“ዘ አርቲስት› የተሰኘው ድምፅ አልባ ፊልም 3 የጎልደን ግሎብ ሽልማቶች ከወሰደ በኋላ በኦስካር የ”ዓመቱ ምርጥ ፊልም” ሽልማት ዋና ተቀናቃኝ ሆነ፡፡ ባለፈው እሁድ በቤቨርሊው ሂልተን ሆቴል በተካሄደው የዘንድሮው የጎልደን ግሎብ ስነስርዓት ላይ “ዘ አርቲስት” ከፍተኛ አድናቆት ያገኘ የዓመቱ ፊልም እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ በ12 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተሰራው ፊልሙ፤ ፈረንሳዊ ድባብ የጐላበት ሮማንቲንክ ኮሜዲ ነው፡፡ ፊልሙ በሆሊውድ መንደር በ1920ዎቹ መጨረሻ የድምፅ አልባ ፊልሞች እየቀሩ መምጣታቸው ዝናውን ስለሸረሸረበት ተዋናይ ይተርካል፡፡“ዘ አርቲስት” በዘንድሮው የጎልደን ግሎብ ሽልማት በ6 ዘርፎች በመታጨት ከፍተኛ ትኩረት ስቦ የነበረ ሲሆን የዓመቱ ምርጥ ፊልም፤ የዓመቱ ምርጥ ሙዚቃዊ ወይም የኮሜዲ ፊልም እና የዓመቱ ምርጥ ሙዚቃዊ ወይንም የኮሜዲ ፊልም ተዋናይ በሚሉ ዘርፎች ሦስት የጐልደን ግሎብ ሽልማቶችን አግኝቷል፡፡ ፊልሙ ከጎልደን ግሎብ በፊት ከ”ክሪቲክስ ቾይዝ አዋርድ” 4 ትላልቅ ሽልማቶችንም ያገኘ ሲሆን “ባፍታ አዋርድስ” በሚል በሚታወቀው የሽልማት ተቋም ደግሞ በ12 ዘርፎች እንደታጨ ታውቋል፡፡