰዓታችን በመድረሱ ምላሻቸውን ለማካተት አልቻልንም፡፡
አቶ ካሳሁን የ3 ወንዶችና የ5 ሴቶች አባት ነበሩ።

Read 8296 times Last modified on Saturday, 28 March 2015 09:01