Saturday, 19 September 2015 09:43

አስማት ውበት

Written by  ከወጋየሁ ማዴቦ
Rate this item
(21 votes)

     አስማት የሆነ ውበት ያላት ሲባል እንደ ዘበት ነበር የምሰማው… ለካሰ ያንዳንዱን ሴት ውበት ለመግለፅ ቃላት ሲጠፉ፣የዘመኑ ልጆች ለዘመኑ ውብ ልጃገረዶች የሰጡት የዘመኑ ምርጥ ቃል ነው፡፡….ሳራ አስማት ውበት የተቸራት ልጅ ናት…. ይህችን ውብ አበባ…የመኖር አዙሪት በኔ ምህዋር አስገብቷት……የፍቅር አማልክት ከተተንከረከከዉና ከጋመው እሳት ውስጥ…..ከሚፋጅና ከሚለበልብ ምድጃ ውስጥ…..ከፍም እሳት ውስጥ…“.እንቁ ” አስቀምጠው…  “በምላስህ አውጣና ውሰዳት” ብለው ፈርደውብኝ፣ በምላሴ ያወጣዃትና…..ትኩስ እንባዬን አንገቷ ስር አፍስሼ እንደምወዳት የነገርኳት ልጅ ናት፡፡
….አስማት የሆነ ውበት ላላት ልጅ የሚከፈል ዋጋ ብዙ ነዉ…..እንቆቅልሹም…ማለቂያ የለውም…..
መጀመሪያ አብረን ያመሸን እለት፣ ኮተቤ ብረታብረት ካለዉ የአያቶቿ ቤት ልወስዳት ሄጄ ከመኪና ወርጄ፣ ለሰላምታ እጆቼን ስዘረጋ፣ አይኖችዋን ጨፍና እቅፌ ዉስጥ ገባችና፣ ፊቷን አንገቴ ስር ቀብራ ለሰኮንዶች  ጸ……….ጥ ስትል…..ስስ ጸጉርዋ ፊቴን እየለሰለሰው፣ ሙቀቷን እንዳልሞቀዉ ሲከለክለኝ….በዚያች ጸ…..ጥ ባለችበት ቅጽበት…አንደበት የነበረውና ሞገድ እየረጨ ልቤን ያናገረዉ…..ጡቷ…ነበር!!…..እርግጠኛ ነኝ ጡት መያዣ አላደረገችም፡፡
ረዥም ቤዥ ከለር የሆነ ቀሚስ፣ ቡላ ጫማና ቡላ ቦርሳ…በቃ…እንደ ዋዛ ጸጉርዋን ወደ ኋላ ለቃዋለች….ሽቶ አልተቀባችም…ሊፕስቲክ----ኩል-----ጌጣጌጥ አልነካትም….ጸጉርዋን እንኳን በሻምፖ አልታጠበችውም…በወተት ነው መሰለኝ የሚያጥቧት አያቷ ----- “.ወተት ወተት የምትል ልጅ፣ ቀስተ ደመና የሚረጩ አይኖች ያሏት”….
ወተት ለሆነች ልጅ የሚሆን ጸጥ ያለ ሬስቶራንት ሳስብ……..ቫቲካን  አርኮባሊኖ ትዝ አለኝ፡፡ እዚያ እራት በልተን ወደ ሰፈርዋ ስሸኛት…ዳንስና ብላክ ሌብል እንደምትወድ….የከተማውን ምርጥ የምሽት ክለቦች እየጠራች----ገድልዋን ታብራራ ጀመር….እንትን ሆቴል ዊስኪውን እንዴት አርገዉ ለሴት ልጅ አጣፍጠዉ እንደሚሰጡ ብትቀምሰው…እንትን ክለብ ያለው ዲጄ ሪትም ሲያነብ ብትሰማው….እያለች ተረከችልኝ፡፡ ቅድም ሳገኛት እጅ ያልነካት ትመስል የነበረችዉ ባለ ወተት ልጅ…አሁን ደግሞ….ሰዶምና ገሞራ ውስጥ የመኖሪያ ፈቃድ ያላት መሰለችኝ….
ወደ ቤቴ ስገባ ለራሴ እንዲህ ብዬ ነገርኩት…“አስማት የሆነ ውበት ካላት ልጅ ጀርባ ብዙ ነገር አለ…አርፈህ ተቀመጥ”…..
ብዙ ቀን ዝም አልኳት….ዳሩ…ያችን የመሰለች ልጅ እኔ ፈለኳት አልፈለኳት ምን ይጎልባታል…? ጉዳይዋ ነዉ…? ይግረምህ ብላ ደወለችና…
“ይቅርታ ጠይቀኝ” አለችኝ….
“ለምኑ?” አልኳት….
“ለምኑ ይላል እንዴ….ይቅርታ ጠይቀኝ እኮ ነዉ የምልህ….!!”ተኮሳተረች….
“እሺ…ይቅርታ…!!” አልኳት….
“…ይቅር ብያለሁ….ስራ ስትጨርስ አግኘኝ…እፈልግሃለሁ….;አዘዘችኝና….ዘጋችዉ፡፡
…..ሳገኛት…በነጭ መደብ ላይ ጥቁር ጠቃጠቆ የበዛበት በጣም አጭር ቀሚስ ለብሳ…መሰላል ላይ የቆመች ያስመሰላትን ባለ ረዥም ታኮ ጫማ አድርጋ ነበር…አይኖችዋን ተኩላቸዋለች…ሊፕስቲክ ተቀብታለች…ጥፍሮችዋን ተሰርታለች…ጸጉርዋ ያብረቀርቃል…አንገቷ…ጣቶቿ…ክንድዋ…በጌጣጌጥ ኳኳታ የሚያቃጭል…ደወል ልጅ ሆና አገኘኋት…ከሁሉም በላይ የሽቶዋ መአዛ ጥንካሬና የቀሚሷ እጥረት ትእግስቴን የሚፈታተን ነበር…ዛሬ ደግሞ ጡት መያዣ አድርጋለች፡፡
የላምበረትን ቁልቁለት ስንያያዝ፤ “ዛሬ መደነስ እፈልጋለሁ” አለችኝ፡፡ ሴቶች የወንድን ልብ የሚያዩበት ልዩ መነጽር አላቸዉ….ሺ ጥያቄዎች ቢኖሩኝም የተሸነፈላትን ውስጤን አይተዋለች፡፡ እንደዛ ባይሆን ኖሮ፣ እንደ ዋዛ ወዲህ ና! ወዲያ ሂድ! አትለኝም ነበር፡፡ አልባኒ እራት እየበላን ሰአቱን ገፋንና፣ ጉዞ ወደ ባይላሞስ ሆነ…..ጎበዝ መደነስ መቻል መሰረታዊ ነገር ነው ለካ….ሰዎች አንገት ማስገቢያ ያህል የሚሉት ቢሆንም፤ቃሉ ለዳንስ ከሰራ/ ዳንስ መቻል ያስፈልጋል….ስራዋ ዳንስ ሳይሆን አይቀርም….እስኪያዞረኝ አወዛገበችኝ፡፡…እንደ ህጻን ልጅ ሰውነቴን እየታከከች እንደ ሀረግ ዞረችኝ፡፡…አ….ቤ…..ት… የሰው አይን ሊበላኝ ነበር…ምን ይሆን የሚያዩት….? እስዋ ለጋ ወጣት፣ እኔ ጎልማሳ…እስዋ አጠር ያለች፣ እኔ ረዥም …እስዋ ብላክ ሌብል፣ እኔ ውሃ መጠጣቴን ነዉ?…ብቻ አምላክ አብረሃምን “ቀና ብለህ ቁጠር” ያለውን ክዋክብቶች የሚያክሉ አይኖች አይተውኛል….እስዋን ሳይሆን እኔን ማየታቸውን ነዉ የማውቀዉ….
እስዋ ደንሳና ሰክራ ደከመች….እኔ ተወዛውዤና ተሳቅቄ ደከመኝ፡፡ ግን ደረጃውን ደግፍያት አውርጄ….መኪና ዉስጥ ተሸክምያት አሳፍሬ…ወደ ቤቴ እሽኮኮ ብዬ አስገብቼ…እንደ ሞተ ሰዉ የተዘረጋችውን ልጅ ማስተኛት የውዴታ ግዴታዬ ነበር፡፡….ጠዋት ስራ መሄድ ስለነበረብኝ  ስነሳም አልነቃችም…የሴትን ልጅ ቁንጅና ማረጋገጫ ናሙና የሚወስድበት ትክክለኛው ሰዓት ጠዋት ውሃ ሳይነካት ነው፡፡…ከንፈሮችዋን ሳታላቅቅ…ፈገግ ያለች ከመሰለች…ድምፅ ሳይወጣት ያንሾካሾከች ከመሰለች…ደምዋ ግጥም ብሎ ጸዳልዋ ከበራ….ያች ሴት በርግጥ ውብ ናት….ሳራ ሞታም የምታምር ይመስለኛል….
ቢሮዬ ገብቼ ለራሴ እንዲህ አልኩት፤“ትቅርብህ…!!.ከነውበትዋ… ከነልጅነትዋ…ትቅርብህ…!!.” …ጥያቄ ምልክት ነፍሴ ላይ አትማ…ግራ አጋብታኝ ብወዳትም ትቅርብኝ!!!
…….ሳምንታት አለፉ……..
….ግን አልቀረም…መ/ቤቴ ህንጻ ስር ካለው ካፌ ሆና በሰው አስጠራችኝ፡፡ እውነቱን ለመናገር ናፍቃኝ ነበር…ድርያ ለብሳለች፤ከስስ አላባሽ ሻርፕ ጋር፡፡ …ጸጉርዋን በሻሽ ሸብ አርጋዋለች….ነጠላ ጫማ ነበር ያደረገችው…ሌላው የሴት ልጅ ውበት ናሙና መውሰጃ ሰዓት አልባሌ ልብሰ የለበሰች ጊዜ ነዉ፡፡…ያኔ ውብ ሆና ከታየች፣ ያለ ጥርጥር በመላዕክት እጅ ተሰርታለች፡፡…አቤት ስታምር!…ግንባርዋ ላይ ሳምኳት…ጨፍና ነበር…
“…..ከረዥም ቀሚስ ውስጥ…ካለ መኳኳል ውስጥ…ካለ ማጌጥ ውስጥ…ቤተክርስትያን ከመሳለም ውስጥ…አንገት ከመድፋት ውስጥ…ትህትናና ጨዋነት ያለ….ይመስልሃል!!...በተቃራኒው.....ካጭር ቀሚስ ዉስጥ…ከማጌጥና ከመኳኳል ውስጥ…ከመደነስ ከመዝፈን ውስጥ..ነውርና ክፋት ያለበት ይመስልሃል…!!.ይህ ግን ስህተት ነዉ!!” አለችኝ፡፡
በርግጥ ጸጥ አሰኘችኝ….ቀጠለችናም…“ለመሆኑ አንድ ደስ ያለህ ቦታ ውሰደኝ ብልህ የት ትወስደኛለህ…?” ብላ ጠየቀችኝ…
“…ቤተ ክርስትያን” አልኳት…
“…ሃይማኖትህ ምንድነው….?”
#…ሀይማኖቴ እግዚአብሄርን ማመን ነው…እግዚአብሄርን መፍራት…ለሱ ክብር መኖር…;አልኳት፡፡
“…ውሰደኝ የምልህ ቀን ትወስደኛለህ…” ብላኝ… ያዘዘችዉን ጁስና በርገር ይዛ ..“ሸኘኝ” አለችኝ፡፡ ሰፈርዋ ስሸኛት ነፍሴ “ኢፍ ላቪንግ ዩ ኢዝ ሮንግ…አይ ዶንት ዋና ቢ ራይት…” የሚለውን ዜማ አንጎራጎረችላት…ደርሳ ልትወርድ ስትል…“ልሳምሽ?”…ብዬ ጠየቅኳት…“ለምን ታስፈቅደኛለህ…?”.ብላ ጮሃ ወረደች፡፡ ..እዳዉ ገብስ ነዉ…ሮጬ ያዝኳትና ከንፈሬ የደረሰበት ሁሉ ሳምኳት፡፡
….ልጅና አዋቂ ሆና…ጨዋና ዱርዬ ሆና…ጥሩና መጥፎ ሆና…እንጃ ብቻ ብዙ እንቆቅልሽ ሆናብኝ….ግራ አጋብታኝ…ወደድኳት…!! …ግን ጥሩና መጥፎዋ ምንድነው….? ባልገባኝ ነገር እኔ “የምፈልገው አይነት ሴት” አደርጋታለሁ ብዬ እልህ ተጋባሁ…በርግጥ “ከነፋስ ጋር” ነበር እልህ የያዘኝ…ምን ልሁንልህ…? እንዴት አይነት ሴት ልሁንልህ? እንድትለኝ…ፈለግሁኝ፡፡ …በደግነት….በፍቅር…በመታዘዝ….በመሸነፍ….የምፈልጋት አይነት ሴት አደርጋታለሁ ብዬ ቆረጥኩኝ…፡፡ በርግጥ ወድጃት ነበር…እንድትደውል ሳልጠብቅ ቀንና ማታ ስደውል…ሰንበትና አዘቦት ቀን ሳልለይ እስዋ… ና!!... ያለችኝ ቦታ ሁሉ ስገኝ…ሳከብራት…ስታዘዛት…ሳፈቅራት…ስናፍቃት….ጊዜው ሮጠ፡፡ እስዋ እንቆቅልሽ እንደሆነችብኝ…..ሳራ እንቆቅልሽ እንደሆነች-----ጊዜው ሮጠ…ከሳራ ጋር ፍቅርና እልህ ይዞኝ….ጊዜው ሮጠ፡፡
**************      **************
አንድ እሁድ ረፋዱ ላይ ሚጢጢዬ ቁምጣ በስስ ፓክ አውት ለብሳ ቤቴ መጣችና “ቸርች እንሂድ” አለችኝ….. በርግጥ ደንግጬ ነበር፤ግን ረጋ ብዬ “..ሳርዬ…እንደዚህ ለብሶ ደጀ ሰላም መሄድ ድፍረት ነዉ..ልብሰ ትቀይሪና እንሄዳለን” አልኳት…ህጻን ልጅ እንደማባበል ተጠንቅቄ….
“…ለመሆኑ መድሃኒአለም ነዉ ወይስ ዩጎ ነዉ የምትወስደኝ…?”
“…እግዚአብሄር ወደ ሚመለክበት ወደ ፈለግነዉ እንሄዳለን….ከአምላክ እንጂ ከተቋሙ ምን አለን…” ስላት አፍታም ሳትቆይ…
“…በቃ ከከተማ እንውጣ” አለች….
“…ሳ……ሪ!…?”.አልኳት ጮክ ብዬ
“…ዋ…..ት!……?”አለች እስዋም ጮኻ
“…ቤተ ክርስትያን ካልሄድን ከከተማ እንውጣ….ማለት….በጣም የሚቃረን ነገር እኮ ነው…ሊተካካ አይችልም!!”
“…ሁለቱም የነፍስን ጉድለት ለመሙላት የሚኬድበት መስሎኝ….ነው…”
“የነፍስ ጉድለት”…..የሚለውን ቃል ከአንደበትዋ ስሰማዉ የባሰ ደነገጥኩ….
“…ለማንኛዉም ልብስሽን ቀይሪ ስሞትልሽ….የኔ ቆንጆ….;
“አልቀይርም……ኡ…….ፍፍፍፍፍ…..አስጠላኝ አሁንስ…!!.ከዚህ ቤት እንውጣ….”
“….ምኑ ነው ያስጠላሽ…..ቤቱ ነው…ወይስ የኔ ንግግር?;
“…ሁሉም ነገር…!!.መመከር ሰለቸኝ!! መታረም ደከመኝ…!!መቼ ነው እኔ ትክክል የምሆነው….?“
“…ሳሪ የምትናገሪውን ታውቂያለሸ….?”
“….አውቃለሁ….ሁሉም ነገር አስጠላኝ አልኩህ’ኮ…..!!;
“….ሳሪዬ….እያናደድሽኝ ነዉ….;
“…ገደል ግባ!!”
ብልጭ አለብኝ “….በዛ…..ሳራ በዛ…..; አፈጠጥኩባት….“…ገደል ግባ አልኩህ’ኮ….!!.አትሰማም….??”
ዘልዬ ጸጉርዋን ጨምድጄ….“አንቺ እኔን ነው ገደል ግባ ያልሽኝ…?;.አልኳት…እስዋ መች ከቁብ ቆጥራኝ…እስዋን ትቼ ስልክዋን ግድግዳው ላይ ከሰከስኩት….“አንቺ እኔን ነዉ ገደል ግባ ያልሽኝ…?” አስጓራችኝ፡፡….ግድግዳዉን በቦክስ ነረትኩት….ፊቴ ያገኘሁትን ዕቃ ሁሉ ሰባበርኩኝ…አፌን ሀሞት ሞላው ---”ውጭልኝ!!....በጄ ሰበብ ሳትሆኝ….ዉጪ…..!!!...; ጮህኩባት…
…..ኮስተር ብላ…“ግደለኝ!!”...ብላ አፈጠጠች…
….ዛሬስ….ለየላት….ለካስ ከእብድ ጋር ነዉ….ስወዛገብ የከረምኩት…..ማልቀስ ሁሉ ዳዳኝ….
“…….መምታት አትችል…መጨከን አትችል…..መሳደብ አትችል….ማሳመም አትችል…..ሁሌ ፍቅር…ሁሌ ትህትና….” ማልቀስ ጀመረች….ከዚህ በኋላ ምንም አላልኩም…እስዋ ብቻ ነበረች የምታወራው…
….ባጭሩ………በጣም ባጭሩ…………
….አያቶቿ ቤት ነው እስዋና ታናሽ እህቷ የሚኖሩት…በ15 አመት ታላቋ የሆነው የወላጅ እናትዋ ወንድም….እሽኮኮ ባረጋት ቁጥር ሽንቷን ጭርር እያደረገችበት….እንዳላሳደገ….ከአፉ አውጥቶ አጉርሶ ያሳደገውን…የሳራን ለጋ ገላ፣ ገና በ14 አመትዋ….ወሲብ ባሰከረው ቁጣ፣ በፈርጣማ ክንዱ ፈጥርቆ….ቀደደው፡፡…ለዚህ ነው ሳራ ….ከትህትና ….ከእንክብካቤና….ከፍቅር…ቀጥሎ…. ምህረት የለሽ ጭካኔ….የሚከተል የሚመስላት….ለዚህ ነው በሁሉም ነገርዋ ግድ የለሽ ሆና የቀረችው….
…መሆን የሚገባው…ሳራን አቅፌ እንባዋን ማበስና ቃላት በስለት ሰብስቤም ቢሆን እስዋን ማፅናናት ነበር…ነገር ግን…
…በለቅሶዋ መሃል  ትዝ ያለችኝ…ትንሽ እህትዋ ነበረች….“እህትሽ የት ነው ያለችው….? እስዋስ….እስዋስ…? ሳራ….!!”ብዬ ጮህኩ….ደመ ነፍሴ የሆነ ነገር ነገረኝ….
….አፍጥጣ እያየች….“እህቴ ምን ሆነች…?ቹቹ ምን ሆነች…?”ብላ….በጥያቄ አዋከበችኝ…
“…ለእናትሽ መንገር ነበረብሽ…!! ለአያቶችሽ መንገር ነበረብሽ…!! ስለ ቹቹ ማሰብ ነበረብሽ….!!” የምይዘዉ የምጨብጠው ጠፋኝ….
…ቹቹ ጋ ደወልኩ… “የት ነሽ ቹቹዬ….?”
“..አጎቴ ቤት ነይ ብሎኝ …በምልክት የነገረኝ ቦታ እየደረስኩ ነው….” “…ቹቹ….ተመለሽ…!!አጎትሽ ቤት…እንዳትገቢ….!!ያለሽበት ቁሚ …!!መጣን….” ተያይዘን…ወደ ቹቹ በረርን፡፡…ድንግርግር ያላትን ብላቴና ይዘን ወደ ኮተቤ….ስንሄድ…ሳራ… “ትወደኛለህ..አይደል …??”.አለችኝ
“….አጥንቴ ፈሳሽ እስኪሆን ድረስ እወድሻለሁ….!!” አልኳት…“ሳርዬ፤ ለአጎትሽ የሚሆን ትህትና አይኖረኝም….እፋረደዋለሁ!!.....አንቺን ግን መምታት….መሳደብ…….አልችልም፡፡ እያሳመምኩሽ መሳም…እያሳመምኩሽ ማቀፍ…እያሳመምኩሽ….አልችልም” አልኳት፡፡….. በህይወቴ “ከባድ ነው” ብዬ ያመንኩበት ችግር ውስጥ እየሰመጥኩ እንዳለሁ ገባኝ፡፡…ደስ እያለኝ የምገባበት…የሳራ ፍቅር!!
…..አስማት የሆነ ውበት ካላት ሴት ልጅ ጀርባ ብዙ ጣጣ አለ፡፡

Read 11501 times