Saturday, 19 September 2015 09:33

የኖቤል ሽልማት ጸሃፊው በኦባማ መሸለም መጸጸታቸውን ገለጹ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

    ከስድስት አመታት በፊት ለተካሄደው የ2009 የኖቤል ሽልማት የአመቱ ተሸላሚዎችን የመረጠውን የተቋሙ የሰላም ኮሚቴ በጸሃፊነት የመሩት ጌር ሉንደስታድ፣የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን ለኖቤል የሰላም ተሸላሚነት በመምረጣቸው መጸጸታቸውን እንደገለጹ ቢቢሲ ዘገበ፡፡በወቅቱ ኮሚቴው ኦባማን ለኖቤል የሰላም ሽልማት በዕጩነት ሲመርጣቸው፣ ለዚህ ትልቅ ሽልማት የሚያበቃ ጉልህ ስራ አልሰሩም በሚል ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበር ያስታወሱት ሉንደስታድ፣ሽልማቱ መነቃቃትን ፈጥሮላቸው ተጨባጭ ስራ ይሰራሉ ብሎ በማመኑ ኦባማን ተሸላሚ እንዳደረጋቸው ሰሞኑን ለንባብ ባበቁት የግለ ታሪክ መጽሃፋቸው ገልጸዋል፡፡ ኦባማ ግን ኮሚቴው እንደጠበቀው ለአለም ሰላም ይህ ነው የሚባል ጉልህ ተግባር አልፈጸሙም ያሉት ሉንደስታድ፣ በወቅቱ ኦባማን የኖቤል የሰላም ተሸላሚ ለማድረግ በነበራቸው ተሳትፎ መጸጸታቸውን በግልጽ ጽፈዋል፡፡ኦባማ የ2009 የዓለም የኖቤል የሰላም ተሸላሚ መሆናቸውን በሰሙበት ቅጽበት ነገሩን ለማመን መቸገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ብዙዎቹ የኦባማ ደጋፊዎችም የሽልማቱን ዜና የተሳሳተ ሳይሆን አይቀርም ብለው ተጠራጥረውት እንደነበር ጠቁሟል፡፡
ጌር ሉንደስታድ እ.ኤ.አ ከ1990 እስከ 2015 መጀመሪያ በኖቤል የሽልማት ድርጅት የሰላም ኮሚቴ ጸሃፊ በመሆን ማገልገላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ተሸላሚዎችን በመምረጡ ሂደት ከፍተኛ ተጽዕኖ እንደነበራቸው ጠቁሟል፡፡ የዘንድሮው የአለም የኖቤል የሰላም ተሸላሚ ከ20 ቀናት በኋላ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Read 2428 times