የልጅ ኢያሱ አባት፣ የእቴጌ መነን አያት፣ የደሴ ከተማ መስራችና የአድዋ ግንባር ቀደም ዘማች በነበሩት በወሎው ገዢ በንጉስ ሚካኤል ህይወትና ስራዎች ላይ የሚያጠነጥነው “ሚካኤል ንጉሰ ወሎ ወትግሬ” የተሰኘው መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ በምስጋና ታደሰ የተዘጋጀው ይኼው የታሪክ መፅሐፍ፤በ19ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻና በ20ኛው ክ/ዘመን የነበረውን የወሎ ክ/ሀገርንና የኢትዮጵያ ታሪክን ለማወቅ ለሚሹ በመረጃነት ያገለግላል ተብሏል፡፡ አዘጋጁ ምስጋናው ታደሰ፣ መጽሐፉን በሁለተኛ ዲግሪው የማሟያ ፅሁፍ ላይ ተመስርቶ ማሰናዳቱንና የታሪክ ጥናትና ምርምር ሊያሟሏቸው የሚገቡ መስፈርቶችን ለማሟላት ጥረት ያደረገበት እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡ በ220 ገጾች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ70 ብር ለገበያ መቅረቡም ታውቋል፡፡