ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 26 ተጨዋቾች መመረጣቸውን የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኮምዩኒኬሽን ክፍል ያስታወቀው በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ነው፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊሶቹ አዳነ ግርማ፤ ደጉ ደበበ እና ሽመልስ በቀለ የኢትዮጵያ ቡናዎቹ ዳዊት እስጢፋኖስ፤ መሱድ መሃመድ፤ መድሃኔ ታደሰና ሌሎችም በብሄራዊ ቡድኑ የሉበትም፡፡ ከ7 ክለቦች የተውጣጡት 26 ተጫዋቾች ግን ከ3 ቀን በፊት አዲስ አበባ ስታዲየም በሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሪፖርት በማድረግ ወደ ልምምድ ገብተዋል፡፡
ከመከላከያ ይድነቃቸው ኪዳኔ፣ ዓይናለም ኋይሉ፣ ዑመድ ኡክሪና ወንድሜነህ ዘሪሁን፤ከአርባ ምንጭ ሙሉዓለም መስፍንና ገ/ሚካዔል ያዕቆብ ፤ከመብራት ኋይል አስራት መገርሳ፤ከሙገር ሽመልስ ተገኝ፣ አብዱራህማን ጀማል፣ ፍሬው ሰለሞን፣ ደረጀ መንግስቱና ፍፁም ገ/ማርያም ተመርጠዋል፡፡ ከደደቢት መንግስቱ አሰፋ፣ ሮቤል ግርማ፣ አዲስ ህንፃ፣ ምንያህል ተሾመ፣ ጌታነህ ከበደና ዳዊት ፍቃዱ ፤ከሐረር ቢራ ሚካኤል ጋሪ፣ ስንታለም ተሻገር ፤ከሀዋሳ ከነማ ግርማ በቀለና መሐሪ መና ፤ከሲዳማ ቡና ሲሳይ ባንጫ ፣ ቢያድግልኝ ኤልያስና ዓመለ ሚሊኪያስ ፤ከድሬዳዋ ከነማ ሐይማኖት አዲስ ሌሎቹ የቡድኑ አባላት ናቸው፡፡
በሻምፒዮንስ ሊግ ቡና ከኮሞሮሱ ኪዩን ኖርድ ጋር ሲጫወት ጊዮርጊስ ከጋቦኑ ማንጋ ስፖርት ይገናኛል፡፡
ሁለቱም ቡድኖች የመልስ ጨዋታቸውን ከሁለት ሳምንት በኋላ በአዲስ አበባ ያስተናግዳሉ፡፡ ፡
ለብሔራዊ ቡድኑ ጥቅም ሲባል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሁለቱ ቡደኖች የመልስ ጨዋታ በአንድ ሳምንት እንዲራዘም ጠይቋል፡፡ የጋቦኑ ማንጋ ስፖርትና የኮሞሮሱ ኪዩን ኖርድ የጨዋታውን መራዘም ከተቀበሉ ወሳኞቹን የሁለቱን ክለብ ተጨዋቾች በብሔራዊ ቡድን የማካተት እድል ሊኖር ይችላል፡፡ በተያያዘ በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ኢትዮጵያን ወክሎ የሚጫወተው ቅዱስ ጊዮርጊስ በጋቦን የተደረገለት አቀባበል ማዘኑን ገልጿል፡፡ የኮምኒኬሽን ክፍሉ የላከልንን መግለጫ ከነፎቶግራፍ ማስረጃው እንዳመለከተው፡፡ 2 ቀን እንዲያድሩበት ተብሎ ተመድቦላቸው የነበረው ሆቴል ግንባታው ያላለቀ ከመሆኑም በላይ የማይገባ ሆቴል ከመሆኑም በላይ ይህንን ችግር ለማሰተካከል ፈቃደኛ ያልነበረው የማንጋ ስፖርት ክለብ እንዳሳዘነው ገልጿል፡፡
ቡና በዚሁ የቅድመ ማጣርያ የመልስ ጨዋታ የኮሞሮሱን ክለብ ኮዮን ኖርድ ጥሎ ማለፍ ከቻለ በመጀመርያ ዙር የማጣርያ ጨዋታ የሚገናኘው ከግብፁ ክለብ አልሂላል ጋር ነው፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደግሞ ቅድመ ማጣሪያውን በድል ከተወጣ በመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ከቱኒዚያው ክለብ አፍሪካን ጋር ይገናኛል፡፡