Saturday, 06 June 2015 13:55

የእሳት ቃጠሎ ትናንት በመርካቶ ንብረት አወደመ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(11 votes)

7 ሰዎች ላይ ጉዳት ደርሷል
             
   በአዲስ አበባ መርካቶ ወረዳ 8 ሸራ ተራ ተብሎ በሚታወቀው ቦታ ላይ ትናንት የደረሰው የእሳት ቃጠሎ ግምቱ ያልታወቀ ንብረት ያወደመ ሲሆን 7 ሰዎች በጭስ የመታፈን አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡
የፕላስቲክ ጫማ ማምረቻ ጨምሮ ወደ 50 የሚጠጉ የብርድልብስና የተለያዩ የላስቲክ ውጤቶች፣ የንግድ መደብሮችና መጋዘኖች መቃጠላቸውን ጉዳቱ ከደረሰባቸው ወገኖች ያገኘነው መረጃ ያመለከተ ሲሆን የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ መቆጣጠር ባለስልጣን በበኩሉ፤ የአደጋው መንስኤና በአደጋው የወደመው የንብረት መጠን እየተጣራ መሆኑን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
እሳቱ የተነሳው ከቀኑ በ8፡50 ገደማ ላይ መሆኑን ከአካባቢው ሰዎች ያገኘነው መረጃ ሲያመለክት የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መቆጣጠሪያ የኮሙዩኒኬሽን ኦፊሰር አቶ ንጋቱ ማሞ፤ ለመ/ቤታቸው ጥሪ የደረሰው 8፡57 ደቂቃ መሆኑንና በ3 ደቂቃ ውስጥ የአደጋ መከላከያ ተሽከርካሪዎችና ሰራተኞች በስፍራው ተገኝተው እሳቱን የማጥፋት ስራ እንደጀመሩ ገልፀዋል፡፡
ከ3 ሰዓት በላይ የዘለቀውን የእሳት ቃጠሎ የእሳትና ድንገተኛ ተሽከርካሪዎች በምልልስ ለማጥፋት ርብርብ ያደረጉ ሲሆን የአየር መንገድ የእሳት አደጋ መከላከያ ተሽከርካሪም ትብብር ማድረጉን አቶ ንጋቱ ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢው ተገኝተን እንደተመለከትነው የአካባቢው ህብረተሰብ አደጋውን ለመቆጣጠር እንዲሁም ከእሳት ቃጠሎብ ንብረት ለማትረፍ ከፍተኛ ርብርብ ያደረጉ ሲሆን በርካታ ሸቀጦችም በዚህ መልክ ማትረፍ መቻሉን ለማየት ችለናል፡፡
እሳቱን በፍጥነት ለመቆጣጠር የቦታው ለተሽከርካሪዎች አመቺ አለመሆንና እንደ ፕላስቲክና ጨርቃጨርቅ ያሉት ተቀጣጣይ ቁሳቁሶች በብዛት መኖር አዳጋች እንዳደረገባቸው የጠቆሙት አቶ ንጋቱ፤ የአደጋ መቆጣጠሩን ስራ ለባለሙያዎች አለመተውም አንዱ ችግር ነበር ብለዋል፡፡ 

Read 4144 times