Saturday, 02 May 2015 12:36

የአስከሬኑ ሳጥን የመጨረሻ ሚስማሮች

Written by  በደረጀ ይመር
Rate this item
(6 votes)

   ወደ  አስኳላ ሲሰዱኝ የስደት ሕይወትን አሀዱ አልኩኝ። ከጎጆዬ ተነቅዬ ወደ አዲስ ግዛት በመጓዝ ከየኔታ እግር ስር ሆኜ ሀሁ ማለት ጀመርኩ። የኔታ ከነፍሴ ጋር የነበረችውን ቀጭን ገመድ ለመበጠስ ክርክሩን በማስፋት ጀመሩ።  የአቅማቸውን አበጃጅተውኝ ለቀጣይ የሙያ ጓዳቸው  አቀበሉኝ። በቅብብሎሽ ሲያገላብጡኝ ሲጠጋግኑኝ አዘገምኩ። ስመስል ሳስመስል እንድኖር ተፈረደብኝ። የወንዜ አድባር  ባበጀለኝ ሕግ እና ደንብ ስፈራ ስቸር ይኸው እንዳለሁ አለሁ። ትውልድ “ቀራጩ”፣ መምህሬ ይሄንን ትመስላለህ ብሎ ከፊት ለፊቴ የቁም መስታወት ደነገረብኝ:: እኔም ተጨብርብሬ ይሄንን እመስላለሁ ብዬ ደመደምኩ። እውን ይሄን እመስላለሁ?
በቤቴ በእናት ጓዳ እያለሁ የአላፊ አግዳሚውን አይን የምይዝ እምቦቃቅላ ነበርኩ። በእረኝነት ከመስክ ላይ ስቦርቅ የተመለከተ አንድ የጥበብ ሰው ፎልፏላ ለጋው የጨቅላ ገጽታዬን በአስደማሚ የጥበብ ሥራ በሸራ ላይ ወጥሮ ቀለም ረጭቶ አበጃጀኝ። ሀገር ምድሩ ይህንን ገጽታዬ ያለበትን ሸራ በየቤቱ አንጠለጠለው። በእኔ የጨቅላ ፎቶ የማይባረክ ሀገሬው አልነበረም። ይህ መሰሪ የጥበብ ሰው አሁን በግዞት ላይ ያለኝን ገጽታ በተለመደ የጥበብ ሥራ ውብ አድርጎ ቀረጸኝ። ከዓመታት በፊት ያበጃጀኝ ጨቅላው እረኛ እንደነበርኩ ሰዓሊው ልብ አላለም ነበር። ይሄኛውን ገጽታዬን ግን ደፍሮ የሚመለከትለት ጠፋ። የልጅነት እና “የአዋቂነት” (የግዞት) ገጽታዬን መሳ ለመሳ ሰቆሎ እያየ በተቃርኗቸው ተሳለቀ።
ሁለቱም ባለሙያዎች በየፊናቸው አበጃጅተው ያኖሩት ሰው ሆኜው አረፍኩ። መምህራኖቼ የመንፈስ ክሳቴን። ሰዓሊው በአካል መጠውለጌን። ከልጅነት እስከ እውቀት። ከየኔታ እስከ ኮሌጅ መበጠስ። በሁለት ሀዲድ ተጓዝኩ። የማይፈራው ፎልፏላው፣ ብሩሁ ሰብእና አሁን ከእዚህ የለም። ከእዚህ ያለው ሰብእና ሁለተኛው፣ ስደተኛው “አዋቂው” ነው፡፡ በኮሽታ ይደነብራል፤ ስንዝር ተራምዶ ኋላውን ይሰልላል፤ ስሜቱ በየአፍታው የሚጎዳ የስለት ልጅ ነው። በክርታስ ተከልሎ ቢኖር ግድ የማይለው፣ ጉስቁልናን የእጅ አምባሩ፣ ጌጡ የሚያደርግ ባተሌ ፍጡር ነው። ጠብ ያለሽ በዳቦ ምግባሩን ባልንጀራው ላይ ሳይቀር የሚያሳይ፣ ከሳር ከቅጠሉ ደም የተቃባ፣ የቃየል ምግባር ከላዩ ላይ የተደፈደፈበት ትልቁ፣ ስደተኛው ሰው ነው እዚህ ያለው።
ደግሞ እዚህ ሌላ ሰው አለ። አቤል። የበኽር ልጅ ነው። ድሮ የነበረ። ወደፊትም የሚኖር አልፋ እና ኦሜጋ። በእረኝነት በልጅነት እንደተያየን ነው። ከአይን የራቀ ከልብ ያልራቀ። በልብ የታተመ ዘላለማዊ ትስስር። ሃገሩ ሰማይ ወሰኑ አድማስ ነው። ጠጠር ላበደረ ወርቅ ይሰጣል። ልግስናው ከሃገሬው ደንብ ጋር አይገጥምም። የፍቅር እና የሀሴት ቤተመቅደስ ነው። የብርሃኑ ወጋገን ለእልፍ አዕላፍ ይተርፋል። ሰላምም ደስታም ከእዚሁ ከደጁ ነው የበቀሉት።
ልጅነቴ አቤል እና ስደተኛው ቃየል እሰጣ ገባ አላስቆም አላስቀምጥ አለኝ። አንተ ትብስ አንቺ ትብስ ተባብለው በአንድ ጣሪያ ስር መኖር የማይታሰብ ሆነ። ልጅነቴ አቤል በተመስጦ ነው የሚያረፋፍደው። ስደተኛው፣ “አዋቂው” ቃየል ይህንን ተመስጦ ከድፍረት ይቆጥረዋል። አቤል ግራውን ሲመታ ቀኙን ለዳግም ምት ያዘጋጃል። ለቃየል። ቃየል ቢወግር ቢወግር ክንዱ የማይዝል ሞገደኛ ነው። ማጀቱን የሞላው የንጹሀንን አንገት መበጠሺያ ቀስት ነው። ግፉን ለመጋት ቤት ለእግዚሀር ይላል። መካን አንጀቱ በአቤል በወላድ አንጀት ላይ ይጨክናል። የተመኘውን የሚያድነው ጦረኛው ቃየል ውስጤ ላይ አቆጥቁጦ ….አቁጥቁጦ….ውሎ አድሮ ወደ ደንነት ተለወጠ። የቃየልን ደን ለበሰኩኝ።
በቃየል ደን ውስጥ ሰላም እና ፍቅር ታዳኝ አውሬዎች ናቸው። የቃየል መስዋዕቶች ደም እረፍት እየነሳኝ ተቸገርኩኝ። ቃየል እና አቤል። ልጅነት እና ጉልምስና። የምስራች እና መርዶ። ፍትህ እና እድሎዎ። ንፉግነት እና ልግስና። ብጽህና እና እርኩሰት። ብህትና እና ግርግር። ሁለት እኔነቶች እንዴት ይኑሩ?
ከእጄ ላይ ነፍስ ሊያልፍ ነው። የንጹህ ነፍስ እንዳልሆነ እረዳለሁ። ደሙ ደመ ከልብ ሊሆን። ከላዬ ላይ ዱቄት እንደጠገበ ማዳበሪያ ሊራገፍ። ቁርጠኛ ውሳኔዬን እንደ ምጽአት ቀን ለዘመናት ተጠባበቀ። እርግጥ ነው ሀሞቴን ኮስተር አድርጌያለሁ። ወንድ ወንድ እየሸተትኩ ነው። ስደተኛውን ቃየል ጨለምለም ካለው ጎሬው አባብዬ ወደ አውላላ አውጥቼ ሞትን ጋትኩት።
ፍርደ ገምድል እንዳልሆኑክ ይገባኛል። “የገደለው ባልሽ የሞተው ወንድምሽ ሀዘንሽ ቅጥ ያጣ ከቤትሽ አልወጣ።” ጉንጭ አልፊ ስንኝ ሆነብኝ።
ዝምድናውም ቅርርቡም ይቅርብኝ ብዬ ቃየልን ገደልኩት። ፋኖ ተሰማራን በቃየል ላይ ተገበርኩት። ቃየል፣ ስደተኛው ሰብዕና ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ አሸለበ። አሁን ያለው የድሮ ቤቴ ልጅነቴ፣ አቤል ነው።
 ዛሬ የቃየል የቀብር ስነ-ስርዓት የሚከበርበት ቀን ነው። የአብራኩን ክፋይ ያጣው ጀማው ፊቱ ጠይሟል። ሰማዩ አኩርፏል። የወንዜው ነዋሪ የአብራኩን ክፋይ በድኑን ሊሸኝ በነቂስ ነው የወጣው። እዚህም እዚያ ደረት ይደቃል።
እምባ ይንዠቀዠቃል። ተንዠቅዥቆ ተንዠቅዥ… መስኩን እንደ ጠል አውርዝቶታል። ስለ ቃየል ገድል አስለቃሿ ስንኞችን ትደረድራለች ፡-
አንበሳን ሲገድል
 ጎሽንም ሲገድል
  ወንድነት
  ሳይጓደል
 በቀን-ጎዶሎ
 ከአፈር ሊመሳሰል
ከእኔ በላይ ማወቋ ደንቆኛል። የአደባባይ ገበናን እንደታቀፍኩ ገባኝ። ሁሉም የሚያውቀው ጸሀይ የጠገበ ገበና። ገድለ ብዙው ቃየል ለኑዛዜ እንኳን የተውኩለት ቅጽበት አልነበረም። እንደው በድንገት ግጥም አለ።
ጀማውን ሳይሰናበት፣ ለበሽታው ሳይጫጫስለት የብኩን ሞትን ሞተ። ሀዘኑን ያከፋው ይህ ሳይሆን አይቀርም።
ወደ ተማሰው ጉድጓድ እየተቃረብን ሳለ ድንገት የዘነጋሁት ነገር እንዳለ ታወሰኝ። ለቃየል መቀበር፣ለጠንቀኛው ሰብዕና ማሸለብ ወሳኙ መከርቸሚያ የመጨረሻ ሚስማሮች አልተመቱም፡፡ ቃየልን በቃል ገድዬው ተግባሩን ዘንግቼው ኖሯል። ንጽሕናን በመሃላ በቃላት ጨዋታ ከውኜ፣ ቃየልን አዳፍኜው ኖሯል፡፡ የተሸከምኩትን ሳጥን በፍጥነት አወረድኩ። ሚስማሮቹን አውጥቼ ገርበብ ያለውን ሳጥን ልከረችመው ስንደረደር ሬሳው ድምጽ አሰማ። ለቀስተኛው በኦኦታ በእልልታ… በሽለላ የሀዘኑን አየር ገረሰሰው። አይኔን ማመን አልቻልኩም። ቃየል ሳጥኑን በርግዶ ጣቱን ወደ እኔ እየጠቆመ ተጠጋኝ፤
“ከደመኛዬ ጋር ምን ጉዳይ አላችሁ? ይህ አመለኛ ከብት እንዳይበጠብጣችሁ ፈጥናችሁ አብሩት” አለ ለለቀስተኛው፡፡
ቃየል እንደጨከንኩበት እርሱም በተራው ጨከነብኝ። ሁለት ወዶ አይሆንም። እኔም አቤልን፣ ልጅነቴን ይዤ እግሬ አውጭኝ ብዬ ጀማውን ተለየሁ።
በሽሽት፣ አይንን በመክደን ከአቤል ጣውንት ከቃየል ለጊዜው ነፃ ሆኜ ይሆናል…..ግን ግን….. ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ…..ካልፈጣጠምኩት……መልሶ ምርኮው የሚያደርገኝ ቀን ሩቅ አይሆንም፡፡

Read 3488 times