Saturday, 16 May 2015 10:18

“ሆላንድ ካር” ወደ ሥራ ሊመለስ ነው 63 ሚሊዮን ብር ኪሳራ ደርሶበታል

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(5 votes)

ገንዘብ ከፍለው መኪናቸውን ላልተረከቡ 115 ደንበኞች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ አስረክባለሁ ብሏል፡፡

    ድርጅቱ በደረሰበት ከፍተኛ ኪሳራ ስራቸውን አቁመው ከአገር የተሰደዱት የ “ሆላንድ ካር” ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ታደሰ ተሰማ፤ መንግስት ባደረገላቸው ድጋፍና በተሰጣቸው የህግ ከለላ ከ3 ዓመት በኋላ ወደ አገራቸው መመለሳቸውን ገለፁ። ለመንግስት ያቀረቡት አዲስ ፕሮፖዛል ተቀባይነት ማግኘቱንና ወደ ሥራቸው በመመለስ መኪኖችን ሰርተው ለደንበኞቻቸው ለማስረከብ መዘጋጀታቸውን ገለፁ፡፡
ሥራ አስኪያጁ ከትናት በስቲያ በኢንተር ኮንትኔንታል ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ድርጅቱ ባጋጠመው ከ63 ሚሊዮን ብር በላይ ኪሣራ አማካኝነት ሥራቸውን አቁመው ከአገር በመሰደድ ላለፉት 3 ዓመታት በተለያዩ የአውሮፓ አገራት የፋይናንስ ምንጭ ሲያፈላልጉ ቆይተዋል። በአሁኑ ወቅት ከተለያ ኩባንያዎች ባገኙት ገንዘብ ድጋፍና መንግስት ባደረገላቸው የህግ ከለላ ወደ አገራቸው መምጣታቸውን የተናገሩት ኢንጂነር ታደሰ፤ የኩባንያውን ሥራ ለማስቀጠልና ገንዘባቸውን ከፍለው መኪኖቻቸውን ላልተረከቡ 115 ደንበኞች በአጭር ጊዜ ውስጥ መኪኖቻቸውን ሠርቶ ለማስረከብ ዝግጅታቸውን አጠናቀው መምጣታቸውን ተናግረዋል፡፡
ቤልጂየም ብራሰልስ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አምባሳደር አቶ ተሾመ ቶጋ፤ ልዩ ድጋፍና ትብብር እንደተደረገላቸው የገለፁት ኢንጂነሩ፤ ኩባንያው የገጠመውን የፋይናንስ ችግር በመቅረፍ በተገቢው መንገድ ሥራቸውን እንደሚያከናውኑና በአጭር ጊዜ መኪኖችን አምርተው ለደንበኞቻቸው እንደሚያስረክቡ ገልፀዋል፡፡ ይህ ደግሞ “ሆላንድ ካር” እንዲያንሰራራና በሥሩ የሚተዳደሩ የነበሩት ከ250 በላይ ሰራተኞች የሥራ ዕድል እንደገና እንደሚከፍት ኢንጂነሩ ተናግረዋል፡፡   

Read 4105 times