Saturday, 16 May 2015 10:17

ኤርትራዊው ዲፕሎማት በኢትዮጵያ ጥገኝነት ጠየቁ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

ላለፉት አምስት አመታት በአፍሪካ ህብረት የኤርትራ ልኡክ ሆነው ያገለገሉትና ከአገሪቱ ከፍተኛ ዲፕሎማቶች አንዱ የሆኑት አምባሳደር ሞሃመድ ኢድሪስ ጃዊ፤ የኤርትራ መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን ጭቆናና የመብቶች ጥሰት በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት መጠየቃቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፍትህና ነጻነትን ለመጎናጸፍ ለዘመናት የታገለው የኤርትራ ህዝብ፤ በኢ-ፍትሃዊ አገዛዝ ስር እየማቀቀ ይገኛል ያሉት አምባሳደሩ፤ ይህም የኤርትራን መንግስት የጭቆና አገዛዝ በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት ለመጠየቅ ውሳኔ ላይ እንዳደረሳቸው ተናግረዋል፡፡
በኤርትራ የነጻነት ትግል ዘመናት በትግል ያሳለፉት አምባሳደር ሞሃመድ፤ኤርትራ ነጻነቷን ከተጎናጸፈች  በኋላም በተለያዩ ከፍተኛ የስልጣን ቦታዎችና በአህጉራዊ የዲፕሎማቲክ ስራዎች ላይ ለአመታት ማገልገላቸው ተነግሯል፡፡
የመብት ተሟጋች ቡድኖችና የተለያዩ ተቋማት፣ የኤርትራ መንግስት በመብቶች ጥሰትና በአስገዳጅ የወታደራዊ አገልግሎት ዜጎቹን እያሰቃየ ነው ሲሉ አገዛዙን ቢተቹም፣ የኤርትራ መንግስት ግን የሚሰነዘሩበትን መሰል የመብቶች ጥሰት ውንጀላዎች በተደጋጋሚ እንደሚያጣጥል አስታውሷል፡፡
የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በአምባሳደሩ የጥገኝነት ጥያቄ ዙሪያ ያላቸውን አስተያየት እንዲሰጡት ያደረገው ሙከራ እንዳልተሳካለት ሮይተርስ ገልጧል፡፡

Read 4376 times