Tuesday, 14 April 2015 07:47

የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ፓስፖርታቸው ተመለሰላቸው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(11 votes)

የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ባለፈው ሳምንት ወደ አሜሪካ ሊጓዙ ሲሉ ቦሌ አየር ማረፍያ ላይ ፓስፖርታቸው ተወስዶ ከጉዟቸው ተስተጓጉለው የነበረ ሲሆን ሰሞኑን ፓስፖርታቸው እንደተመለሰላቸው ገለፁ፡፡
ፓስፖርታቸው ለምን እንደተወሰደባቸው አሁንም ድረስ እንዳልተገለፀላቸው የጠቆሙት ኢንጂነሩ፤ በፓስፖርቱ መወሰድ የተስተጓጐለውን የፓርቲያቸውን የአሜሪካ ስብሰባ በስካይፒ ለመሳተፍ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት ወደ አሜሪካ ለመጓዝ የሚያስፈልጉ ሰነዶችን አሟልተው ቦሌ ኤርፖርት ከሄዱ በኋላ ፓስፖርታቸው በፀጥታ ሃይሎች ተወስዶ ከጉዟቸው መደናቀፋቸውን ያስታወሱት ኢንጂነሩ፤ የዜግነትና ኢምግሬሽን ጉዳይ ጽ/ቤት ተመላልሰው ፓስፖርታቸው እንዲመለስላቸው መጠየቃቸውን ጠቁመው ባለፈው ማክሰኞ የተነጠቁበት ምክንያት ሣይገለጽላቸው እንደተመለሰላቸው ተናግረዋል፡፡
ከፋሲካ በኋላ በድጋሚ ጉዟቸውን የሚያደናቅፍ ተመሳሳይ ችግር ካልገጠማቸው ወደ አሜሪካ በማቅናት በአራት ግዛቶች ፓርቲው ያዘጋጃቸውን ስብሰባዎች እንደሚመሩም ከፓርቲው የተገኙ መረጃዎች ጠቁመዋል። 

Read 2934 times