Monday, 06 April 2015 07:56

የቦብ ማርሌይ ሃውልት ለዳግማይ ትንሳኤ ይመረቃል

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(12 votes)

ከ20 ሺህ ሰው በላይ  የሚታደምበት ትልቅ ኮንሰርት ይካሄዳል

በገርጂ ኢምፔሪያል ሆቴል ፊት ለፊት የሚተከለው የሬጌው ንጉስ የቦብ ማርሌይ ሃውልት የዳግማይ ትንሳኤ ዕለት እንደሚመረቅ ታዋቂው ድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰ፣ የአርቲስቶች ማናጀር አዲስ ገሰሰና የኪነ-ጥበብ አድናቂው አዋድ መሃመድ ሰሞኑን በጋራ በሰጡት  ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቁ፡፡
ከ10 ዓመታት በፊት የሬጌውን ንጉሥ 60ኛ ዓመት የልደት በዓል ለማክበር በኢትዮጵያ የተካሄደውን ታላቅ የሙዚቃ ኮንሰርት ተከትሎ የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ዶ/ር አርከበ እቁባይ ኢምፔሪያል ሆቴል ፊት ለፊት የሚገኘውን አደባባይ “ቦብ ማርሌይ አደባባይ” ብለው መሰየማቸው ይታወሳል፡፡
“አደባባዩ ከተሰየመ አይቀር ለምን ሃውልቱ አይቆምም” የሚል ሃሳብ ያመነጩት ወንድማማቾቹ ዘለቀና አዲስ፤ የቦብ ማርሌይን ሃውልት በእውቁ ሰዓሊና ቀራፂ ብዙነህ ተስፋ ማሰራታቸውን ጠቁመው ሚያዚያ 10 ቀን 2007 ዓ.ም የዳግማይ ትንሳኤ ዕለት እንደሚመረቅ አስታውቀዋል፡፡ 3 ሜትር ከ80 ሳንቲ ሜትር ቁመት ያለውን የቦብ ሃውልት የሰራው ቀራፂ ብዙነህ ተስፋ በሰጠው አስተያየት፤  “ሃውልቱ ከሁሉም በላይ በሙዚቀኞችና በሙዚቃ አፍቃሪዎች ተነሳሽነት መተከሉ አስደስቶኛል” ብሏል፡፡  
ሃውልቱ ከተመረቀ በኋላ እዚያው አካባቢ በሚገኘው የወጣቶች ስፖርት አካዳሚ ግቢ ውስጥ ታላቅ የሙዚቃ ኮንሰርት የሚካሄድ ሲሆን ከ20ሺ ሰው በላይ በነፃ እንደሚታደምበት ይጠበቃል፡፡ በኮንሰርቱ ላይ ጃሉድ አወል፣ ዘለቀ ገሰሰ፣ አብነት አጎናፍር፣ ኬኒ አለን፣ ሲድኒ ሰለሞን፣ ጆኒ ራጋ፣ ራስ ጃኒ፣ ሸዋንዳኝ ሃይሉ፣ የሺ ደመላሽ እና ሌሎችም ዕውቅ ድምፃውያን የሚካፈሉ ሲሆን ጃኖ፣ መሃሪ ብራዘርስና ብሉ ቫይብስ የሙዚቃ ባንዶች አቀንቃኞቹን እንደሚያጅቧቸው ታውቋል፡፡
ከኮንሰርቱና ከሃውልት ምረቃው ጎን ለጎን የቦብ 70ኛ ዓመት የልደት በዓልም እንደሚከበር አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የጤና እክል የገጠማት የቦብ ባለቤት ሪታ ማርሌይ፤ ጤናዋ ከተስተካከለላት በዝግጅቱ ላይ በክብር እንግድነት እንደምትገኝ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡

Read 4104 times