Saturday, 04 July 2015 09:52

ጥራት ያለው የቢራ ገብስ ያመረቱ ገበሬዎች ተሸለሙ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

ከውጭ የሚገባውን የቢራ ገብስ ምርት እስከ መጪዎቹ ሁለት አመታት ሙሉ በሙሉ ለማስቀረት ታስቦ በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን በመተግበር ላይ በሚገኘው ፕሮጀክት ውጤታማ የሆኑ አርሶ አደሮች ተሸለሙ፡፡
ክሪኤት የተባለውና ላለፉት ሁለት አመታት በዞኑ ሲተገበር የቆየው ፕሮጀክቱ፤ የተሻሻለና ጥራት ያለው የቢራ ገብስ ምርት ማምረት እንዲቻል ለአርሶ አደሮች እገዛ የሚሰጥ ነው፡፡
በግብርና ሚኒስቴርና በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ድጋፍ ሰጪነት የተዘረጋውን ፕሮጀክት፤ የኔዘርላንድ መንግስትና ሔኒከን ቢራ ፋብሪካ በገንዘብ እንደሚደግፉት ታውቋል፡፡
የሔኒከን ኩባንያ የጥሬ እቃ ማበልፀግ ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ጋሩምሳ እንደተናገሩት፤ ባለፉት ሁለት አመታት በዚህ ፕሮጀክት 10ሺ 200 አርሶ አደሮች እንደሆኑ የተደረገ ሲሆን፤ በቀጣዮቹ ሁለት አመታት ተጨማሪ 10ሺ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ውጤታማ ስራ ለማከናወን እንቅስቃሴው ቀጥሏል።
በፕሮጀክቱ ተሳትፈው ውጤታማ እንቅስቃሴ ያከናወኑ ማህበራትና አርሶ አደሮች ሰሞኑን በአርሲ በርሔ ኢ ሆቴል የግብርና መሳሪያዎችና ሌሎች ማበረታቻዎች እንተበረከተላቸው ለማወቅ ተችሏል።
የሔኒከን ኢትዮጵያ ኮርፖሬት ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሮ ሠራዊት በዛብህ በሽልማት አሰጣጥ ሥነ ሥርዓቱ ወቅት እንደገለፁት፤ በዚህ ፕሮጀክት ተሳትፈው ውጤታማ የሆኑ አርሶአደሮችን መሸለም ያስፈለገው ለማመስገንና የበለጠ እንዲተጉ ለማበረታታት ነው፡፡
ፕሮጀክቱ ለአርሶአደሮቹ የሙያ፣ የገንዘብ እንዲሁም የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ጥራት ያለው የገብስ ምርት እንዲያመርቱ የሚያግዝ እንደሆነም ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡ በፕሮጀክቱ ዕቅድ መሠረት፤ ኢትዮጵያ በ2017 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) 20ሺ ሜትሪክ ቶን የቢራ ገብስ በማምረት ከውጭ የምታስገባውን ምርት ታስቀራለች ተብሏል።

Read 2004 times