Saturday, 04 July 2015 10:15

ተቃዋሚዎች የኦባማን ጉብኝት ተቃወሙት

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(21 votes)

“በኢትዮጵያ ስላለው የመብት ረገጣ 90 ሚሊዮን ህዝብ ምስክር ነው”
- ለእድገታችን አሜካ ምስክር ሆነችልን ማለት ውጤት አያመጣም - ዶ/ር መረራ

    በአለማቀፍ ታላላቅ የሚዲያ አውታሮች መነጋገሪያ ሆኖ የዘለቀው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ኢትዮጵያን የመጐብኘት ውጥን አሜሪካ አምባገነን መንግስታትን ከመደገፍ የመነጨ በመሆኑ እምብዛም ትኩረት የሚሠጠው ጉዳይ አይደለም ብለዋል - የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፡፡
ዶ/ር መራራ ጉዲና
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሣይንስ መምህር እና የመድረክ የፖለቲካ ማህበር አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት ዋነኛ ትኩረቱ የሽብር ጉዳይ ነው ይላሉ፡፡
የአሜሪካ ትልቁ ትግል ሽብርተኝነትን ማሸነፍ በመሆኑ ኢትዮጵያ ለአሜሪካ ፀረ - ሽብር ፖሊሲ አጋር ነች መባሉ ለጉብኝቱ ዋጋ አለው የሚሉት ዶ/ር መረራ፣ በዚያው ልክ አሜሪካ አምባገነኖችን የምትደግፍም ሃገር መሆኗን በምሳሌ አስደግፎ ማስረዳት ይቻላል ይላሉ፡፡ በቀዝቃዛው ጦርነት ጊዜ “የኛ ወዳጅ ነው” እያሉ የአፍሪካ ቁጥር አንድ አምባገነን የነበረውን  ሞቦቱ ሴሴኮን እና ሌሎች ነፍሰ ገዳይ የነበሩ መሪዎችን ለራሷ ጥቅም ስትል ስትደግፍ ኖራለች፤ የፕሬዚዳንቱ ጉብኝትም የተለየ አንድምታ የለውም፤ የዚሁ ፖሊሲም ውጤት ነው ብለዋል ምሁሩ - ዶ/ር መረራ። “የኔ አሽከሮች እስከሆኑ ድረስ ምንም ቢያደርጉ ሆዴ አይጨክንባቸውም” የሚል ፖሊሲ ሃገሪቱ አላት” ያሉት ዶ/ር መረራ “እናሸንፋለን ብለው የገቡበት የሽብር ትግል አቅጣጫውን ቀይሮ እየሰፋ መምጣቱ ለጭንቀት ዳርጓቸው ጉዳይ አስፈፃሚ ሃገራትን እንዲንከባከቡ አስገድዷቸዋል” ብለዋል፡፡
“ዲሞክራሲ እንደሸቀጥ እቃ ከውጪ ተገዝቶ የሚመጣና የሚሸጥ አይደለም የሚሉት ዶ/ሩ፤ “የኢትዮጵያ ህዝብ ከሚያደርገው ትግል የሚመጣ በመሆኑ አንድ የአሜሪካ መሪ ዲሞክራሲያዊ ያልሆነ ሀገርን ስለጐበኘ የትግሉ ተዋናዮች ተስፋ መቁረጥ የለባቸውም ሲሉም አሳስበዋል፡፡
በአሜሪካ ይደግፍ የነበረው የአፄ ኃይለሥላሴ ስርአትም ሆነ በሶቪየቶች ይደገፍ የነበረው የደርግ ስርአት መውደቁን ያስታወሱት ዶ/ር መረራ፤ ይሄም ስርአት ሃቀኛ ዲሞክራሲ ስለማስፈኑ የኦባማ ጉብኝት ማረጋገጫ አይሆንም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ትግልንም አያዛንፈውም ብለዋል፡፡
“ኦባማ ኢትዮጵያን በዚህ ሁኔታ መጐብኘት ለአሜሪካ ህዝብ አሣፋሪ ነው” ያሉት ዶ/ር መረራ በአንፃሩ የኢትዮጵያን ህዝብ ትግል የሚገታው አይሆንም ብለዋል፡፡ ኦባማ ወደ ስልጣን ሲመጣ አምባገነኖች ቦታ አይኖራቸውም እያለ ስለዲሞክራሲ የሚዘምር የነበረና የወጣቶችን ቀልብ መግዛት የቻለ ነበር የሚሉት ዶ/ሩ በመጨረሻ በዚህ ደረጃ መውረዱ ቃሉን እንደበላ ነው የሚያረጋግጠው ብለዋል፡፡
የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት
የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሀሪ በበኩላቸው፤ ፕሬዚዳንቱ የሚመጣበት ጉዳይ ወሳኝነት እንዳለው ጠቅሰው የኢትዮጵያ መንግስት እየፈፀመ ያለውን የዲሞክራሲያዊ መብቶችና ሰብአዊ መብት ጥሰቶችን እንዲያርም የሚያሣስቡ ከሆነ ጉብኝቱ አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል፤ ዝም ብሎ በፀረ ሽብር ጉዳይ ላይ ተወያይቶ የሚመለሱ ከሆነ ትክክል አይሆንም ብለዋል፡፡
ወሳኙ ፕሬዚዳንቱ መጥቶ ምን አድርጐ ነው የሚሄደው የሚለው ጥያቄ ነው፤ የሚሉት አቶ አበባው፤ የሃገሪቱን እድገት አድንቆና ሽብር ላይ ዘክሮ የሚመለስ ከሆነ መምጣቱ ውጤታማ አይሆንም ብለዋል፡፡
ሠማያዊ ፓርቲ
የሠማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው ዮናታን ተስፋዬ በበኩሉ፤ “የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በፓርቲው በኩል ብዙም ትኩረት የሚሠጠው አይደለም” ብሏል፡፡ “ድሮም አሜሪካ አምባገነኖችን ትረዳ ነበር አሁንም እየረዳች ነው” ያለው ዮናታን፤ “በኢትዮጵያ ውስጥ ላለው አፈናና ጭቆናም አንደኛዋ ተባባሪ አሜሪካ ስለሆነች ህዝቡም ያን ያህል ትኩረት የሚሰጠው አይመስለኝም” ብሏል፡፡
ኢዴፓ፣ መኢአድ እና ኢራፓ
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጋራ ጉዳዮች ላይ አብረው ለመስራት ተስማምተናል ያሉት ኢዴፓ፣ መኢአድ እና ኢራፓ በበኩላቸው፡- ፕሬዚዳንቱን የማግኘት የማነጋገር አድሉ ከገጠመን በሰብአዊ መብት ጥሰት እና ዲሞክራሲያዊ ስርአትን ባለማስፈኗ የምትታማን ሃገር ለመጎብኘት ለምን ፈለጉ የሚለውን እንጠይቃቸዋለን ብለዋል፡፡
የአሜሪካው 44ኛ ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ በኢትዮ-አሜሪካ የ112 አመታት የዲፕሊማሲ ታሪክ ውስጥ ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ማቀዳቸው መነጋገሪያ ሆኖ የከረመ ሲሆን ዋሽንግተን ፖስት እና ዘ ጋርዲያን ጋዜጦችን እቅዱን ክፉበኛ አብጠልጥለውታል፡፡

Read 8319 times