Saturday, 25 April 2015 10:17

በሊቢያው የጀልባ አደጋ አንድ ኢትዮጵያዊ መሞቱ ተረጋገጠ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(12 votes)

    ባለፈው እሁድ ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ከ900 በላይ የተለያዩ አገራት ስደተኞችን አሳፍራ ስትጓዝ በሜዲትራኒያን ባህር የመስጠም አደጋ በደረሰባት ጀልባ ከሞቱት መካከል አንዱ በአዲስ አበባ የኮተቤ ነዋሪ የነበረው እንዳልካቸው አስፋው ይገኝበታል፡፡ በታክሲ ረዳትነትና ሹፌርነት ይተዳደር የነበረው እንዳልካቸው፤ ኑሮን ለማሸነፍ የተሻለ ስራ ፍለጋ የዛሬ 6 ዓመት ወደ ሱዳን ማቅናቱንና እዚያ ለ5 ዓመታት ከቆየ በኋላ ከዓመት በፊት ሊቢያ መድረሱን ደውሎ እንዳሳወቃቸው ቤተሰቦቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ “ለረጅም ጊዜ ድምፁ ጠፍቶብን ነበር” የሚሉት ቤተሰቦቹ፤ በሊቢያ ያለው ሁኔታ አስጨናቂ እየሆነ ከመጣበት ጊዜ አንስቶ በሃሳብና በሰቀቀን ‹እንዴት ሆኖ ይሆን?› እያሉ ድምፁን ለመስማት በመናፈቅ ወደ ፈጣሪያቸው ይለማመኑ እንደነበር ይገልፃሉ፡፡ በመጨረሻቡ ባልጠበቀው ሁኔታ እንደወጣ የቀረውን የእንዳልካቸውን ህልፈት የሰሙት ባለፈው ረቡዕ መሆኑን ወንድሙ ሙሉጌታ አስፋው ተናግሯል፡፡ የእንዳልካቸውን ህልፈት በስልክ ለቤተሰብ ያረዱት ለቀጣዩ የባህር ጉዞ ተረኛ የነበሩና እርሱን በቅርበት የሚያውቁት ስደተኞች ናቸው፡፡ “ወንድማችን ሱዳን ውስጥ ሲኖር የተለያዩ ስራዎችን እየሰራ ራሱን ያስተዳድር ነበር” የሚለው የሟች ወንድም፤ ባጠራቀመው ገንዘብ የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ወደ አውሮፓ ለመሻገር ጥረት ሲያደርግ ባደረገበት አጋጣሚ ከቤተሰቡ እንደተነፋፈቀ መቅረቱ ለቤተሰቡ መሪር ሀዘን እንደሆነበት ተናግሯል፡፡ “ዴይሊ ሜይል” ጀልባዋ 950 ኤርትራዊያን፣ ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያውያን ስደተኞችን አሳፍራ ስትጓዝ መስጠሟን የዘገበ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ 200 ያህሉ ሴቶች እንደነበሩ ጠቁሟል፡፡ ከአደጋው የተረፉት 28 ብቻ መሆናቸውን የዘገበው ጋዜጣው፤ ሲሆኑ አስክሬናቸው የተገኘው የ20ዎቹ ብቻ ነው ብሏል፡፡ “አልጀዚራ” እና “ዘ ጋርዲያን” በበኩላቸው ጀልባዋ 700 ስደተኞችን አሳድራ እንደነበር ጠቁመውየተረፉት 28 አስከሬናቸው የተገኘው 20 ብቻ መሆኑን ዘግበዋል፡፡ አደጋው የተፈጠረው በጀልባዋ ላይ ተፋፍገው የተጫኑት ስደተኞች በርቀት ሌላ የንግድ መርከብ
ተመልክተው ጥሪ ለማቅረብ ሲሉ በፈጠሩት ግርግር ጀልባዋ ሚዛኗን በመስጠሟ ነው ብለዋል ዘገባዎች፡፡
ከአደጋው የደረሰው ከሊቢያ የባህር ዳርቻ 96 ኪ.ሜ እንዲሁም ከጣሊያኗ የስደተኞች መዳረሻ
ላምፔዱሣ ደሴት 193 ኪ.ሜ ርቀት ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

Read 5422 times